አትሮኖስ
281K subscribers
112 photos
3 videos
41 files
481 links
╔╦╦╦═╦╗╔═╦═╦══╦═╗
║║║║╩╣╚╣═╣║║║║║╩╣
╚══╩═╩═╩═╩═╩╩╩
ግጥሞች አዳዲስና ቆየት ያሉ የታዋቂ ደራሲያን መፅሐፍቶችን በ PDF እንዲሁንም
ያልተነበቡ ድርሰቶችን ግጥሞችን ታሪኮችን ያገኙበታል።


Contact. @atronosebot
please dont touch the leave button.😔😳😳
Download Telegram
#ሮሚዮና_ዡልየት

#ክፍል_ሁለት

#ሞንታግ ፡ (መጣ)
ወገኖቼ ሁሉ ድረሱ በፍጥነት
እንሆ ሰውቼን ፈጅዋቸው በድንገት
ሰይፌን ፡ አቀብሉኝ፡ በቶሎ፡ ፍጠኑ ።

የሞንታግ ፡ ሚስት ፡(ተከትላ ፡ መጣች) "
እስቲ፡ ባዶ ፡ እጅዎን ፡ አሁን ፡ ምን ፡ ሊሆኑ ?

#ካፑሌ ፡ (መጣ)

ሰይፌን ፡ አቀብለኝ፡ ማነህ ፡ ቶሎ ፡ ድረስ
የካፑሌ ፡ ሚስት ፡(ተከትላ ፡ መጣች) ።
ሽማግሌው ፡ አብዷል ፡ ድረሱልኝ ፡ በነፍስ

#ወታደር
ይርጋ ፡ በየቦታው ፡ ሁሉም ፡ ጠቡን ፡ ትቶ
ልዑልነታቸው ፡ መጣ ፡ ተቆጥቶ ።

#መስፍኑ ፡ (አገረ ገዥ) ።መጣ
መልካም ፡ ነው ፡ አየነው ፤ ይብቃ ፡ አሁን ፡ እርጉ፤ውጊያውን ፡ ትታችሁ ፡ ወደ ፡ እኔ ፡ ተጠጉ ፡
#ካፑሌና#ሞንታግ ፡ ልንገራችሁ ፡ ስሙ
የናንተ ፡ አምባጓሮ ፡ በመደጋገሙ ፡
አልነቀል ፡ ብሎ ፡ የቂማችሁ ፡ መርዙ ፡
ሥር ፡ ስለ ፡ ሰደደ ፡ ጠንቃችሁ ፡ መዘዙ ፡
ደከመኝ ፡ ሰለቸኝ ፤ ታከተኝ ፡ በብዙ ።
ምንድንነው ፡ በውነቱ ፡ እንዲህ ፡ ያለ ፡ ነገር፤ ሰላም 'እያወኩ' ዘለዓለም ፡ ማስቸገር ።
ሁል ፡ ጊዜ፡ ግርግር' ሁል፡ጊዜ ፡
ሁል ፡ ጊዜ ፡ አምባጓሮ 'ሁል ፡ ጊዜ ጫጫታ ።
በናንተ ፡ ምክንያት ፡ ስንት ፡ ደም ፡ ፈሰሰ፤
ስንት፡ጊዜ፡አገሩ፡ጸጥታው፡ ፈረሰ ፡
ስንት ፡ ጊዜ ፡ በጠብ ፡ ከተማው ፡ ታመሰ ?
አገሬ ፡ በናንተ ፡– ንገሩኝ ፡ በሉ ፡ እኮ ፡
እስከ ፡ መቼ ፡ ድረስ ፡ ይኖራል ፡ ታውኮ ?
እስቲ ፡ በማን ፡ አገር ፡ እስቲ ፡ በማን ፡ ዕድሜ፡ እንዲህ ፡ ያለ ፡ ጥጋብ ፡ የሌለው ፡ፍጻሜ፡
እስከ ፡ ዛሬ ፡ ድረስ ፡ ይታወቃል 'ታይቶ ፤
ማንም ፡ ሰው ፡ ይፍረደው ፡ ይህን ፡ተመልክቶ ።
እስከ ፡ መቼ፡ድረስ ሕዝቤ ፡ በሰይፍ፡ያልቃል?
ትሰሙኝ ፡ እንደሆን ፡ እንግዴህ ፡ ይበቃል
በእውነቱ ፡ ዕወቁት' ከዛሬ ፡ ጀምሮ '
በናንተ ፡ መካከል ፡ ቢሆን ፡ አምባጓሮ '
አዝዣለሁ ፡ አጥፊው ፡ በሞት ፡ እንዲቀጣ
አለዚያም ፡ ጨርሶ ፡ ካገር ፡ እንዲወጣ ።
እንግዴህ ፡ ልባችሁ ፡ የኔን ፡ ፍቅር ፡ ቢሻ ፡
የዛሬው ፡ ጠባችሁ ፡ ይሁን ፡ መጨረሻ ፡
ስታዝኑ ፡ እንዳልሰማ ፡ በኋላ ፡ በፈራጅ ፡
ይህን ' ያሁን 'ቃሌን ፡ ቁጠሩት፡ እንዳዋጅ"

#ካፑሌ#ፓሪስ ፡ አንድ ፡ #አሽከር

#ካፑሌ
የመስፍኑ'ትእዛዝ ፡ ስለ ፡ ሆነ ፡ ብርቱ ፡
ሞንታግና ፡ እኔ ፡ ሳስበው ፡ በውነቱ ፡
እንግዲህ ፡ ጠባችን ፡ እየቀዘቀዘ :
ይሄድ' ይመስለኛል ፡ ባዋጅ ፡ ከተያዘ ።

#ፓሪስ
ስማችሁ ፡ ዝናችሁ፡ በጣም ፡ የታወቀ ፡
እንዲሁም ፡ ክብራችሁ ፡ ከሁሉም ፡ የላቀ ፡
ሆኖ ይህን ፡ ያኽል ፡ ጊዜ ፡ ተጣልታችሁ ፡
በጣም ፡ ያሳዝናል ፡ በጠብ ፡ መኖራችሁ ፤
እረ ፡ እንደ ፡ ምን ፡ ሆነ ፡ ደግሞስ ፡ የኔ ፡ ነገር ?
ልጅዎን ፡ ለማግባት ፡ ጠይቄዎት ፡ ነበር ።

#ካፑሌ
ችላ ፡ ብዬ ፡አይደለም ፡ ጥቂት ፡ ጊዜ ፡ ታገሥ ፤
ዡልዬት ፡ ከፍ ፡ ትበል ፤ ለመታጨት ፡ ትድረስ ፡
አሁን ፡ አእምሮዋ ፡ ዕውቀቷም ፡ አልጠና
ከልጅነት ፡ ዕድሜ ፡ አልወጣችም ፡ ገና ፡
እስከዚያ ድረስ ፡ ግን 'አንተ ፡ ተላመዳት ፤
ትወቅህ ፡ ዕወቃት ፡ትውደድህ ውደዳት
አሁን ፡ ለምሳሌ ፡ ይኸው ፡ ዛሬ ፡ ማታ ፡
ትልቅ ፡ ግብዣ ፡ አድርጌ ፡ በቤቴ ፡ ጨዋታ፡
ደስታም ፡ ይሆናል ፡ አንተም ፡ እንዳትቀር ፤
ናና፡ ከሷ ፡ ጋራ ፡ ቀርበህ ፡ ተነጋገር ።
በጣም ፡ ተዋወቁ፤

ና፡ እባክህ ፡ አንተ ፡ #አሽከር

በዚህ ፡ ወረቀት፡ ላይ ፡ ተጽፎ ፡ ስማቸው ፡
የሚነበበውን ፡ ቶሎ ፡ ፈልጋቸው ፤
ውጣ ፡ ከከተማ ፡ ዙር ፡ በየመንገዱ ፤
ታገኛቸዋለህ ፡ በድንገት ፡ ሲሄዱ ።
አደራ ፡ በላቸው ፡ ማታ ፡ እንዲመጡ ፤
ከግብዣዬ ፡ ቀርበው ፡ በልተው ፡ እንዲጠጡ ፡
እንዲጫወቱልኝ ፡ ፈቃዴ ፡ መሆኑን ፡
ፈጥነህ ፡ ንገራቸው ፤ ቶሎ ፡ ሂድ ፡ አሁኑን

#አሽከር ፡(ወረቀት ፡ ተቀብሎ ፡ ሄዴ) ።

(#ሮሜዎና#ቤንሾሊዎ) "

#ሮሜዎ
የነካፑሌ ፡ አሽከር ፡ አንድ ፡ ወረቀት ፡ ይዞ ፡
መንገድ ፡ አገኘሁት ፡ ሲመለከት ፡ ፈዞ ፡ .
እሱስ ፡ ለካ ፡ ማንበብ ፡ የማያውቅ ፡ ኖሮ ፡
የሚያነብለት ፡ ሰው ፡ በጣም ፡ ተቸግሮ ፡
እኔን ፡ ቢለምነኝ፡ እኔም ፡ የነሱ፡አሽከር ፡
ሳላውቅ ፡ መሆኑን ፡ ባለመጠራጠር፡
ምንም ፡ ሳልተረጒም ፡ በደግም ፡ በመጥፎ ፡
የብዙ ፡ ሰዎች ፡ ስም ፡ አየሁኝ ፡ ተጽፎ ።
አንብቤ ፡ ስጨርስ ፡ ከሰማ ፡ በኋላ ፡
በወረቀቱ ፡ ላይ ፡ ስማቸው ፡ የሞላ፡
ምንድናቸው ፡ ብዬ ፡ እኔ ፡ ብጠይቀው ፡
ዛሬ ፡ ካፑሌ ፡ ቤት ፡ ማታ ፡ራት፡ተጋብዘው ፡
የሚመጡ ፡ ናቸው ፡ አለና ፡ ነገረኝ ።

#ቤንቮሊዎ
- እኔም ፡ ሰምቻለሁ ፡ እንኳን ፡ አስታወስከኝ ፡
እርግጥ፡በነሱ ፡ ቤት ፡ ይኸው ፡ ዛሬ ፡ ማታ
ትልቅ ፡ ግብዣ ፡ ሆኖ ፡ የዳንስም ፡ ጨዋታ ፡ብዙ፡ሰው፡ተጠርቷል፤ሰውም፡ የሚሄደው!
ፊቱን ፡ በመሰውር ፡ እየሸፈነ ፡ ነው ።
ስለዚህ ፡ አያውቅም ፡ አንዱን፡አንዱን ፡ ለይቶ ፤
አንተና፡እኔ ፡ብንሄድ ፡ ማንም ፡ ቢሆን ፡ ከቶ
አያውቀንምና ፡ እንሂድ ፡ ሳንፈራ ፤
እዚያም ፡ ከሮዛሊን ፡ ካንተ ፡ እጮኛ፡ጋራ ፡
እንገናኛለን ፡ ተጠርታለችና።

#ሮሜዎ
እውነት ፡ ቤንቮሊዎ ፡ አስበሃል ፡ ደኅና ፡
በል'እንግዴህ ፡ ፍጠን ፡ ቶሎ ፡ እንሰናዳ
እውነትም ፡ ባስበው ፡ የኔን ፡ ጽጌ ፡ ረዳ ፡
ካየኋት ፡ ቈይቷል ፡ ወር ፡ ሆኖኛል ፡ ይኸው ፤
በጣም ፡ ጥሩ'አሳብ' ነው፡አሁን'ያመጣኸው ።

(#ሮሜዎና' #ሜርኮቲዎ)

#ሜርኩቲዎ
ወዴት ፡ ትሄዳለህ ፡ እንዲህ ፡ በጨለማ ?

#ሮሜዎ
ዐይንህ፡እንዳላየ ፡ ጆሮህ'እንዳልሰማ ፡
ሆነህ ፡ ዝም ፡ ብለህ ፡ እለፍ ፡ በጐዳና ፤
ማንም ፡ ሰው ፡ እንዲያውቀኝ ፡ አልፈልግምና ።

#ሜርኩቲዎ
ባሁን ፡ ሰዓት ፡ ስትሄድ ፡ ብቻህን ፡ አይቼ ፡
ለመቅረት ፡ አልችልም ፡ ካንተ ፡ ተለይቼ ።

#ሮሜዎ
ልብህ 'እንዳይሠጋ፡ ሆድህ ፡ እንዳይፈራ ፡
ምስጢሬን ፡ ልንገርህ ፡ የኔ ፡ ባልንጀራ ፤
ዛሬ ፡ ካፑሌ ፡ ቤት፡ ትልቅ ፡ ግብዣ ፡ ሆኖ ፡
ሰዉ ፡ በመሰውር ፡ ፊቱን ፡ ተሸፍኖ ፡
ዳንስ ፡ ይጫወት፡ ነበር፡ ከቤንቮሊዎ፡ጋራ፡
ማንም ፡ ሰው ፡ ሳያየን ፡ ገባን ፡ ሳንፈራ ፡
የቀድሞ ፡ እጮኛዬን ፡ ሮዛሊንን' ልሻ '
ሄጄልህ ፡ ነበረ ፤ ኋላም ፡ መጨረሻ ፡
በጣም ያስገርማል ፡ ይደንቃል ፡ ወዳጄ፤
አልማዝ አገኘሁኝ ፡ ወርቅ ፡ ልሻ 'ሄጄ
የነካፑሌን ፡ ልጅ ፡ ዡልዬትን ፡ አይቼ ፡
በውበቷ ፡ ብርሃን ፡ መጣሁ ፡ ተረትቼ ፡
ግብዣው ፡ ስላለቀ ፡ ሰዉ ፡ ተበትኖ ፡
ብቅ ፡ ብትልልኝ ፡ ምናልባት ፡ ልቧ ፡ አዝኖ
ይኸው ፡ መሄዴ ፡ ነው ፡ ደግሞ ፡ ተመልሼ
እመጣለሁ ፡ አሁን ፡ በፍጥነት ፡ ደርሼ ።

#ሜርኩቲዎ
እንዴት ፡ ትሄዳለህ፡ደፍረህ ፡ ከነሱ ፡ቤት ?
አንድ ፡ ሰው ፡ ከነሱ ፡ ቢያገኝህ ፡ በድንገት
ዕወቅ ፡ ይገድልሃል ፡ አብደሃል ፡ ፈጽሞ ፤
በራቸው ፡ ይዘጋል ፡ ለመግባትስ ፡ ደግሞ
እንዴት ፡ ትችላለህ ? ይቅርብህ ፡ ተመለስ

#ሮሜዎ
ማ ፡ ሊያየው ፡ ይችላል ፡ ሰው ፡ ጨለማ ፡ ሲለብስ ?
አጥሩ ፡ ቢረዝም ፡ በሩ፡ ቢጠነክር ፡
ጠላትም ፡ አድፍጦ ፡ ሊገድለው ፡ ቢሞክር
ሰው ፡መውደድ፡አድሮበት፡ፍቅር ካሰከረው
ምንም ፡ አያግደው ፤ምንም አይበግረው
ባገኛት ፡ ቢቀናኝ ፡ ቶሎ ፡ ልምጣ ፡ ሄጄ ፤
ሜርኩቲዎ ፡ደኅና ፡ እደር ፡ አትሥጋ ፡ ወዳጄ።

💫ይቀጥላል💫
#ሮሜዎና_ዡልዬት

#ክፍል_ሶስት

#ሜርኮቲዎ
የሆነስ ሆነና ቀጠሮ ግን አለክ?

#ሮሜዎ
የወጣ ፡ ቃል ፡ የለም ፡ አፋችን ፡ ተናግሮ ፡
ዳሩ ፡ ግን ፡ ተያይተን ፡ ባይን ፡ ስንገናኝ ፡
ለኔ ፡ መፈጠሯ ፡ ለልቤ ፡ ተሰማኝ ።
እሷም ፡ እንደዚሁ ፡ በውስጣዊ ፡ ልቧ ፡
አይጠረጠርም ፡ እንደ ፡ እኔ ፡ ማሰቧ ።
እጅግ ፡ የሚያስደንቅ ፡ ለብልኋ፡ አስተዋይ
እነሆ ፡ ይኸ ፡ ነው ፡ የሰው ፡ ፍቅር ፡ ጠባይ
አፍ ፡ ሳይንቀሳቀስ ፡ ታስሮ ፡ በዝምታ ፡
ልብ ፡ ከልብ ፡ ጋራ ፡ ያደርጋል ፡ ጨዋታ ፡
ተወኝ ፡ ልሂድበት ፡ እንግዲህ ፡ ደኅና ፡ እደር ፤
እኔን ፡ አየሁ ፡ ብለህ ፡ ለሰው ፡ አትናገር ።

(ሮሜዎ ፡ ሄደ) ።

#ሮሜዎ ፡ (በዡልዬት ፡ መኝታ ፡ ቤት ፡ አጠገብ • ማታ፡በጨረቃ ከውጭ ፡ ሆኖ)

የሚያፈቅራትን ፡ ልጅ ፡ የሚጠብቅ ፡ ወጣት ፡ ረዝሞ ፡ ይታየዋል ፡ ደቂቃ ፡ እንደ ሰዓት ፤ሰዓቱም ፡ እንደ ፡ ቀን ፥ ቀኑም ፡ እንደ ፡ ዘመን እኔስ ፡ መሞቴ ፡ ነው ፡ በፍቅሯ ፡ ሰመመን ።

(#ዡልዬት ፡ መስኮት ከፍታ'ብቅ'አለች "
አሳቤ ፡ ተነሣ 'ተከፈቱ'ዐይኖቼ፤
ደሜ ፡ ተንቀሳቀስ፡ተፍታቱ ፡ ሥሮቼ ።
ልቤ ፡ ተስፋ፡ ሲቈርጥ ፡ የማትወጣ ፡ መስሎት ፡ ያቻት፡ የኔ ፡ ሥራ ፡ ብቅ አለች ፡ በመስኮት ።
ልቤ ፡ ደስ ፡ ይበልህ ፡ መንፈሴ ተሸበር ፤
የዡልዬትን ፡ ውበት ፡ እንግዴህ 'ልናገር ፤
መስኮቷ ፡ ምሥራቅ ፡ ነው' ፊቷ' የጧት'ጀንበር ብርሃኗ' የለውም ፡ የሚያግደው ' ድንበር ።
ሰላም ፡ ላንቺ ፡ ይሁን ፡ ትልሻለች ፡ ነፍሴ ፤
ጮራሽ፡ ኣለበሰኝ ፡ ከእግር ፡ እስከ ፡ ራሴ ፡
እኔ ፡ እንደምወድሽ ፡ አታውቂውም ፡ ፍቅሬ ፤
አላጫወትኩሽም ፡ ባፌ ፡ ተናግሬ ፡
ካየሁሽ ፡ ይበቃል ፡ ቆሜ' ከሩቅ ፡ ቦታ፤
ያጠግበኛልና 'ያይኖችሽ ፡ ጨዋታ ፡
ዐይንሽ ፡ የሚመስለው ' የርግብ ፡ የሚዳቋ ፣
እኔ ፡ የማልጠግበው 'አለው ፡ ልዩ ፡ ቋንቋ
ዐይኔ ፡ እንደ ፡ ቀለበት ፡ ጣትሽ ፡ ላይ ፡ ተሰካ ፤
እዩት ፡ በቀኝ ፡ እጅዋ 'ጕንጮቿን ' ስትነካ ፡
የእጅ ፡ ሹራብ ፡ ሆኜ፡ ገላሽን ፡ ባለብሰው ፡
ፊትሽን ፡ ጕንጭሽን' ዡልዬት፡ብዳብሰው ፡
ደስታ፡ሕይወቴን'እንደ 'ምን' ባደሰው !

#ዡልዬት
ሮሜዎሮሜዎ'የልቤ'ወለላ '
እባክህ ፡ ለውጠው ፡ ስምህን ፡ በሌላ ፡
ፍቅራችንን 'ገደል ፡ ሆኖ ፡ የሚያግደው
ቂም ፡ በቀል ፡ ስላለ ፡ ኀጢአት ፡ የወለደው ,
እኔም ፡ ዘሬን ፡ ልካድ፤ አንተም'ዘርህን ፡
የኔ ፡ አባት ፡ ላንተ' አባት ፤ የናንተ ፡ ዘር ፡ ለኛ መሆኑን ' አትርሳ ፡ ባላንጣ 'ደመኛ ።

#ሮሜዎ
ይህን ፡ ኣልዘነጋም ፡ ዡልዬት ፡ ይሰማኛል
ነገር ፡ ግን 'ምን ፡ በቀል'ምንስ'ቂም ፡ ይገኛል ፡
ምንስ ' ጠላትነት ስታስቢው ፡ በሰው ፡
የፍቅር ፡ ማዕበል ፡ የማይደመስሰው ፡
የኔ ፡ አባት ፡ ላንች ፡ አባት' ቢሆንም ፡ ባላንጣ ፡
እኔ ፡ እወድሻለሁ ፡ ነፍሴ ፡ እስክትወጣ ።

#ዡልዬት
ሮሜዎ ፡ እውነት ፡ ነው ፡ ዕድሜ ፡ ለሰው ፡ ክፋት !
በፍቅር ፡ መካከል ፡ አለ ፡ ብዙ፡ ዕንቅፋት ፡
የጌታ ፡ ልጅ'ድኻን 'አይውደድ' ይላሉ ፤
ብዙዎች ፡ ልጃቸውን ' በዚህ ' ይክዳሉ ፡
ዳሩ ፡ ግን ፡ የሰው ፡ ልብ ፡ በሰው ፡ አይመራም
የፍቅራችን ፡ መብራት፡በትእዛዝ አይበራም
ልጅ' ካባት 'አጣልቶ፡ብዙ፡ ሰው ፡ የጐዳ '
ይህን'የመሰለ'አለብን'ብዙ ዕዳ "
ቂም ፡ በቀል ፡ የሚሉት ፡ መከረኛ' ጣጣ'
ካያት ፡ ካባት ' ከናት ' ከዘር ፡ የሚመጣ
እኛ ፡ እንዳንፋቀር ፡ ማንንም ፡ ሳንፈራ ፡
ሆኖብን ፡ ተገኘ ፡ የፍቅር 'ደንቃራ ፤
ዳሩ ፡ ግን ፡ ይህ ፡ እክል ፡ ለሰው ፡ የማይራራ
እጅ ፡ እግር ፡ የሌለው ፡ እኛ፡ የማናውቀው፡
አይችልም ፡ ልብህን ፡ ከልቤ ፡ ሊያርቀው :
ሞንታግስ ምንድነው ፡ ፊደል አይደለም፡ ወይ ?
እኛን ፡ ሊለያየን'አይችልም ፡ ፍቅሬ ፡ ሆይ ፡
ስሟን 'ብንለውጠው ፡ እስቲ ፡ ጽጌ'ረዳ ፡
ይችላል ፡ ወይ ፡ መልኳ፡ ሊለወጥ ' ሊጐዳ
አይችልም ፡ ውሸት ፡ ነው ፡ በማዛ ፡ በውበት ፤
ጽጌ ረዳ'ያው ፡ ነች፡አይነካትም ፡ጕድለት ፡
ሮሜዎም ፡ እንዲሁ ፡ ስሙን ፡ ቢለውጠው ፡
ባሕርዩን 'ኣይችልም ፡ ከቶ ፡ ሊያናውጠው
ተወዳጅነቱ ፡ እስከ ፡ ዘላለሙ ፡
በጠባይ ፡ ነው ፡ እንጂ ፡ አይደለም ፡ በስሙ ።
ያንተ ፡ ስም ፡ ቢለወጥ፡ ዋጋህን ፡ አትርሳ ፡
እኔን ፡ ማግኘትህ ፡ ነው ፡ ያንተ ፡ ትልቅ ፡ ካሳ ።

#ሮሜዎ
በመካከላችን ፡የተገኘው ፡ እክል ፡
ስሜ ፡ ከሆነማ ፡ የኛ ፡ መሰናክል ፡
አጭር ፡ ነው፡ ነገሩ፡ ዡልዬት፡ የኔ፡ ፋና ፡
አንቺን ፡ ደስ ፡ እንዲልሽ ፡ ለፍቅሬ ፡ ዋስትና ፡
ላደርገው ፡ የማልፈቅድ ፡ ነገር ፡ የለምና ፤
ቢያስፈልግ ፡ ልነሣ ፡ ዳግም ፡ ክርስትና ፡
ሲሰማ ፡ እንዳይቀፈው ፡ ስሜን ፡ ያንቺ ፡ ዦሮ ፡
ሮሜዎ ፡ኣይደለሁም ፡ ከዛሬ፡ ጀምሮ ፤
ፍቅርሽና ፡ ፍቅሬ ፡ በዘር ፡ ቂም ፡ ኣይፈርስም ፤
ከዛሬ ጀምሮ' ይለወጥ ፡ የኔ ፡ ስም ።

#ዡልዬት
ማነህ ፡ አንተ ፡ ከዚህ ፡ የቆምከው ፡ ከደጄ ?
ባይኔ ፡ የማላይህ ፡ የማልነካህ ፡ በእጄ ፡
ጨለማ ፡ የለበስክ ፡ የፍቅር ፡ ማዕበል ፡
የልቤ ፡ ነበልባል ፡ ስምህን ፡ ማ ፡ ልበል?

#ሮሜዎ
ባንቺ ፡ ፍቅር ፡ ብቻ፡ የሚኖር ፡ ከርታታ፡
የቀን ፡ ብርሃን ፡ ሸሽቶ ፡ የመጣ ፡ በማታ ፡
አንቺን በመውደዱ ፡ ከራሱ'አብልጦ ፡
ያለ ፡ ስም ፡ የቀረ ፡ ስሙንም ፡ ለውጦ ።

#ዡልዬት
ያጥራችን ፡ ግንቡ ፡ ትልቅ ፡ አይበገር ፤ ..
እንዴት ፡ ነው ፡ የገባህ ፡ አንተም ሳትቸገር ? .
መች ፡አጥር ፡ብቻ ነው ፡ ትልቁን ፡ጉድ ትቼ
ደግሞም ፡ ይገድሉሃል ፡ቢያዩህ ፡ ዘመዶቼ

#ሮሜዎ
ፍቅር ፡ ስለ ፡ ሆነ ፡ ጕልበቴና ፡ ክንፌ ፡
ግንቡ ፡ ሳያግደኝ መጣሁኝ ፡ አልፌ ፡
ጨለማም ፡ አጥርም ፡ ሳያሰናክለኝ ፡
እንዴት ፡ ያለ ፡ ሰው ፡ ነው ፡የሚከለክለኝ ?

#ዡልዬት
ታዲያ ፡ እዚህ ፡ ቢያገኙህ፡ይገድሉህ ፡ የለም ፡ ወይ?

#ሮሜዎ
ለኔ ፡ ምንም ፡ አይዶል ፡ ይህ ፡ ሁሉ ፡ ፍቅሬ ፡ ሆይ ፡
አጥር ፡ እጥሳለሁ ፡ ጦርም ፡ አያግደኝ ፤
ብርሃን ፡ የሞላበት ፡ እኔን ፡ ያሳበደኝ ፡
ጦሩስ ፡ ያንቺ ፡ ዐይን ፡ ነው ፡ የኔን ፡ ልብ ፡ የወጋ
በፍቅር ፡ ኣይተሽኝ ፡ መንፈሴ ፡ ቢረጋ ፤
ምንም ፡ ባላሠጋኝ ፡ የቀረው ፡ አደጋ ።

#ዡልዬት
ሳይህ ፡ በኛ ፡ ግቢ ፡ ይሰማኛል ፡ ሥጋት ፤
በሻምላ ፡ ወይ ፡ በጦር ፡ ልብህን ' ለመውጋት ፡
ስለማይመለስ ፡ ወገኔ ፡ አንተን ፡ አይቶ ፡
ቢያዩህ ፡ አልፈልግም ፡ ምንም ፡ ቢሆን ፡ ከቶ ።

#ሮሜዎ
ዥልዬት ፡ አታስቢ ፡ አትሥጊ ፡ለነፍሴ
ወዳንቺ' ስመጣ፡ ጨለማ ፡ ነው ፡ ልብሴ ፡
ትወጂኝ ፡ አትወጂኝ ፡ ባለመለየቴ ፡
ይህ ፡ ብቻ ፡ ነው ፡ ለኔ ፡ ሕመሜና' ሞቴ ፤
ስለዚህ ፡ ንገሪኝ፡ ምንም ፡ አትደብቂ ፤
ሌላውን'አደጋ ፡ ግድ ፡ የለሽም ፡ ናቂ ።
አትወጂኝ' እንደሆን ፡ ሰፊ ፡ ነው፡ ሐዘኔ ፤
በዚህ ፡ ሕመም ፡ ብቻ ፡ እሞታለሁ ፡ እኔ ።

#ዡልዬት
እፍረት ፡ እንዳይዘኝ ፡ ጨለማ ፡ ለብሼ ፡
እንግዲያው ' ልንገርህ ፡ አሳቤን ፡ ጨርሼ
እፍረት'ደኅናሰንብት መግደርደር ደኅና ሁን
ሮሜዎ 'አንድ ፡ ነገር ፡ ልጠይቅህ ፡ አሁን ፡
ከፊቴ የቆምከው ፡ ወዳጄ ፡ ፍቅሬ 'ሆይ'
ካንጀትህ ' ከልብህ ፡ ትወደኛለህ ' ወይ ?
ማንንም ፡ አልወድም ፡ ብለህ ፡ካንቺ ፡ሌላ
ትናገራለህ ፡ ወይ ፡ አሁን ፡ በመሐላ ?
እኔ ፡ ባንተ ፡ ፍቅር በጣም ፡ ተጨንቄ '
ስለምወድህ ፡ ነው ይህን
መጠየቄ '
እኔስ ፡ የት'ዐውቃለሁ፡ትወደኝ' አትወደኝ
ይህንን • ከድፍረት' ቆጥረህ 'አትፍረደኝ "
ካፌ፡ በመውጣቱ ፡ እንደዚህ ፡ ያለ ፡ ቃል ፡
እንዳትገምተው ፡ ጠባዬን ፡ በቀላል ፥
ከልብህ ፡ እንደሆን ፡ መንፈሴ ፡ ይረጋል ፤
መሠረት ፡ ከሌለው ፡ ፍቅር ፡ ምን ፡ ያደርጋል ።

#ሮሜዎ
እንደ ኣልማዝ እንደ ፡ዕንቍ ውበቷ' በጠራ'
በመስክ ፡ በሸለቆ ፡ በዱር ፡ በተራራ ፡
ብርሃን ፡ በዘረጋች ፡ መሬት ፡ ላይ ፡ ፈንጥቃ ፡
እምልልሻለሁ ፡ በዚች ፡ በጨረቃ ።

#ዝልዬት
ተው ፡ አስብ ፡ ተመልከት ፡ አንድ ፡ ነገር ፡ ፍራ ፤
ፍቅርህ ፡ ተለዋዋጭ ፡ እንዳይሆን ፡ አደራ
በጨረቃ ' አትማል ፡ በዚች ፡ ወረተኛ፤
ሁሉ ፡ ቀን ፡ አትገኝ ፡ ዘወትር ፡ መንገደኛ ፡
ወር፡አይሞላምና ፡ ይህ ፡ የሷ ፡ ግሥገሳ፤
ምን ፡ ጊዜም ፡ ያስታውሰው ፥ ልቡናህ ፡ አይርሳ '
አለች ፡ ስንል ፡ ኰርተን ፡ በብርሃን ፡ ሞገሷ፡
ለጨለማ ፡ ትታን ፡ ትጠፋለች ፡ እሷ ።

#ሮሜዎ

በምን 'ልማልልሽ ንገሪኝ' ዥልዬት !

💫ይቀጥላል💫
#ሮሜዎና_ዡልዬት

#ክፍል_አራት

#ዡልዬት
ይቅርብኝ 'አትማል በውነትም ፡ በውሸት ፡
ደግሞም ፡ ልማል ፡ ብለህ፡አሳብህ ፡ ከጸና
ምን ጊዜም ፡ ጣዖቴ ፡ ፍቅሬ ፡ አንተ ፡ ነህና
በራስህ ፡ ማልልኝ ፡ የኔ ፡ ሁለንተና ።

#ሮሜዎ
እንግዲያውስ ፡ ስሚ ፡ እኔ ፡ አንቺን ፡ መውደዴ ፡

#ዡልዬት
ይቅር ፡ በቃ ፡ አትማል ፤ ተናወጠ ፡ ሆዴ ፡
ፈጥነህ ፡ ብትምልልኝ ፡ አሁን ፡ ዛሬ ፡ ማታ
ምንም ፡ አይሰማኝ ፡ ለልቤ ፡ ደስታ ፡
እንደዚህ ፡ በድንገት ፡ እንዲህ ፡ በችኰላ ፡
እንደዚህ ፡ በቶሎ ፡ የሆነ ፡ መሓላ ፡
መሠረት ፡ የለውም ፡ ይጠፋል ፡ ባንዳፍታ፤
አላፊ ፡ ነፋስ ፡ ነው ፡ የሰማይ ፡ ብልጭታ
የፍቅሩ፡ ቡቃያ ፡ ከዛሬ ፡ ጀምሮ ፡
ለምልሞ ፡ ይጠንክር ፡ በልባችን ፡ አድሮ ፡
እኛም ፡ እዚያ ፡ ድረስ ፡ሆነን ፡ ትዕግሥተኛ
ወደየቤታችን ፡ ገብተን ፡ እንተኛ ።

#ሮሜዎ
ልትሄጂ ፡ ነወይ ፡ ትተሽኝ ፡ በከንቱ ?

#ዥልየት
ይበቃል ፡ ለዛሬ ፡ መሽብን ፡ ሰዓቱ ።

#ሮሜዎ
ስጭኝ ፡ የሚያጠግብ፡አንድ ፡ ቃል ፡ የበቃ

#ዡልዬት
አንተ ፡ ሳትጠይቅ ፡ በፊት፡ዡልዬት ፡ዐውቃ
ሰጥታህ፡ወስደኸዋል፡የፍቅሯን፡ቃል ኪዳን
የተረፈው ፡ ይደር ፡ ለነገ ፡ እንዲረዳን ።

#ሮሜዎ
መልሰሽ ወስደሺው ፡'መልካሙን ፡ ስጦታ

#ዡልዬት
ቃሌን ፡ እሰጣለሁ ፡ ላንተ ፡ በችሮታ
የልቤ ፡ ደግነት ፡ ባሕር ፡ ነው ፡ ስፋቱ ፤
ፍቅሬም ፡ እንደዚሁ፡ ጥልቅ ፡ ነው ፡ ርቀቱ
መልካም ፡ ጠባዮቼ ፡ እነዚህ ፡ ሁለቱ ፡
ሰፊ ፡ ሀብት ፡ናቸው፡ ከሁሉም ፡ የላቁ ፤
ብሰጥህ ፡ ብሰጥህ ፡ ምን ፡ ጊዜም ፡ አያልቁ ።
(#ሞግዚቷ' #ጠራቻት ) ።
ጠሩኝ ፡ ድምፅ ፡ ሰማሁ ፡ በል ፡ ሄድኩኝ፡ደኅኖ፡እደር።
ሞግዚቴ ፡ እሺ ፡ መጣሁ ፤ ሮሜዎ ፡ አንድ ነገር ፡ አለ ፡ የምነግርህ፡አትሂድ፡ጠብቀኝ ፣ (ወደቤት'ግባች) »

#ሮሜዎ : (ብቻውን) "
የዛሬው ፡ ደስታ ፡ ምንኛ ፡ ደነቀኝ ።
ሕልም ፡ ነው ፡ ራእይ፡ ወይስ ' ደግሞ ቅዠት አልችልም ፡ ይህ ፡ ነገር ፡ ከቶ'ልደርስበት ፤
ፀሓዬ ፡ ጠለቀች ፡ ገባች ፡ ወደ ፡ ቤቷ ።
አሁን ፡ ተመልሳ ፡ ዳግም ፡ በመስኮቷ ፡
ብቅ ፡ እስክትል ፡ ድረስ ፡ ሆነብኝ ፡ ጨለማ ፡
ይኸው ፡ ተመለሰ ፡ የብርሃኗ ፡ ግርማ ።

#ዡልዬት ፡(ተመልሳ • መጣች
ሮሜዎ ፡ ልንገርህ ፡ የመጨረሻ ፡ ቃል ፤
እንደምታፈቅረኝ ፡ ዐወቅሁት ፡ ይበቃል ፡
ዳሩ ፡ ግን ፡ ፍቅራችን ፡ መሠረት ፡ አግኝቶ
በተክሊል ፡ ጋብቻ ፡ እንዲፈጸም ፡ ጸንቶ ፡
ትፈቅድ ፡ እንደ ፡ ሆነ ፡ እልካለሁና ፥
ነገ ፡ ሰው ፡ ወዳንተ ፡ ጒዳዩን ፡ ካጠናህ ፡
ካሰበ ፡ በኋላ ፡ መንፈስህ ፡ መርምሮ ፡
የተክሊሉ ፡ ሰዓት ፡ ይሁን ፡ በቀጠር ።
ወስነህ ፡ ላክብኝ ፤ ከዚያ ፡ በኋላ ፡ ግን ፡
ማመንታት ፡ ሳይኖረው ፡ ልቤ ፡ ሳይገነግን
ችግር ፡ ሳያግደኝ ፡ አደጋና ፡ ሞትም ፡
አንተን ፡ ተከትዬ ፡ እሄዳለሁ ፡ የትም ።
ነገር ግን ፡ ያንተ ፡አሳብ ከሌለው ፡ ንጽሕና
የማይሄድ ፡ ከሆነ ፡ እንደኔ ፡ ኅሊና ፡
አትምጣ፡ ወደኔ ፡ አትድከም ፡ በከንቱ
እንግዴህ ፡ ደኅና ፡ ሁን ፡ አለፈ ፡ ሰዓቱ '
ግባ ፡ ወደ ፡ ቤትህ ፡ ፍጠን ፡ አታመንታ ፤
ሊነጋ ፡ ነውና ፡ ይታያል ፡ ወገግታ ፡
ጨለማ ፡ ለቀቀ ፡ ብርሃን ፡ ተከፈተ ፡
ስንት ፡ ሰዓት ፡ ሲሆን ፡ ሰው ፡ ልላክ ፡ ወዳንተ ?

#ሮሜዎ
ሦስት ፡ ሰዓት ሲሆን መልክተኛሽ ፡ ይምጣ

#ዡልዬት
እንግዴህ ፡ ደኅና ፡ ሁን ፡ ፀሓይ ፡ ሳትወጣ
እንግባ ፡ ቤታችን ። (ሄደች)•

#ሮሜዎ
ዡልዬት ፡ ደኅና ፡ ሁኝ፤
ልቤ ፡ ካንቺ ፡ ጋራ ፡ መቅረቱን ፡ እመኝ ። (ሄዴ) •

#ሮሜዎና #ኣባ_ሎራ ፡ (ባባ ' ሎራ' ቤት)

#ሮሜዎ
እንደምን ፡ አድረዋል፡ አባቴ ፡ አባ ፡ ሎራ ?

#አባ_ሎራ
ከምሥራቅ ፡ ሳይታይ ፡ የፀሓይዋ ፡ ሥራ ፡
ማነህ ፡ በማለዳ ፡ የመጣህ ፡ ከቤቴ ?
በጣፋጩ ፡ ድምፅህ ፡ የምትል ፡ አባቴ ።
እረግ ! አንተ ፡ ነህ ፡ ወይ ፡ሮሜዎ ፡ ጐበዙ
ዐይኔ ፡ ደከመና ፡ አላየም ፡ በብዙ ፡
እንደ ፡ ምን ፡ አድረሃል ፡ የምወድህ ፡ ልጄ
ዐይንህ፡በጣም፡ቀልቷል፡ምን ነካህ ወዳጄ ?
አንድ ፡ ሰው ፡ እንደዚህ ፡ በጧት ፡ የሚነሣ
ነገር ፡ ሲያገኘው ፡ ነው ፡ እንቅልፍ ፡ የሚነሳ ፡
አሳብ ፡ የምንለው ፡ የሰላም ፡ መጋኛ ፡
መንፈሱን ፡ ሰፍሮበት ፡ እንቅልፍ ፡ የማይተኛ ፡
ሽማግሌ ፡ ሰው ፡ ነው ፤ ወጣት ፡ ግን ፡ በውኑ ፡
ከእንግዲህ ፡ ያለ ፡ ነገር ፡ ነጻ ፡ በመሆኑ ፡
ተኝቶ ፡ ያነጋል ፡ እንቅልፉን ፡ በሰላም ፤
ስለዚህ ፡ ይህ ፡ ዐይንህ ፡ በደኅናው ፡ አልቀላም ፡
ሮሜዎ ፡ ምን ፡ ሆኖ ፡ ሳይተኛ ፡ ያደረ ?
አለመተኛቱን ፡ ዐይኑ ፡ መሰከረ ።

#ሮሜዎ
እውነት ፡ ነው ፡ ነገር ፡ ግን ፡አርፌያለሁ ፡ በጣም

#አባ_ሎራ
ብታርፍማ ፡ ኖሮ ፡ በሌሊት ፡ አትመጣም ፡
ንገረኝ ፡ አትደብቅ ፡ ወዴት ፡ ነው ፡ ያደርከው ?

#ሮሜዎ
ድል ፡ አድራጊው : ፍቅሯ ፡ መንፈሴን ፡ ማረከው
አባቴ ፡ እጅዎ ፡ ተክሊሌን ፡ ይባርከው ።

#አባ_ሎራ
ያሰብከውን ፡ ነገር ፡ ንገረኝ ፡ አትፍራ ፤
ከመልካሟ ፡ እጮኛህ ፡ ከሮዛሊን ፡ ጋራ ፡
የተክሊል ፡ ቃል ፡ ኪዳን ፡ ዛሬ ፡ ልትሞላ ፡
የመጣህ ፡ መሰለኝ ፡ ሳስበው ፡ በመላ ።

#ሮሜዎ
ሮዛሊን ፡ ቀርታለች ፡ አያንሷት ፡ አባቴ ፡
ትናንትና ፡ ማታ ፡ ተመታ ፡ ደረቴ ፡
ባዲስ ፡ የፍቅር ፡ ጦር ፡ በሰላ ፡ ጐራዴ ፤
ከመውደዷ ፡ ጋራ ፡ ገጠመ ፡ መውደዴ፡
ስሜታችን ፡ እኩል ፡ ፍቅራችን ፡ የጋራ ፡
ሆኖ ፡ ከተገኘ ፡ አባቴ ፡ አባ ፡ ሎራ ፡
ተክሊሉን ፡ ይሙሉልን ፡ በሥልጣንዎ ፡ ባርከው ፡
እኛ ፡ ቂም ፡ የለንም ፤

#አባ_ሎራ
መንፈሴን ፡ ኣወከው
ምን ፡ አመጣህብኝ ፡ የማላውቀው ፡ ምስጢር ፥
መላ ፡ መትቶ ፡ ያውቃል ፡ ብለህ ፡ አትጠርጥር ፤
አልገባኝምና ፡ ያሁኑ ፡ ንግግር ።
ይህን ፡ እንቆቅልሽ ፡ እንደ ፡ ሾላ ፡ ድፍን ፡
ትተህ ፡ ፡ ግለጥልኝ ፡ ነገሩን ፡ ሳትሸፍን ።

#ሮሜዎ
አባቴ ፡ አልደብቅም ፡ ሁሉንም ፡ ገልጬ ፡
ለርስዎ ፡ ልነግር፡ ነው ፡ የመጣ ፡ ሮጬ፡
የነካፑሌን ፡ ልጅ ዡለየትን ፡ ወድጄ ፤
ራሴ ፡ እስቲጠፋ ፡ በፍቅር አብጄ ፡
እሷም ፡ በጣም ወዳኝ፡አድርገን ፡ መሐላ ፡
ተስማምተን ተዋደን ከቈረጥ ኋላ ፡
አሁን 'የሚቀረን'ተክሊል ፡ የሚሞላ ፡
ካህን ፡ ስለ ፡ ሆነ የሚሰጥ፡ ቡራኬ ፡
ከሷ ጋር ፡ መጥቼ ፈትዎ' ተንበርክኬ ፡
ሞልተው 'ያሰናብቱን የተክሊሉን ፡ ሥርዐት
ሰዓቱን 'ይንገሩኝ መቼ እንደምጠራት ።

#አባ_ሎራ
አይጣል፡ነው፡እናንተ፡ የወጣቶች ፡ ወረት፤
ፍቅራቸው ፡ ቃላቸው ፡ የለውም መሠረት፡
የቀድሞ ፡ እጮኛህ ፡ ሮዛሊን 'ተረስታ፡
ሌላ ፡ ልጅ ፡ አግኝተህ አሁን ትናንት ፡ ማታ
እንዴት ተለወጠ፡ ኣሳብህ ፡ ባንድ ፡ አፍታ፡
በሮዛሊን ፡ ፍቅር ፡ ልብህ ፡ እንዲያ፡ግሎ ፡
ዘላለም ፡ የማይበርድ፡እውነተኛ፡መስሎ ፡
ታጫውተኝ ፡ ነበር አሁን ፡ ይኸውና ፡
ያ ፡ ሁሉ ፡ መውደድህ 'ከመቼው 'ቀረና ፡
መጣህ ' ባዲስ ፡ ፍቅር ፡ ልብህ ፡ ተብረክርኮ ፡
ለምታያት፡ሁሉ፡መንፈስህ ፡ ተማርኮ፡

💫ይቀጥላል💫
👍1
#ሮሜዎና_ዡልዬት

#ክፍል_አምስት

ከተሸንፍክማ ' በጕንጮቿ ፡ ቅላት '
በወገቧ ቅጥነት፡ በደረቷ፡ ሙላት'
አበድኩ ፡ ካልክማ፡ ለጥርሶቿ 'ንጣት '
ለባቷ፡ አቀራረጽ ለጠጕርዋ ፡ቀለም ፡
ፍቅርህ ፡ ባይንህ ፡ ላይ ፡ነው፤ በልብህ ፡ አይደለም ይቅር በለኝ፡ልጄ፡ ባሁኑ ፡ ወቀሣ
ለዚች ፡ ከንፈህላት፡ ያችን ' ስትረሳ ፡
አመዛዘንኩና' ሠጋሁ፡ ኣስተውዬ '
ይችንም ፡ እንደዚያች' ትረሳለህ ፡ ብዬ ።

#ሮሜዎ
አባቴ ፡ በፍጹም ፡ ይህን ፡ አይጠርጥሩ፤
የዚችና ፡ የዚያች ፡ ልዩ ፡ ነው ፡ ነገሩ
በምን ፡ ቃል ፡ ልናገር ፡ ይህን ፡ ለማሳመን
በግሪክ ፡ በሮማ ፡ በጥንታዊው ፡ ዘመን ፡
ያነቡ፡ እንደ'ነበር' የእንስሳውን ፡ ሞራ ፡
ይችሉ ፡ እንደ ፡ ሆነ ፡ አባቴ ፡ አባ፡ ሎራ '
እርስዎም ፡ እንደዚሁ፡ የልቤን ፡ ብራና፡
በጥበብ ፡ አውጥተው ፡ገልጠው፡ያንቡና '
የወረት ፡ ምልክት ፡ ቢያገኙ፡ በውስጡ '
ያን ፡ ጊዜ 'ይገባል ፡ ቢንቁኝ ፡ ቢቈጡ ።

#አባ_ሎራ
መልካም ነው አመንኩህ ፡ግን ከዚህ ፡ በኋላ
አንድ ፡ ነገር ፡ አለ ፡ የሚያስቸግር ፡ ሌላ ፤
ካፑሌና ፡ ሞንታግ ፡ የናንተ ፡ አባቶች ፡ .
ወገኖቻቸውን ፡ ጨምረው ፡ ጠላቶች ፡
ባላንጦች ፡ ቂመኞች ፡ ደመኞች ፡ ሲሆኑ ፤
በየመንገዱ ፡ ላይ ፡ እንዳውሬ ፡ እያደኑ ፡
አንዱ ፡ አንዱን ፡ ሲገድለው ፡ ባይኑ ፡ ሲያየው፡ብቻ
እንዴት ፡ ሊፈጸም ፡ ነው ፡ የናንተ ፡ ጋብቻ ? .
ይኖሩ ፡ የለም ፡ ወይ ፡ ዘወትር ፡ በዘመቻ ፡
ዘለዓለም ፡ ለውጊያ ፡ ለጠብ ፡ ተሰልፈው ፡
ለቄስ ፡ ላስታራቂ ፡ ለዳኛ ፡ አሸንፈው ።

#ሮሜዎ
ይኸው፡አባቴ ሆይ ይህ ነው፡ ዋናው ነገር
በዚህ ፡ ላይ ፡ ይገባል ፡ በብዙ ፡ መማከር ፡
እውነት፡ ነው ፡ ቢኖሩ፡ ዘለዓለም ፡እነሱ፡
በጠብ ፡ ባምባጓሮ ፡ ደም ፡ እያፈሰሱ ፡
ለፍርድ ፡ ቢያስቸግሩ የቄስ ፡ ቃል ፡ ባይሰሙ ፡
እኔና ፡ ዡልዬት ፡ ግን ፡ንጹሕ ፡ ነን ፡ ከቂሙ፡
አለ ፡ ወይ ፡ አባቴ ፡ በሃይማኖት ፡ መንገድ
የሚከለክል ፡ ሕግ ፡ እኛ ፡ እንዳንዋደድ ፡
እንግዲህ ፡ አባቴ ፡ ይህንን ፡ ካወቁ ፡
ዘዴውን ፡ ለማግኘት ፡ እርስዎም ፡ ይጨነቁ ፡ቤተ ሰቦቻችን ወሬውን ፡ ሳይሰሙ
ተክሊሉን ፡ በምስጢር ፡ እርስዎ፡ ይፈጽሙ ።

#አባ_ሎራ
ይህንን ፡ ታልህማ ፡ ዘዴ ፡ ጠፍቶ ፡ ለርቁ ፡
ካህንም ፡ አልቀረም ፡ አብሮ ፡ መጨነቁ ፡
ለሁለቱ ፡ ወገን ፡ ሰላምን ፡ መልሶ ፡
ያባቶቻችሁን ፡ ክፉ ፡ ቂም ፡ ደምስሶ ፡
ስለታቸው ፡ ዘወትር ፡ የሰው ፡ ደም ፡ ከማፍሰስ ፡
እንዲቆም ፡ ለማድረግ ፡ ትንሽ ፡ እንዲታገሥ ፡
ለሻምላ ፥ ለጩቤ ፥ ለሰይፍ ፡ ለጐራዴ ፡
ከዚህ ፡ የተሻለ ፡ መች ፡ ይገኛል ፡ ዘዴ ።
የናንተ ፡ ጋብቻ ፡ ይህን ፡ ቂም ፡ አብርዶ ፤
ዕርቅ ፡ ይመሠረታል ፡ ሰላምን ፡ አውርዶ ።

#ሮሜዎ
እንግዴህ፡ አባቴ ፡ እንፍጠን ፡ በቶሎ ፡
ተክሊሉ ፡ ይፈጸም ፡ በዛሬ ፡ቀን ፡ ውሎ ፡
ጊዜና ሰዓቱን ፡ ካልተሻማን ፡ በጣም :
እንዲህ ፡ ያለ ፡ ፍቅር ፡ ዕንቅፋት ፡ አያጣም

#አባ_ሎራ
እንግዲያው ፡ መልካም ፡ ነው ፡ ኑና ፡ ባሥር ፡ ሰዓት፡
ትፈጽማላችሁ ጋብቻችሁን በስራት

#የዡዬየት_ሞግዚትና #ሮሚዎ

#ሞግዚት
መልሱን ፡ ተቀብለሽ ፡ እንድትመጪ ' ብላ
ልካኝ' እመቤቴ ፡ በቶሎ ፡ አስቸኵላ '
ይኸው ፡ መጥቻለሁ፡ መልሱን ፡ ለመቀበል ፤
ቸኩያለሁና ፡ ንገረኝ፡ ቶሎ ፡ በል ።

#ሮሜዎ
ምላሴ 'ያሞግስ ፡ አፌም ፡ ያመስግናት ፤
በውነት' ያንቺ ፡ እመቤት ፡ የተባረከች ፡ ናት
ዐመሏ ' ጠባይዋ ፡ በለጠ ' ከመልኳ፤
ቃሏን ፡ ፈጸመችው ፡ አንቺን ፡ በመላኳ
ዥሮቼ ፡ ተከፍተው 'እሰማለሁና፡
እንግዴህ ፡ ንገሪኝ የዡልዬትን ፡ ዜና ።

#ሞግዚት
ለተነጋገርነው ፡ ትናንትና ፡ ማታ ፡
እንድትልክብኝ' ያሳብህን ፡ ሁኔታ ፡
በመጠበቅ ፡ ላይ ፡ ነኝ ፡ አስታውቀኝ ፡ በቶሎ ፤
በዪና፡ ንገሪው ፤እንደዚህ ፡ ነው፡ ብሎ ፡
አሳቡን ፡ ሲነግርሽ ፡ ተቀብለሽ ፡ አምጪ፡
ብላኝ ' መጥቻለሁ ።

#ሮሜዎ
መልሴን ፡ ስትሰጪ '
እንግዲያው ፡ ንገሪያት ፡ ሮሜዎ ፡ ከልቡ ፡
ይወድሻል ፡ ብለሽ ፡ መንፈሱም ፡ አሳቡ ፡
ወዳንቺ ፡ ነው ፡ በያት ፡ ንገሪያት ፡ አደራ ፤
እስቲ ፡ ልለምንሽ ፡ እባክሽ ፡ ሳልፈራ ፡
እኔ ፡ እንደምወዳት፡ እንደዚሁም ፡ እሷ'
ትወደኝ ፡ እንደሆን ፡ ዡልዬት፡ በመንፈሷ፡
ታውቂዋለሽና ፡ እባክሽ ፡ ንገሪኝ ፡
አሳቧን ፡ ጠባይዋን 'እንዳውቀው ፡
ምከሪኝ ።

#ሞግዚት
ምንም ፡ አልደብቅህ ፡ ልንገርህ ፡ ካንዠቴ
አንተን ፡ ስታፈቅር ፡ ዝልዬት ፡ እመቤቴ'
እመነኝ ፡ ልንገርህ ፡ በውነት ፡ ከልቧ' ነው
የመስፍኑ ዘመድ፡ፓሪስ የሚባለው፡
ሊያገባት፡ ፈልጎ ፡ መሞቱ ፡ ነው ፡ ደክሞ ፡
ጨርሳ ፡ አትወደውም፡ እሷ ፡ ግን ፡ ፈጽሞ
አታንሡ፡ትላለች ፡ የሱን ፡ ስም ፡ ከፊቴ ፤
ትቈጣለችና ፡ ስቈይ ፡ እመቤቴ ፡
ልመለስ ፡ እባክህ ፡ መልሱን ፡ ስጠኝና ፤

#ሮሜዎ
አቀርብልሻለሁ'በሰፊው ፡ ምስጋና ።
እንደዚህ ' በዪና ፡ መልሱንም ፡ ንገሪያት ፤
ከቀትር ፡ በኋላ ፡ ዛሬ ፡ ባሥር ፡ ሰዓት ፡
አባ 'ሎራ፡ ድረስ ፡ አስፈቅዳ ፡ ትምጣ፤
ተናዘን ፡ ተባርከን ፡ የተክሊሉን ፡ጣጣ፡
ደብቀው ፡ በሙሉ ፡ ሊፈጽሙ፡ ቄሱ ፡
ተስማምተናል ፡ በያት ፡ ዛሬ ፡ ሊጨርሱ ።

#አባ_ሎራ #ዡልዬት #ሮሜዎ

#አባ_ሎራ
የናንተ ፡ ጋብቻ ፡ ፍጻሜው ፡ እንዲያምር ፡
ፈጣሪ ፡ ጸጋውን ፡ ምሕረቱን ፡ ይጨምር ።

#ሮሜዎ
አሳቤ ' ሞላልኝ ፡ እንግዲህ ፡ አባቴ ፡
ይህ ፡ ብቻ፡ ነበረ ፡ የቀረኝ ፡ ምኞቴ ።
ከሷ'ጋራ ፡ መጥቼ ፡ ቀርበን ፡ ከመንበሩ፡
ሥራቱን ፡ ከሞላን ፡ አለቀ ፡ ነገሩ ፡
እንግዲህ ፡ ግድ ፡ የለም የመጣ ፡ ቢመጣ

#አባ_ሎራ
ልጄ ፡ ሆይ ፡ ብዙ ነው የዚህ ዓለም ፡ ጣጣ
ለደስታ ፡ ሐዘን ፡ ለማር ፡ አለው ፡ እሬት ፤
ጠፊ ፡ ካጥፊው ፡ ጋራ ፡ ይኖራል ፡ በመሬት
ስለዚህ ፡እግዚአብሔር መጥፎውን ፡ አርቆ
ልጄ ፡ ያኑራችሁ ፡ በሰላም ፡ ጠብቆ ።

(ዡልዩት ፡ መጣች) ።

ፍቅሯንና ፡ ጌጧን ፡ በልቧ ፡ ሸፍና ፡
አልማዟ ፡ ማስተዋል ፡ ወርቋ ፡ ትሕትና ፡
ምስጢሯን ፡ ባሳቧ ፡ በጥበብ ፡ ሰውራ ፡
ይኸው ፡ መጣችልን ፡ መልካሟ ፡ ሙሽራ

#ዡልዬት
ሰላም ፡ ለርስዎ ፡ ይሁን ፡ ኣባቴ ፡ አባ ሎራ

#አባ_ሎራ
ደኅና ፡ ነሽ ወይ? ልጄ። ወጣት ፡ ሴት ፡ ወይዘሮ ፤
መልካም ፡ ጊዜ ፡ መጣሽ ፡ ልክ ፡ በቀጠሮ

#ዡልዬት
አመሰግናለሁ ፡ ለኔም ፡ ለሮሜዎ ፡
አባቴ ፡ ስለ ፡ እኛ ፡ በመቸገርዎ ።

#ሮሜዎ
እንዳንቺ ፡ እንደ ፡ እኔ ፡ በፍቅር ፡ ተሳስረው
ለመጡ ፡ ወጣቶች ፡ ሥራቱን ፡ አክብረው
ፍቅራቸውን ፡ ባርኮ ፡ በእጁ ፡ ሊቀድሰው ፡
ምን ፡ ጊዜም ፡ ሥራው ፡ ነው ፡ ካህን ፡ የሆነ ፡ሰው።

#አባ_ሎራ
እጆቹን ፡ ዘርግቶ ፡ ካህን ፡ ይጠብቃል ፤
እውነት ፡ ነው ፡ ሮሜዎ ፡ የተናገረው ፡ ቃል'
ከቤተ ፡ ክርስቲያን ፡ እንግባና ፡ በሉ ፡
ሳይዘገይ ፡ በቶሎ ፡ ይፈጸም ፡ ተክሊሉ ።

(ቤተ ፡ ክርስቲያን'ገቡ)

(#በቬሮና #ከተማ' #መንገድ) •

#ሜርኩቲዎ #ቤንቮሊዎ ፡ አንድ ፡ የእልፍኝ #አሽከር

#ቤንቮሊዎ
ሜርኩቲዎ ፡ እንሂድ ፡ የካፑሌ ፡ ሰዎች ፡
ይጠፉ ፡ አይመስለኝም በነዚህ መንደሮች
ድንገት ፡ ብንገናኝ ፡ ኋላ ፡ ጠብ ፡ ይነሣል ፤
ደግሞ ፡ ጠብ ሲነሣ ፡ ጸጥታ ፡ ይፈርሳል ፡
ብንሸሽ ፡ ይሻላል ፡ ከዚህ ፡ ሁሉ ፡ ጣጣ ።

#ሜርኩቲዎ
እነሱም ፡ አስበው ፡
👍1
#ሮሜዎና_ዡልዬት


#ክፍል_ስድስት


አሁንም ፡ ፡ ይሻላል ፡ ብታየው ፡ አስተውለህ ፤

የደረቀ፡ደም፡ነው፡ዝገት፡የመሰለህ

#ቲባልት
ኧረግ ፡ እንዲህ ፡ነው ፡ ወይ ! የበግ ፡ ነው ፡ የዶሮ ?

#ቤንቮሊዎ
ፈሶ : የተገኘ ፡ ካንገቱ ፡ ጕረሮ ፡
የወገንህ ፡ ደም ፡ ነው ፡ ከበግ ፡ የማይሻል

#ቲባልት
በመሳደብ ፡ ብቻ ፡ ጊዜያችን ፡ ይመሻል ፡
እንግዲህ፡ ይቀጥል ፡ የወንዶቹ ፡ ሥራ ።
(#ሻምላ#መዘዘ)።

#ሜርኩቲዎ
ዘወትር፡ዝግጁ፡ነኝ፡ማንንም፡አልፈራ፤(#ሜርኩቲዎም #መዘዘ)
(ሮሜዎ ፡ መጣ) ።

#ቲባልት
ከናንተ ፡ ኣልዋጋም ፡ መጣ ፡ የኔ ፡ እኩያ ፤
ስማኝ ፡ ሮሜዎ ፡ ወጥቼ ፡ ገበያ ፡
አቃተኝ ፡ ለማግኘት ፡ ፈልጌ ፡ ክፉኛ ፡
አንተን ፡ የመሰለ ፡ የወንድ ፡ መናኛ ።

#ሮሜዎ
ተፍቋል ፡ ጨርሶ ፡ ቂም ፡ በቀል ፡ ከልቤ ፤
በመጥፎ ፡ ንግግር ፡ ሮሜዎን ፡ ሰድቤ ፡
ላስቈጣው ፡ በማለት ፡ ቂሙን ፡ ልቁስቀሰው ፡ ማለት በከንቱ ፡ ይደክማል ፡ የተጣጣረ ፡ ሰው' .
የፍቅሬ ፡ ምክንያት ፡ ሆኗልና ፡ ብርቱ ፡
ቲባልት ፡ የኔ ፡ ወዳጅ ፡ አትድከም ፡ በከንቱ

#ቲባልት
ኀይለኛው ፡ ቂማችን ፡ ያከማቸው ፡ ዕዳ ፡
መች ፡ እንዲህ 'ይፋቃል ፡ ይልቅ ፡ ተሰናዳ

#ሮሜዎ
ቲባልት ፡ ስማኝ ፡ እኔ ፡ ንጹሕ ፡ ነኝ፡ ከቂሙ
ካፑሌ ፡ የሚሉት ፡ የዘራችሁ ፡ ስሙ ፡
እንደ ማር፡ ጣፋጭ ነው፡አይመረኝም ለኔ
ጠባችሁ ፡ ብቻ ፡ ነው ፡ በውነቱ ፡ ሐዘኔ ።
የፍቅሬን ፡ ምክንያት ፡ ሳታውቀው ፡ መርምረህ ፤
አትድከም ፡ በከንቱ ፡ ክፉ ቃል ፡ተናግረህ፡
ቲባልት ፡ እኔና ፡ አንተ መቼም : አንጣላም
ደኅና ፡ ዋል ፡ ወዳጄ ፡ እንሂድ ፡ በሰላም ፡
ደግሞም ፡ ከዚህ በቀር ፡ የሕጉን ፡ ወቀሣ
የመስፍኑን ፡ ዐዋጅ ፡ ልብህ ፡ እንዳይረሳ ።

#ሜርኩቲዎ
ዦሮዬ ፡ አይሰማም እንዲህ ፡ ያለ ፡ ፍራት
ቲባልት ፡ እይ ፡ ሻምላዬ ፡ ሲያበራ ፡ እንደ ፡ መብራት ። (መዘዘ)።
ተመልሶ ፡ እንግዴህ ፡ ኣይገባም ፡ ካፎቱ ፡
በደም ፡ ካልታጠበ ፡ የዛገው ፡ ስለቱ ።
(አቲባልት'ጋራ ውጊያ'ገጠሙ)•

#ሮሜዎ
ፍጠን ፡ ቤንቮሊዎ ፡ እንገላግላቸው ፤
ሁለቱም አይረቡ በውነት እብዶች ፡ ናቸው
ቲባልት ! ሜርኩቲዎ ! አስቡት ፥ አትርሱ ፤
ልዑል ፡ በቀደም ፡ ለት ፡ ደም ፡ እንዳታፈሱ
ብለው ፡ የሰጡትን ፡ ዐዋጁን ፡ አስታውሱ
(ገላገላቸወ፡ ቲባልት' ከወገኖቹ'ጋራ'ሄደ)

#ሜርኩቲዎ
ቈስያለሁ ፡ እኮ ፡ በቃ ፡ የኔ ፡ ነገር ፤
ተበላሸሁ ፡ እኔ ፡ ወይ ፡ አለመመከር ።
ቤንቮሊዎ ፡(ቁስሉን'ያያል)"
ለካ ፡ ቁስለሃል ፡ ወይ ? አላየሁም ፡ እኮ !

#ሜርኩቲዎ
ሐኪም ፡ ይጠራልኝ ፡ አንድ ፡ ሰው ፡ ተልኮ
(የልፍኝ' አሽከር መሄዴ) "

#ቤንቮሊዎ
አይዞህ ፡ የኔ ፡ ወንድም፡ ትንሽ ፡ ነው ፡ቍስሉ ፤

#ሜርኩቲዎ
ምንም ፡ ትንሽ ፡ ቢሆን ፡ አይቀርም ፡ መግደሉ'ካፑሌና ፡ ሞንታግ ፡ ትውልዳቸው ፡ ይጥፋ፤
በነሱ፡ ምክንያት ፡ ስንት ፡ ሰው ፡ ተደፋ፡
በምን ፡ ኀጢአታችን ፡ እንሞታለን ፡ እኛ ፡
ለማይረባ፡ ነገር ፡ ተሳድቦ ፡ እንደ እረኛ ፡
በሰው፡እጅ፡ መሞት ፡ በሆነ ፡ ባልሆነው '
ከንቱ ፡ ሞት ይሉሃል ፡ እንደዚህ ፡ ያለ ነው
ተመቸውና ፡ ነው ፡ ይኸ ፡ ፈሪ፡ መጥፎ ፡
በሮሜዎ ፡ እጅ ፡ ሥር ፡ ታቹን ፡ አሳልፎ ፡
በድንገት ፡ የወጋኝ ፡ በቃ ፡ የኔ ፡ ነገር ፤
ባትገላግሉኝ ፡ አይነካኝም ፡ ነበር ።
(ሜርኩቲዎን'ቤንሾሊዎ 'ደግፎት ፡ አብረው ሄዱ)”

#ሮሜዎ ፡ (ወቻውን)
ወዳጄ ፡ ሜርኩቲዎ ፡ የመስፍኑ፡ ዘመድ ፡
አባቴን ፡ ወገኔን ፡ እኔንም ፡ በመውደድ
እንሆ ፡ቈሰለ ፡ ለኛ ፡ ሲል ፡ ተጣልቶ ፤
ቲባልት ፡ አዋረደኝ ፡ ከመሬት' ተነሥቶ
ዡልዬትን • ወድጄ ፡ ፍቅር ፡ መፈለጌ ፡
ስድቡንም ፡ ሸሽቼ ፡ ከጠብ ፡ ማፈግፈጌ፡
ወደ 'መለማመጥ ወገኖቼን ' መሪ
ወንድነት 'ያነሰኝ'አስመሰለኝ ' ፈሪ ።
(ቤንቮሊዎ መጣ)

#ቤንቮሊዎ
አልቅስ ፡ሮሜዎ ' እንባህን 'አፍስሰው
ሜርኩቲዎ ፡ ሞተ፡ መልካሙ 'ደጉ' ሰው ።
መልካሙ ፡ ወዳጄ ፡ ሜርኩቲዎ ' ከሞተ '
እንግዴህ ፡ መታረቅ ፡ ሰላም ፡ ተከተተ ፥
ጠባችን ፡ ነደደ ፡ በሉ ፡ የተነሣ ፤
ወደ ፡ ፊት ፡ ይወድቃል ፡ ገና ፡ ብዙ ፡ ሬሳ
(ቲባልት' ተመልሶ ፡ መጣ)

#ቤንቮሊዎ
ቲባልት ፡ ይኸ ሰይጣን መጥፎ ፡ ጥጋበኛ
እየው ተመልሶ ፡ ሲመጣ ፡ ወደ ፡ እኛ ።

#ሮሜዎ ፡ ለብቻው' ይናገራል) "
ወይ ፡ ጥሎኝ ወይ ፡ ጥዬው አንጀቴን ላርሰው ፤
ቆይ ፡ ይምጣ ፡ ግድ ፡ የለም ፡ ደም ፡ ነው፡ የመለሰው።
ዡልዬት ፡ ደግነቷ ፡ ፍቅሯ ፡ ሰላም ፡ ሆኖ ፡
ይዞህ ፡ የነበርከው ፡ በትዕግሥት ፡ ሸፍኖ ፡
በልቤ ፡ ያለኸው ፡ የቂሜ ፡ ትኵሳት ፡
ለብልበኝ ፥ ጠበሰኝ ፡ አቃጥለኝ ፡ እንደ ፡ እሳት ።
(ለቲባልት • ይናገራል) "
ቲባልት ፡ በል ስደበኝ፡ አሁን እንደ ቅድም
የሜርኩቲዎ ፡ ነፍስ ፡ ብቻዋን ፡ አትሄድም
ወይ ፡ እኔን ፡ ወይ ፡ አንተን ፡ አንዱን ፡ ሳያስተክትል፤
ሻሞላህን ፡ ምዘዘው ፡ ዛሬ ፡ ነገ ፡ ሳትል ፡
የምትሻው ፡ ቂሜ ፡ የነደደ ፡ ይሁን ።

#ቲባልት ። ..
አንተም፡ ከሱ ፡ ጋራ ፡ ትሞታለህ ፡አሁን ።
(ይዋጉና'ቲባልት 'ይወድቃል )

#ቤንቮሊዎ
ሮሜዎ ፡ አትቁም ፡ ቶሎ ፡ ከዚህ ፡ ጥፋ ፤
ቲባልት ፡ ከሞተ ፡ ምንም ፡ የለህ ፡ ተስፋ፡
መስፍኑ ፡ ሲያገኝህ ይህን ፡ነገር ፡ ሰምቶት
ዕወቅ ፡ አይምርህም ፡ ይቀጣሃል ፡ በሞት
(ሮሜዎ 'ሸሸ ፡ ሰዎች፡ መጡ)

#ወታደር
እንዴህ ፡ ያለ ነገር ዘለዓለም ፡ የማይበርድ
ነጋ ፡ ጠባ ፡ ሬሳ ፡ በየዋናው ፡ መንገድ ፡
ጠብ መሆኑን፡ሰምተው ይኸው፡ልዑል መጡ፤
ማነው ፡ የገደለው ? አሁን ፡ በቶሎ ፡ አውጡ ።

#መስፍን
አወይ ፡ ዘመዴ ፡ ሆይ፡ ሜርኩቲዎ ፡ ሞተ፤
ማነው ፡ ጠብ ፡ ሲጀመር 'የተመለከተ?

#ቤንቮሊዎ
ልዑል ሆይ፡እኔ ነኝ'ያየሁ፡ሁሉንም ፡ ነገር !
ፈቃድዎ ፡ ቢሆን' ፈጥኝ፡ ልናገር ።

#መስፍን
ንገረኝ ፡ ሁሉንም ፡ ከምንጩ ፡ ጀምሮ፤

💫ይቀጥላል💫
#ሮሜዎና_ዡልዬት


#ክፍል_ስምንት


#ሞግዚት
የተሠራውን ፡ ጉድ ፡ እንግዲህ ፡ ዕወቂው
እርገሚው ፡ ሮሜዎን ፡ ከልብሽም ፡ ናቂው
በቀልሽን ፡ ቂምሽን ፡ አድርጊው ፡ የጸና ፤
በውነቱ ፡ ሮሜዎ ፡ ሰው ፡ አይደለምና ።
አብነት ፡ ይሁንሽ ፡ ይህ ፡ መጥፎ ፡ ደመኛ
ሰውን ፡ አትመኝ ፡ እንግዲህ ፡ ዳግመኛ ፡
ፍቅሩም ፡ደግነቱም ፍሬ ቢስ ፡ ነው ፡ ከንቱ
ፈጽሞ ፡ ሰው ፡ የለም መጥፎ ፡ነው ፡ ሰዓቱ
እንዲህ ፡ ያለ ፡ ነገር ፡ ሮሜዎ ፡ ሲሠራ ፡
ማነው ፡ የሚታመን ? ማነው ፡ ባለአደራ ?

#ዡልዬት
ምንም ፡ አልተገኘ ፡ የሚበጀኝ ፡ ለኔ ፤
ሁለት ፡ ስለት ፡ ያለው ፡ ሰይፍ ፡ ነው ፡ ኀዘኔ
ቲባልት ፡ ባይሞት ኖሮ ሮሜዎ ፡ ይሞታል፤
ቲባልት ፡ ባይሸነፍ ፡ ሮሜዎ ፡ ይረታል!
ሮሜዎን ፡ ከልብሽ ፡ ትይኛለሽ ፡ ጥዪው ፤
ምነው ልቤን ገብተሽ መርምረሽ ብታዪው
ለኔም ፡ገዳይ ፡ ቢሆን ፡ ለናቴም ፡ ላባቴ ፡
ሮሜዎን ፡ ለመጥላት አይችልም ፡አንጀቴ
ቲባልትም ፡መጥፎ ነህ ፡ሮሜዎም አትረባ
መሪር ፡ ነው ፡ ከናንተ ፡ የሚተርፈኝ ፡ እንባ
ባሌ ፡ ካገር' ወጣ ፤ቲባልት ፡ ሞተ ፡ በፊት፤
ሐዘኔ ፡ ዐጓጕል ፡ የሌለው ፡ መድኀኒት ፡
እንደ ምን ፡ አድርጌ ደግሞስ ፡ እስከ መቼ
እኖራለሁ ፡ እኔ ፡ እናንተን ፡ አጥቼ ፡
ከቲባልት ፡ መሞት ፡ ሮሜዎ ፡ ስደቱ ፡
ከሮሜዎ ፡ ስደት ፡ ቲባልት ፡ መሞቱ ፡
ቢሆን ፡ ምን ፡ ቸግረው ፡ ሐዘኔ ፡ በተራ ፤
ለማንኛው ፡ ላልቅስ ፡ ወይ ፡ የኔ ፡ መከራ !
ዛሬ ፡ በሠርጌ ፡ ቀን ፡ ደስ ፡ብሎኝ ፡ መዋሌ
ቀረና ፡ ሰው ፡ ገድሎ ፡ እንዲሰደድ ፡ ባሌ '
ቲባልትም ፡ እንዲሞት ፡ አድርጎ ፡ ዕድሌ ፡
ሐዘን ፡ ከሆነ ፡ ለኔ ፡ የደገሰው ፡
ልቤ ፡ ሳያደላ ፡ እንባዬን ፡ ላፍስሰው ።

#ሞግዚት
በእውነት፡ሴት ልጅ ባሏን፡ከወደደች አይቀር
እንዳንች ፡ አድርጎ ፡ ነው ከልቡና ማፍቀር
ከልብ ፡ አዘንኩልሽ ፡ በጣሙን ፡ አድርጌ ፤
አለበት ፡ ገብቼ ፡ ሮሜዎን ፡ ፈልጌ ፡ .
እኔ ፡ አመጣዋለሁ ፡ እንባሽን ፡ አድርቂው
እመኝታ ፡ ቤትሽ ፡ ግቢና ፡ ጠብቂው ።
በስደተኛነት ፡ ሳይሄድ ፡ ነገ ፡ ርቆ ፡
ተሰነባበቱ ፡ ይምጣ ፡ ተደብቆ ።

#ዡልዬት
መልካም ፡ ነው ፡ ሞግዚቴ ፡ሙሽራ ፡ ሲገባ
አጊጦ ፡ ታጅቦ ፡ በዘፈን ፡ ባበባ ፡
በወግ ፡ በማዕርግ ፡ ባለም ፡ በደስታ ፡
በክብር ፡ ነበረ ፡ በብዙ ፡ እልልታ ፤
ሌሊት ፡ ጨለማውን ፡ ከለላው ፡ አድርጎ ፡
የኔ ፡ ሙሽራ ፡ ግን ፡ ይግባ ፡ ተሸሽጎ ።
እንቢ ፡ ብሎ ፡ እንዳይቀር ፡ጠርተሽ ፡ ስታመጪው
እንቺ ፡ ለምልክት ፡ቀለበቴን ፡ ስጪው ፡
(ቀለበቷን ፡ ሰጠቻት)

#አባ_ሎራ (ባባ ሎራ ፡ ቤት)
ሮሜዎ ፡ ብቅ ፡ በል ፡ውጣ ፡ ከጨለማ ፤
የፍርዱን ፡ ቃል ፡ ይዤ ፡ መጣሁ ልጄ ስማ

#ሮሜዎ
ሳልሰማው ፡ ቢዘገይ ፡ ይሻለኝ ፡ ነበረ ፤
ፍርዱ ፡ ምን ፡ ዐይነት ነው ? ልቤ ፡ ተሸበረ

#አባ_ሎራ
መስፍኑ ፡ ፈቀደ ፡ በቀላል ፡ ሊቀጣ ፤
የሞት ፡ ፍርድ ፡ ቀርቶ ፡ካገር ፡ እንድትወጣ

#ሮሜዎ
ጨካኝ ፡ ቅጣት ፡ እንጂ ፡ ከሞትም ፡ የከፋ
ይህ ፍርድ መሪር ነው ያስቈርጣል ፡ ተስፋ
ዥልዬት ፡ ካለችበት ፡ ከተማ ፡ ወጥቼ ፡
ስደተኛ ፡ ሆኜ ፡ አገሬንም ፡ ትቼ ፡
የምኖረው ፡ ኑሮ ፡ እንደ ፡ ምን ፡ ይገፋል ፣
ቀኑና ፡ ሰዓቱ ፡ ደቂቃው ፡ መች ፡ ያልፋል ፡
እንዴት ፡ እችላለሁ ፡ ዡልዬትን ፡ ለመርሳት
ሲኦል ፡ ነው ፡ ኵነኔ ፡ ሞት ፡ገሃነመ ፡ እሳት

#አባ_ሎራ
ደስታህ ፡ ቀረና ፡ በማመስገን ፡ ፈንታ ፡
ለምን ፡ ትረሳለህ ፡ የእግዜርን ፡ ውለታ ፡
ዐዋጁ ፡ የሚያዘው ፡ የሞት፡ ቅጣት ፡ ነበር'
ለምን ፡ አታስብም ፡ ይህን ፡ ትልቅ ፡ ነገር ፡
ሄደህ ፡ ብትቀመጥ ፡ በማንቱ ፡ ከተማ ፡
አገሩ ፡ ጥሩ ፡ ነው ፡ በጣም ፡ የሚስማማ
ልጄ ሆይ ፡ ቅጣቱ ፡ በጣም ፡ የቀለለ ፡
ጥሩ ፡ ነው ፡ ሺ ፡ ጊዜ ፡ ከሞት ፡ የተሻለ ።

#ሮሜዎ
ያስቡት ፡ አባቴ ፡ ነገሩን ፡ ያስተውሉት ፤
ምኑን ፡ ነው እርስዎ ቀላል ነው ፡ የሚሉት

#አባ_ሎራ
ብስጭት ፡ አታብዛ ፡ በጣም ፡ አትናደድ ፤
ከመሞት ፡ ይሻላል ፡ ሺ ፡ ጊዜ ፡ መሰደድ
ልጄ ፡ ዓለም ፡ሰፊ ፡ ነች ወጥተህ ከቬሮና
የትም ፡ ሄደህ ፡ መኖር ፡ ትችላለህና ።

#ሮሜዎ
ወጥቼ ፡ ከሄድኩኝ ፡ እኔ ፡ ከቬሮና ፡
ውሸት ፡ ነው ፡ አባቴ ፡ ምን ፡ዓለም ፡ አለና፡
ሕይወት ፡ ነው ፡ አይበሉት የምኖረው ኑሮ
ዓለም ፡ እዚህ ፡ ቀረ ፡ ከሚስቴ ጋር አብሮ'
ሰው ነህ እንስሳ ዕንጨት አበባና ፡ቅጠል ፡
ፀሐይ ፡ ተከልሎ ፡ አየር ፡ ሳይቀበል ፡
የኖረ ፡ እንደ ፡ ሆነ ፡ ይሞታል ፡ ይደርቃል፤
ለኔም ፡ እንደዚህ ነው ፡ ስደት የሚሉ፡ ቃል
አገሬ ፡ ንብረቴ ፡ አየሬ ፡ ፀሓዬ ፡
ዓለሜ ፡ ትንፋሼ ፡ ሕይወቴ ፡ ሰማዬ ፡
የነበረችውን ፡ ዝልዬትን ፡ አጥቼ ፡
እሷ ፡ ካለችበት ፡ ከተማ ፡ ወጥቼ ፡
መሄዴ ፡ ከሆነ ፡ እሷም ፡ ከኔ ፡ ርቃ ፡
ነጣጥለው ፡ ከለዩን ፡ የኔ ፡ ነገር ፡ በቃ ።
ሕይወቴም ፡ ኑሮዬም ፡ ሞተ ፡ ተበላሸ ፤
ደስታ ፡ ተለየኝ ፡ ከኔ ፡ ርቆ ፡ ሸሸ ፡
እንግዲህ ፡ መቆሜ ፡ ለምንም ፡ አይበጅ ፤
ይህን ፡ኑሮ ፡አይበሉት መናወዝ ነው እንጅ
ፍርድ ፡ ማሻሻያ ፡ የተባለው ፡ ዘዴ ፡
ከመርዝም ፡ ይብሳል ፡ ከጦር ፡ ከጐራዴ '
ስደት ፡ የሚሉ ፡ ቃል ፡ ጨለማ ነው ፡ ገደል
እኔን ፡ አስጨንቆ ፡ መጣ ፡ ለመግደል ።

#አባ_ሎራ
እረ ፡ ስማኝ ፡ ልጄ ፡ ምክሬንም ፡ ተቀበል ፡
ሞትና ፡ መሰደድ ፡ እኩል ፡ ነው ፡ አትበል

#ሮሜዎ
ተመልሰው ፡ ስደት ፡ ወደሚባለው ፡ ቃል ፡
ሊመጡ ፡ ነውና ፡ አባቴ ፡ ይበቃል ፡
ምን ፡ አደከመዎት ፡ በቃ በዚህ ፡ ዓለም ፡
እኔን ፡ የሚያጥናና ፡ ምንም ፡ ነገር ፡ የለም
ከሞት ፡ የባሰ ፡ ነው ፡ የመከራ ፡ ጭቃ ፤
የሮሜዎ ፡ ነገር ፡ ተከተተ ፡ በቃ ።

#አባ_ሎራ
ዐውቃለሁ ፡ እንዲሆን ፡ ስደትህ ፡ መራራ ፤
ግን ፡ መድኀኒት ፡ አለው ለዚህ ፡ ለመከራ'
ዕረፍት ፡ እንድታገኝ ፡ ባሳብ ፡ በኅሊና ፡
የደረሰብህን ፡ ጭንቅህን ፡ እርሳና ፡
ልብህን ፡ መልሰው ፡ ወደ ፡ ፍልስፍና ።

#ሮሜዎ
ዡልዬትን ፡ ፈጥሮልኝ ካልሰጠኝ ፡ አምጥቶ
የመስፍኑን ፡ ብይን ፡ በጥበብ ፡ አጥፍቶ ፡
እኔን ፡ ካላዳነኝ ፡ የርስዎ ፡ ፍልስፍና ፡
ለምንም ፡ አይበጀኝ ፤ የለውም ፡ ርባና ።
(የዡልዬት'ሞግዚት'ከደጅ'ሆና'በር መታች)

#አባ_ሎራ
ተነሣ ፡ ሮሜዎ ፡ ግባ ፡ ወደ ፡ ጓዳ ፤
ስማ ፡ በር ፡ ይመታል ፡ መጣብን ፡ እንግዳ
ተደበቅ ፡ በቶሎ ፡ ጥግ ፡ ይዘህ ወደ ፡ ጐን
ይይዙሃልና ፡ ያገኙህ ፡ እንደሆን ።
(በሩ ይመታል)

#ሮሜዎ
በስደት ፡ ከሆነ ፡ እኔ ፡ የምቀጣ ፡
ምን ፡ ያስጨንቀኛል ፡ የፈቀደው ፡ ይምጣ

#አባ ፡ ሎራ ።
ለምን ፡ ትሆናለህ ፡ አንተ ፡እንደዚህ ፡ ደረቅ
እባክህ ፡ ግባና ፡ በቶሎ ፡ ተደበቅ ፡ (ሮሜዎ ሄደ)
እንዲህ ፡ ባሁን ፡ ሰዓት ፡ የመጣ ፡ በማታ ፡
ማነው ፡ በጨለማ ፡ በሬን ፡ የሚመታ ?

#ሞግዚት
መጥቻለሁና ፡ ልካኝ ፡ እመቤቴ ፤
የዡልዬት ፡ ሞግዚት ፡ ነኝ ያስገቡኝ ፡ አባቴ

#አባ ፡ ሎራ ።
እንኳን ፡ ደኅና መጣሽ ፡ ነይ ግቢ ወዳጄ፤
(ከፍተውላት ገባች)

#ሞግዚት
ሮሜዎን ፡ አጣሁት ፡ ብፈልገው ፡ ሄጄ ።
ይንገሩኝ ፡ አባቴ ፡ ከመሸ ፡ አሁን ፡ ማታ
አይተው ፡ እንደ ፡ ሆነ ፡ ያለበትን ፡ ቦታ ፡

#አባ ፡ ሎራ ።
በሐዘኑ ፡ ሰክሮ ፡ ያለቅሳል
👍1
፡ ተጨንቆ ፤
ያውልሽ ፡ ከጓዳ ፡ እመሬት ፡ ላይ ፡ ወድቆ

#ሞግዚት
ዠልዬት ፡ እመቤቴም ፡ በዚሁ ፡ ሁኔታ ፡
ስታለቅስ ፡ ዋለች ፡ ይኸው ፡ እስከ ፡ ማታ ፡
ጥሩልኝ ፡ አባቴ ፡ መልክቴን ፡ ልንገረው ።
ሮሜዎ ፡ (ከጓዳ ' ወጣ) ።
ዡልዬት ፡ እንደ ፡ ምን ፡ ነች?መልካም ፡ የነበረው
ልቧ ፡ ተለውጦ ፡ ባደረግሁት ፡ ነገር ፡
አልጠላችኝም ፡ ወይ ? ምላስሽ ፡ ይናገር ፡
ልብሽ ፡ አይደብቀኝ ፡ ንገሪኝ ፡ አትፍሪ ፤
ያየሽውን ፡ ሁሉ ፡ አስተካክለሽ ፡ አውሪ ።
በሠራሁት ፡ ሥራ ፡ ፍቅራችን ፡ መጥፋቱ ፡
እንግዴህ ፡ ወደ ፡ ፊት ፡ ተቀብሮ ፡ መቅረቱ
እርግጥ፡አይደለም ፡ ወይ ? እንዴት፡ ነው ፡መንፈሷ ፤
እኔን ፡ ስታነሣ ፡ ምን ፡ ትላለች ፡ እሷ ።

#ሞግዚት
በሐዘን ፡ ተጨንቃ ፡ ከማልቀስ ፡ በስተቀር ፡
ክፉም ፡ ሆነ ፡ በጎ ፡ ምንም ፡ አትናገር ፡
ቲባልት ሮሜዎ ! አዬ ፡ ጕድ ፡ እያለች ፡
እንባዋን ፡ በማፍሰስ ፡ ቀኑን ፡ሙሉ ፡ ዋለች
ሐዘኗ ፡ ግን ፡ ሆኗል፡ አለመጠን ፡ ብርቱ ፥
ከመሄድህ ፡ በፊት ፡ ተሰነባበቱ ፤
እንሂድ ፡ በቶሎ ፡ መሸብን ፡ ሰዓቱ ።

#ሮሜዎ
ገላዬን ፡ ብወጋ ፡ እስቲ ፡ ከምን ፡ ቦታ ፡
መሞት እንደምችል በቅጽበት ፡ አንዳፍታ
ብልኅ ፡ ነዎትና ፡ ጥበብን ፡ መርማሪ ፤
ተምረው ፡ እንደሆን ፡ ያከላትን ፡ ባሕሪ ፡
በፍጥነት ፡ ይንገሩኝ ፡ አባቴ ፡ አባ ፡ ሎራ ፤
የት ፡ ነው የሰው ነፍሱ ያለችበት ፡ ስፍራ ?
አድርጊያለሁና ፡ ጸጸቷን ፡ መራራ '
ሐዘኔ ፡ጥልቅ ፡ ነው ፡ አልችልም ፡ ልጥናና
በገዛ ፡ እጄ ፡ ልሞት ፡ ቁርጫለሁና ። (ሰይፉን መዘዘ።)

💫ይቀጥላል💫
#ሮሜዎና_ዡልዬት


#ክፍል_ዘጠኝ


#አባ_ሎራ
ለምን ፡ ታስባለህ ፡ እንዲህ ፡ ያለ ፡ ነገር ፤
ብላሽ ፡ ሰው ፡ አትሁን ፡ ሲመክሩህ ፡ ተመከር ,እንደ ፡ ሴት ፡ አታልቅስ ፡ እንዳውሬ ፡ አትቈጣ
እንደ፡እብድ፡አትበሳጭ ፥ ከሰው፡ ግብር፡ አትውጣ
ትመስለኝ ፡ ነበረ ፡ በውነቱ ፡ ጠንካራ ፤
ሰው ፡ ለምን ፡ ይረባል ፡ ካልቻለ ፡ መከራ
መቀጣት ፡ ከወደድህ ፡ በገዛ ፡ እጅህ ፡ ሞተህ ፡
ስለምን ፡ ገደልከው ፡ ቲባልትን ፡ ተዋግተህ ?
በገዛ ፡ እጅህ ፡ ብትሞት ፡ ባለማመዛዘን ፡
መግደልህ ፡ እኮ ፡ ነው ሚስትህን ፡ በሐዘን '
ለዚህ ፡ ነው ፡ ልጄ ፡ ሆይ ፡ ኅሊናና ፡ አእምሮ ፡
ከእግዜር ፡ የተሰጠ ፡ ለሰው ፡ ልጅ ፡ ተፈጥሮ'
ዡልዬት ፡ ጠልታኛለች ፡ ብለህ ፡ ስትሠጋ፡
ሰው ፡ ልካ ፡ ጠራችህ ምሕረትን ፡ አድርጋ
ቲባልት ፡ ሊገድልህ ፡ ቢመጣ ፡ ደንፍቶ ፡
በገዛ ፡ ጥጋቡ ፡ ወደቀ ፡ ተወግቶ "
ባንተም የሞት ቅጣት ሊወድቅ የነበረው
በስደት ፡ ለውጦ ፡ መስፍናችን ፡ ሻረው '
ብትመለከተው : በውነቱ ፡ የት ፡ አለ ፤
እንዳንተ ፡ የቀናው ፡ በጣም ፡ የታደለ ፡
ተጠንቀቅ ፡ በውነቱ ፡ ልጄ ፡ በጣም ፡ ሥጋ
ሳታውቀው ፡ ብትቀር ፡ የደስታን ፡ ዋጋ ፡
ኑሮህ ፡ይበላሻል ፡ አለመጠን ፡ ፍራ ፡
ምን ፡ጊዜም ፡ አይለቅህ ፡ ጭንቅና ፡ መከራ ።
ሚስትህን ምከራት ፡ እንዳትሞት ፡ አልቅሳ
መምሸቱ፡ነውና፡ በል ቶሎ ፡ ተነሣ፡
ነገ ፡ ግን ፡ ለመሄድ ፡ ልብህ ፡ይሰናዳ ፤
ውጣ ፡ ከቬሮና ፡ ሌሊት ፡ በማለዳ
ተዛውረህ ተቀመጥ ፡ ሄደህ ፡ ወደ ፡ ማንቱ
እኛ ፡ ጊዜ ፡ አግኝተን ፡ ሲመቸን ፡ ሰዓቱ ፡
ወገኖቻችሁን ፡ በምክር ፡ አስታርቀን ፡
ጋብቻችሁንም ፡ በገሃድ ፡ ኣስታውቀን ፡ .
ላንተም ፡ ከመስፍኑ ፡ ምሕረትን ፡ ጠይቀን
እንጣጣራለን ፡ ቶሎ ፡ እንድትመለስ
እግዜር ፡ይጠብቅህ በል እስከዚያ ፡ ድረስ
አሁን ፡ ወደ ፡ ዡልዬት ፡ በቶሎ ሂድ ፡ ተነሥ

የካፑሌ ሚስት #ካፑሌ #ፓሪስ

#ፓሪስ
ጉዳዩ ዘገየ ፡ በመዋል' በማደር ፤
ታዲያስ እንዴት ፡ ሆነ ፡የጋብቻው ፡ ነገር ?

#ካፑሌ
ነገሩን ፡ ለዡልዬት ፡ ሳልነግር ፡ መቅረቴ ፡
ወድጄን ፡ አይደለም ፡ እንዲህ ፡ መዘግየቴ
በቲባልት ፡ መሞት ፡ አዝናለች ፡ በብርቱ ፤
ታፈቅረው ፡ ነበረ ፡ ከልቧ ፡ በውነቱ ፡
ስለዚህ ፡ ሐዘኑ ፡ ጥቂት ፡ ሳይረሳ ፡
አልቻልኩም ፡ ጕዳዩን ፡ ለጊዜው ፡ ላነሣ ፡
አድርግልኝና ፡ ከልብህ ፡ ይቅርታ ፤
እኔ ፡ እጨርሳለሁ ፡ ነገሩን ፡ አንድ ፡ አፍታ

#ፓሪስ
እውነት ፡ ነው ሐዘኑ ፈጽሞ ፡ አልተመቸም
ተስማምተንበታል ይህን ጕዳይ ፡ መቼም
እሷም እንቢ እንዳትል ፡ እናንተ ፡ አስቡበት

#የካፑሌሚስት _ ።
ግድ የለም ሠርጋችሁ ይሆናል በፍጥነት

#ካፑሌ
ፓሪስ ሆይ አትሥጋ አይዞህ ይህን ጕዳይ
መሄድ ፡ ትችላለህ ፡ ጥለኸው ፡ በኔ ፡ ላይ
እንዴት ፡ ትወጣለች ፡ ከኔ ፡ ፈቃድ ፡ ልጄ ፤
ያቀረብኩላትን ፡ መርጬ ፡ ወድጄ
ያላንድ ፡ ቅሬታ ፡ አለባት ፡ መቀበል ፤
እንዲያውም ፡ እንፍጠን ፡ ዛሬ ነገ ፡ አንበል
በይ ፡ ፍጠኝ ፡ ሚስቴ ፡ ወደ ፡ ልጅሽ ፡ ሂጂ
በዘዴ ፡ በርጋታ፡ነገሩን አስረጂ ፡
መልካሙ ፡ ልጃችን 'ፓሪስ ፡ አንቺን ፡ ወዶ ፡
እኔም ፡ ደስ ፡ ብሎኝ ፡ አባትሽም ፡ ፈቅዶ ፡
ይኸው ፡ በዚህ መሰሞን ሊያገባሽ ፡ ነውና
ተዘጋጂ፡ በያት ፡ በሙሉ ፡ ልቡና '
በል ፡ አንተም ፡ ንገረኝ ፡ እንደምትፈልገው
ሰርጉ ፡ እንዲፈጸም ለመቼ እናድርገው ?

#ፓሪስ
እንደ ፡ እኔ ፡ ሰርጋችን ፡ የራቀ ፡ ከሚሆን ፡
ቢፈጸም ፡ ይሻላል ፡ አሁን ፡ በዚህ ፡ ሰሞን

#ካፑሌ
እንግዲያው መልካም ነው ባጭር እንደግስ
ተክሊሉም ፡ ይፈጸም ፡ በሚመጣው ፡ ኀሙስ ፡
ጃጃታ ፡ አላበዛም ብዙም ፡ ሰው ፡ አልጠራ ፤
ልጄን ፡ እድራለሁ ፡ ብዬም ፡ አላወራ ፡
ሐዘን ፡ ስለ ፡ ሆነ ፡ቲባልት፡ በመሞቱ ፡
ቅር ፡ ያሰኛልና ፤ ዘመድ ፡ በጥቂቱ ፡
በድብቅ ፡ እንጥራ ፡ ነገር ሳናበዛ ፤
እንደዚህ 'ብናደርግ ፡ ወሬው ፡ ሳይነዛ ፡
ጉዳያችን'ያልቃል፡ያግር፡ ሰው ፡ ሳይሰማ ፤
እንግዲህ ፡ መልካም ፡ ነው ፤ በዚሁ 'እንስማማ ።

#ፓሪስ
እኔም ፡ እስማማለሁ ፡ ይሁን ፡ በዚሁ ፡ ቀን
በሉ ፡ እስከዚያው፡ድረስ፡እግዜር፡ይጠብቀን ። (ሄዳ).

#ካፑሌ ፡ (ለሚስቱ )
እንደዚህ ፡ ያለ ፡ ባል ፡ ትልቅ ፡ ሰው ፡ የበቃ
ቢሄዱ ፡ አይገኝም ፡ እግር ፡ እስቲነቃ ፡
በይ ፡ ቶሎ ፡ ፍጠኚ ፡ ወደ ፡ ልጅሽ ፡ ሂጂ ፤
ነገ ፡ ጧት ፡ አሳቧን ፡ ልቧን ፡ አዘጋጂ ።

#ሮሜዎና #ዡልዬት ፡ (በዥልዬት ' መኝታ ፡ ቤት) ።

#ዡልዬት
አይዞህ፡አትቸኵል ፡ አልነጋም ፡ ሌሊቱ ፤
ቁጭ ፡ በል ፡እናውጋ ፡ ገና ፡ ነው ፡ ሰዓቱ ፡
ተመልከት ጨለማ መሬቱን
ሲሸፍን ፡
የሰማናትም ፡ ወፍ ፡ አሁን ፡ ስትዘፍን ፡
ዞትር ፡ ልማዴ ፡ ነው ፡ ሌሊቱ ፡ ሳይነጋ ፡
መጮህ ፡ ትወዳለች ፡ እመነኝ ፡ አትሥጋ

#ሮሜዎ
ይህች ፡ የንጋት ፡ ወፍ ፡ ነች ፡ አሁን ፡ የጮኸችው ፤
ትክክል ፡ ይታያል ፡ ዡልዬት ፡ ተመልከችው
ሰማይ ወገግ፡ አለ ፡ ያው በምሥራቅ በኩል ፤
ሰዓቱ ፡ ደረሰ ፡ እንግዴህ ፡ ልቸኵል ፡
በቬሮና ፡ አድሬ ፡ ቢያገኙኝ ፡ ሳልወጣ ፡
መስፍኑ ፡ ፈርደዋል ፡ በሞት ፡ እንድቀጣ ፡
ልዳን ፡ ያልኩ ፡ እንደሆን ፡ ሕይወቴን ፡ ወድጄ ፡
መሄድ ፡ ይገባኛል ፡ አሁን ፡ ተሰድጄ ።

#ዡልዬት
እኔ ፡ መች ፡ አጣሁት ፡ ይህ ፡ ያሁኑ ፡ ብርሃን ፡
የሰማይ ፡ ፋና ፡ ነው ፡ የኮከብ ፡ ውጋጋን
ሌሊት ፡ በጨለማ ፡ ሳይነጋ ፡ ሌሊቱ ፡
ለምን ፡ ትሄዳለህ ፡ አሁን ፡ ወደ ፡ ማንቱ ፡
አይዞህ ፡ እንጫወት ሌቱ ፡ አልነጋም ፡ ገና
ጊዜ ፡ አለን ፡ እስኪታይ ፡ የንጋቱ ፡ ፋና ።

#ሮሜዎ
ዘፈኑ ፡ ሲወጣ ፡ አልሰማንም ፡ ካፍ
አልነጋም ፡ ሌሊቱ ፡ አልጮኸችም ፡ ወፍ፡
ይህም ፡ በሰማይ ላይ የሚታይ ፡ ውጋጋን አይደለም ፡ የመጣ ፡ ከፀሓይዋ ፡ ብርሃን ፡
ብለን ፡ እንካደው ፤ አምኜ፡ ልቀበል !
ሳልወጣ ፡ ይያዙኝ ፡ ተይዤም ፡ ልገደል "
ካንቺ ፡ ተለይቼ ፡ የሐዘን ፡ ኵነኔ ፡
ከሚያገኘኝ፡ መሞት ፡ እመርጣለሁ ፡ እኔ ።
አልፈራም ፡ ፈጽሞ ፡ በሞት ልቀጣ
ዡልዬት ፡ ከፈቀደች ፡ የፈለገው ፡ ይምጣ ፡
ወፎች አልተንጫጩም ሌሊቱም ፡ አልነጋ
ዡልዬት ጨዋታ አምጪ እንግዴህ እናውጋ፡

#ዡልዬት
እኔ ፡ ብዬ ፡ ነበር ፡ ገና ፡ ነው ፡ ሌሊቱ፤
አሁን ፡ ገና ፡ታየኝ ፡ ትክክል ፡ መንጋቱ ፡
ንጋት ፡ ነው ፡ የመጣው ፡ ሂድ ፡ ቶሎ ፡ ተነሣ፤
አምልጠህ ፡ ሽሽ ፡ ቶሎ ፡ ብረር ፡ በግሥገሣ ፡
እየው ፡ ተመልከተው ፡ የንጋት ፡ ወገግታ፤
ጨለማውን ቀዶ፡ ሄደ ፡ እየበረታ ፡
አስተውለው ፡ መሬቱ ፡ ሲታየን ፡ ተገልጦ ፤
አሞኘችኝ፡ ወፏ ድምፅዋ ፡ ተለውጦ ፡
ፍጠን ፡ ቶሎ ውጣ እየው፡እንደ፡ ነጋ ፤
ተነሥ ፡ ቶሎ ፡ ጥፋ፤ አይንካህ ፡ አደጋ ።

#ሞግዚት
እናትሽ ፡ ነቅተዋል' እመቤቴ ፡ ዕወቂ፤
መንጋቱ ፡ ነውና ' በጣም' ተጠንቀቂ "
ደኅና ሰንብት ፡ ልበል ፡ እኔው ፡ አስቀድሜ
እንግዴህ ፡ ደኅና'ሁን'ሮሜዎ ፡ ወንድሜ ።

#ሮሜዎ
ዡልዬት ደኅና ሁኝ ፡ ደኅና ሰንብች ፡ ፍቅሬ

#ዡልዬት
አደራ ፡ እንዳገኘው ፡ እኔ ፡ ያንተን ፡ ወሬ ፡
ሁል ፡ ጊዜ ጻፍልኝ ፡ መሆንህን ፡ ጤና ፤
መቼ ፡ እንደማገኝህ ፡ አላውቀውምና ።

#ሮሜዎ
መቼም ፡ ቢሆን ፡ ካንቺ ፡ አይለይም ፡ ልቤ
እጽፍልሻለሁ ፡ ሁል ፡ ጊዜ ፡
ደብዳቤ ።

#ዡልዬት
አንተ ፡ ስታስበው ፡ ወደ ፡ ፊት ፡ ዳግመኛ ፡
እንገናኛለን ፡ ትላለህ ፡ ወይ ፡ እኛ?

#ሮሜዎ
አምናለሁ ፡ ፍቅሬ ፡ ሆይ ፡ አምላክ ፡ እንዲራራ፤
ትምህርት ፡ ይሆነናል 'ያሁኑ ' መከራ ።

#ዡልዬት
የሆንኩትን ፡ እንጂ ፡ እኔ ፡ ግን ፡ ለራሴ ፤
መጥፎ' መጥፎ ነገር ያስባል' መንፈሴ

#ሮሜዎ
ያገኘን ፡ መከራ ፡ ስለ ፡ ሆነ ፡ ብርቱ ፡
ከመንፈሳችን ውስጥ አይጠፋም
ስሜቱ ፤
ዡልዬት ፡ ደኅና ፡ ሁኝ ፡ ረፈደ ፡ ሰዓቱ ፡(ሄዳ).

💫ይቀጥላል💫
#ሮሜዎና_ዡልዬት


#ክፍል_አስራ_ሁለት

#ሞግዚት
ሞታለች ፡ ሞታለች ፡ ጕድ ፡ ነው ፡ የሚያስደንቅ ,

#የካፑሌ_ሚስት
ምን ፡መድኀኒት ላምጣ ወዴት ስፍራ ሄጄ

#ካፑሌ
ቆዩ፡እስቲ፡እኔ፡ልያት፡ የታለች፡ ቀዝቃዛ ፡ (እየዳበሳት).
ፈጽማ ፡ ሞታለች ፡ በምን ፡ ጕዴ በዛ
ሌሊት፡ በጨለማ ፡ ፀሓይዋ፡ ሳትወጣ ፡
ልጄ ፡ አበባዬ ፡ ወድቃለች ፡ ተቋርጣ ።

#ሞግዚት
የተረገመ ፡ ነው ፡ አወይ ፡ የዛሬው ቀን ፤

#የካፑሌ_ሚስት
ምነው ፡ ብንቀበር ፡ ሁላችንም ፡ አልቀን !

#ካፑሌ
ምንም ፡ አልናገር' ምላሴ 'ታሰረ
ልሳኔ ፡ በሐዘን 'ተቁልፎ ፡ ቀረ ።
(አባ ' ሎራና 'ፓሪስ ' በሙዚቃ ገቡ ።)

#አባ_ሎራ
ወደ ፡ ቤተ ፡ ክርስቲያን እንሂድ ፍጠኑ
ሙሽራዋን ጥሩ እናንተም ቶሎ'ኑ ።

#ካፑሌ
ጉድ ሆነናል ዛሬ ይተዉ አባቴ
ጕድ ፡ ለማየት ፡ ኖሯል ፡ የቈየች ፡ ሕይወቴ
እኔ ፡ ወዴት ፡ ልድረስ ፡ የት ፡ አባቴ ፡ ልግባ
ሞተች ፡ ተቀጠፈች ፡ ልጄ ፡ የኔ ፡ ኣበባ ።
እናቷ ፡ ሳታስብ ፡ ኣባቷ ፡ ሳይሰማ ፡
ሞት ፡ የሚባል ፡ ሌባ ፡ ሌሊት በለጨለማ
ለካ ፡ ከቤታችን ፡ ገብቶ ፡ ተደብቆ ፡
ይዟት ፡ ሄዶ ፡ ኖሯል ፡ ልጃችንን ፡ ሰርቆ ፤
እንዴት ፡ ጉድ፡ ሆነናል ፡ እንዲህ ፡ ተደግሶ
ሰርጓ ሐዘን ፡ ሆነ ደስታችን ለቅሶ ።

#ፓሪስ
እኔ ፡ ዕድለ ፡ ቢሱ፡ እንዴት፡ ያለ ፡ መርዶ፡
እንዴት ፡ ያለ ፡ሐዘን ፡ ጠበቀኝ ፡ ተወልዶ

#የካፑሌ_ሚስት
የተረገመ ፡ ነው ፡ አወይ ፡ የዛሬ ፡ ቀን
ቀረን ፡ እኮ ፡ ሰዎች ፡ እንደዚህ ፡ ተሳቀን ፡
ያይኖቼ ፡ ማረፊያ ብትኖረኝ አንዲት ፡ ልጅ
ያንድ ፡ ቀን 'ደስታ' ለማየት'ስዘጋጅ፡
ለማን ኣቤት ልበል ፡ ሞት ፡ ይዞብኝ ፡ ሄደ
ሆዴ ተቃጠለ አንጀቴ ፡ ነደደ

#አባ_ሎራ "
ይብቃ ፡ ለሐዘኑ ፡ አድርጉለት ፡ መጠን ፤
አስቡ ፡ ይችን 'ልጅ' እግዜር ፡ ነው' የሰጠን
አሁንም ፡እግዚአብሔር ወሰዳት መልሶ :
ሐዘናችሁ ፡ አይሁን ፡ ያረመኔ ፡ ለቅሶ ፡
ቀረባት ፡ ብላችሁ ፡ የመሬት ፡ ደስታ ፡
ጸጸታችሁ ፡ አይሁን ፡ በጣም ፡ የበረታ ፡
የመሬት ፡ ደስታ ፡ ምንም ፡ የለው ፡ ዋጋ ፤
ይልቅ አይበልጥም ወይ የሰማይቤት ጸጋ፡
ከሚያልፍ ፡ዓለም ወጥታ፡ ከዘለዓለም ቤቷ
መተላለፍ፡ ነው ፡ በሰላም ፡ መግባቷ ፡
መሆኑ ፡ ቀረና፡ ሰርጓ በመሬት ላይ፤
ብርሃን ፡ ወዳለበት፡ሄደች፡ ወደ ፡ ሰማይ ፡
እናድርጋት ፡ ስንል ፡ ምድራዊት ፡ ሙሽራ ፡
አይሆናትም ፡ ብሎ ፡ የመሬት ፡ መከራ ፡
ሺሕ ፡ ጊዜ ፡ የላቀ ፡ ደስታ፡ አዘጋጅቶ ፡
እግዚአብሔር ፡ ወሰዳት ፡በፈቃዱ ፡ ጠርቶ
የሰርግ ልብሷን ለብሳ እንዳማረች በክብር
በሉ ፡ ያዟትና ፡ እንሂድ ፡ መቃብር ።

#ሮሜዎ ። (በተሰደደበት ፡ አገር 'ሆኖ)
መሠረት ፡ ቢኖረው ፡ የኔ ፡ ሕልም፡ ዛሬ ፡
አገኝ ፡ ይመስለኛል ፡ ደስ የሚያሰኝ ፡ ወሬ
ዡልዬት ፡ ስትመጣ ፡ ስታገኘኝ ፡ ሞቼ ፡
አልቅሳ ፡ ስትስመኝ ፡ እኔ ፡ ተዘርግቼ ።
ኋላም ፡ በሷ ፡ ትንፋሽ ፡ ሕይወቴን ፡ አድሼ
ከሞት ፡ ተነሥቼ ፡ አየሁኝ ፡ ነግሼ ።
በጣም ፡ ደስ ፡ ብሎኛል ፡ ዛሬ ጧት፡ጀምሮ
ሰላም ፡ ይሰማኛል ፡ የመንፈስ ፡ የአእምሮ
(ቤልሻጥር ቦት ጫማ አድርጎ፡ መጣ)
ቤልሻጥር ፡ጐበዙ፡ እንኳን ፡ ገባህ ፡ ደኅና'
ምን ወሬ ይዘህ መጣህ ዛሬ ከቤሮና ?
ዡልዬት ደኅናነች ወይ አባቴስ እንዴት ነው ?
እሷ ፡ ደኅና፡ ብትሆን ፡ግድ የለም የቀረው
ዡልዬት ፡እንደ ፡ምን ነች ? አሁንም አድሼ
ልጠይቅህ ፡ በጣም ሺሕ ፡ ጊዜ ፡ መልሼ

#ቤልሻጥር
ደኅና ፡ ነች ፡ ልበልህ ፡ አልነካትም ፡ ዐፈር
እንደሌላው ፡ ፍጥረት ፡ መሬት ፡ ሳትቀበር
ከመቃብሩ ፡ ቤት፡ ሠርተው ፡ አባቷ
ካዘጋጁት ፡ ገብታ ፡ እግሮቿም ፡ እጆቿ ፡
ታስረው ፡ ሳትገነዝ ፡ በማዕርግ ፡ ተንጋላ ፡
ተኝታ ፡ ኣየናት ፡ ያንቀላፋች ፡ መስላ ።
እንዲህ ፡ በጌትነት ፡ ዡልዬት ፡ ተቀበረች ፤
በቃ ፡ የሷ፡ ነገር ፡ እንደ ፡ ዘበት ፡ ቀረች ።
ነፍሷ ፡ ግን ወደ እግዜር ዐረገች ወደ ላይ
ዐርፋ ፡ ከዚህ ዓለም ወጣች ፡ ወደ ሰማይ

#ሮሜዎ ። (በድንጋጤ ፊቱ ተለወጠ)
ምን ፡ አገኛትና ? በምን ፡ የተነሣ ?

#ቤልሻጥር
ጧት፡ ባልጋዋ ፡ ላይ ፡ በድን ሆና ሬሳ፡
ተገኘች ፡ ከእንቅልፍ፡ ሳትነቃ ፡ ሞታ ፤

#ሮሜዎ
እንደዚህ ፡ ከሆነ 'የዡልዬት ፡ ሁኔታ ፡
ደግ ፡ ነው መልካም ፡ ነው ፤ ብዕር፡ቀለም፡ኣምጣ፡
ፈረሶች ፡ ተከራይ ፈጥነህ መንደር ፡ውጣ
ማንም ሰው ሳያየኝ ማንም ሰው ሳይሰማ
መሄዴ' ነውና ፡ ሌሊት ፡ በጨለማ ።

#ቤልሻጥር
እባክህ ፡ ጌታዬ ፡ ፊትህ ፡ ተለወጠ ፤
ደምህም ፡ ጠቈረ ፡ ልቤ ፡ ደነገጠ '
ቻለው ፡ ሐዘንህን ፡ ከትዕግሥት ፡ ጋራ

#ሮሜዎ
አትሥጋ ፡ ግድ የለም ፡ ቤልሻጥር አትፍራ
የማይሆን አይሆንም የሚሆን ፡ ይሆናል !

ይልቅ ፡ቶሎ ፡ ፍጠን ፡ ጊዜው ፡ ያልፍብናል
(ቤልሻጥር ሄደ፤ ሮሜዎ'ብቻውን) »
እንገናኛለን ፡ ዥልዬት ፡ ዛሬ ፡ ማታ ፤
ወዳንቺ ፡ ለመድረስ ፡ ቶሎ ፡ በደስታ ፡
መንገዱን ፡ መፈለግ ፡ አለብኝ ፡ ግዴታ ፡
መድኀኒት ፡ የሚሸጥ ፡ አንድ ፡ ጎረቤቴ ፡
መኖሩን ፡ ዐውቃለሁ ፥ እኔ ፡ በሕይወቴ ፡
አይቼ ፡ አላውቅም ፡ ችግረኛ ፡ እንደ ፡ እሱ
ሁል ፡ ጊዜ ፡ ያደፈ፡ ቀዳዳ ፡ ነው ፡ ልብሱ ፡
የተጐዳ ፡ ሰው ፡ ነው ፡ ድህነት ፡ ያጠቃው
ሰውነቱ ፡ ከስቷል ፡ የመደብር ፡ ዕቃው ፡
አሮጌ ፡ ብቻ ፡ ነው ፡ ቈሻሻ ፡ ሰባራ ፤
ተጠርጎ ፡ የማያውቅ ፡ የለበሰ ፡ ዐቧራ ።
ከሱቁ ፡ ስገባ ኔም አስተውዬ
እሱን ፡ባየሁ ቍጥር አሰብኩ እንዲህ ብዬ
በማንቱ ፡ ከተማ ፡ ለሰው ፡ መርዝ ፡ የሸጠ
በምንም ፡ አኳኋን ፡ አውጥቶ ፡ የሰጠ ፡
ምንም ፡ እንኳ፡ የሚያዝ ፡ በሞት ፡ እንዲቀጣ ፡
ኀይለኛ ፡ ዐዋጅ ፡ ቢኖር ፡ ተጽፎ ፡ የወጣ ፡
መርዝ ፡ የሚፈልግ ፡ ሰው ፡ ብዙ ፡ ገንዘብ ፡ ሰጥቶ ፡
ይህን ችግረኛ፡ ቢጠይቀው ፡ መጥቶ ፡
አይጠረጠርም : እንቢ ፡ እንደማይለው ፤
ስለዚህ ፡ ጠርቼ ፡ እስቲ ፡ ልሞክረው ፡
አንተ ፡ መድኀኒት ፡ ሽያጭ፡ እባክህ ፡ ወዲህ ፡ ና ።

#መድኀኒት_ሽያጭ
ምነው ፡ ሮሜዎ አይዶለም ወይ ፡ ደኅና ?

#ሮሜዎ
ሰው ፡ አንተን ይሻሃል ባጣ ፡ ጊዜ ፡ ጤና፡
አንድ ፡ ነገር ፡ አሁን ፡ ልንገርህ ፡አድምጠኝ
ቶሎ ፡ የሚገድል ፡ ብርቱ ፡ መርዝ ፡ ስጠኝ፡
አርባ ፡ ዱካ ፡ ልስጥህ ለመርዝህም ዋጋ
አንተም ፡ ትሆናለህ ፡ በዚህ ፡ ባለጸጋ ፡
አንተን ፡ ለመሰለ ፡ በጣም ፡ ለተጐዳ ፡
ይህ ፡ ብዙ ፡ ገንዘብ ነው በጣም የሚረዳ

#መድኅኒት ፡ ሽያጭ ።
ኀይለኛ ፡ መርዝ አለኝ በመደብሬ ውስጥ
ግን ፡ ባዋጅ ፡ ክልክል ነው፡ለማንም፡ እንዳልሸጥ ።

#ሮሜዎ
ሞኝ ፡ ነህ ፡ መሰለኝ ፡ ዐዋጅ ፡ብሎ ፡ ጣጣ
ራብ ፡ ለገደለህ ፡ ዐጥንትህ ' ለወጣ'
ላንተ ፡ ምን ' ጠቀመህ ይልቅ ስጠኝ' ቶሎ
ድኽነት ፡ ይታያል ፡ በመልክህ ፡ ተሥሎ'
ጒዳት ፡ አቈራምዶ፡ ችግር ፡ ያሸነፈህ

💫ይቀጥላል💫
👍1
#ሮሜዎና_ዡልዬት


#ክፍል_አስራ_ሶስት

#በአባ_ሎራ_ቤት

አባ ፡ ዮሐንስ ፡ (ከውጭ ፡ መጣ) ።
ወዴት ፡ ነው ፡ ያለኸው ፡ አባቴ ፡ አባ ፡ ሎራ ?

#አባ_ሎራ
ተሳሳትኩ ፡ ብዬ ፡ በልቤ ፡ ባልፈራ ፡
በድምፅህ ፡ መሰልከኝ ፡ የኛ ፡ አባ ፡ ዮሐንስ ።

#አባ_ዮሐንስ
ዐውቀሃል ፡ እኔ ፡ ነኝ ።

#አባ_ሎራ
አንተ ፡ እስክትመለስ ፡
እጠብቅህ ፡ ነበር ፡ ቸኩዬ ፡ ባሳቤ ፡
ፈጥነህ ፡ ደረስክልኝ ፡ ስሥጋ ፡ በልቤ ፡
መልሱን ፡ ከሮሜዎ ፡ ለጻፍኩት ፡ ደብዳቤ አመጣህልኝ ፡ ወይ ?እስቲ ቶሎ ፡ ስጠኝ፤

#አባ_ዮሐንስ
የሆንኩትን ፡ ነገር ፡ ልንገርህ ፡ አድምጠኝ
ደብዳቤህን ፡ ቶሎ ፡ ለመስጠት ፡ ወስጄ
አንዱን ፡ የኛ ፡ ካህን ፡ ልፈልገው ፡ ሄጄ ፡
ወደ ፡ ሮሜዎ ቤት፡ እንዲወስድኝ መርቶ :
እሱም ፡ እሺ ፡ ብሎ ፡ ሊወስደኝ ፡ ተነሥቶ
ዘበኞች ፡ መጡና ፡ ከቤት ፡ እንዳንወጣ ፡
ዘግተውብን ፡ ሄዱ፤ ከውጭ ፡ የመጣ ፡
በሽታ ፡ ስላለ ማንም ፡ ከሌላ ፡ አገር፡
ሲመጣ ፡ አስቀድሞ ፡ ለካ ፡ እስቲመረመር
ለብቻው ፡ እንዲሆን ፡ የመጣው ፡ ሥራቱ፡
የሚያስገድድ ፡ ኖሮ ፡ ሳልሄድ ወደ ፡ማንቱ
ሮሜዎን ፡ ሳላገኝ ፡ ሳላየው ፡ ደርሼ
ያንተንም ፡ ደብዳቤ ፡ አመጣሁ ፡ መልሼ
ልልከው ፡ አስቤ ፡ ብሞክር ፡ ብለፋ:
ብጠይቅ ባስጠይቅ የሚላክ ሰው ፡ ጠፋ፡
አልሆንልህ ፡ አለኝ ፡ ነገር ፡ አልሳካ ፤
ይቅርታ ፡ አድሮግልኝ ፡ ደብዳቤህን፡እንካ ። (ሰጠው)

#አባ_ሎራ
ምንኛ ፡ መጥፎ ፡ ነው ፡ያመጣኸው ወሬ !
አይ ፡ አባ ፡ ዮሐንስ ፡ ጉድ ሰራኸኝ ፡ ዛሬ ።
መልክቴ ፡ በውነቱ፡ ትልቅ ጕዳይ ፡ ነበር ፤
በጣም ፡ የከበደ ፡ ከፍ ያለ'ቁም ፡ ነገር ፡
ባለመፈጸሙ ፡ የመልክቴ ፡ አደራ ፡
እጅግ ፡ የሚያሳዝን በጣም የሚያስፈራ፡
ነገር ፡ ለማስከተል ፡ ይችላል ፡ ወዳጄ ፤
ጽፌ ፡ የሰጠሁህ ፡ ያ ፡ ወረቀት ፡ በእጄ ፡
ለሮሜዎ ፡ ቶሎ ፡ መድረስ ፡ ነበረበት ፤
አይ ፡አባ ዮሐንስ ጕድ ሠራኸኝ በውነት !
እባክህ ፡ አሁንም ፡ ቶሎ ፡ እንረዳዳ ፤
ጕጠት ፡ ፈልግና ፡ አምጣልኝ ፡ ከጓዳ ።

#አባ_ዮሐንስ
ሳልችል ፡ ቀርቼ ፡ ነው ፡ በጣም ፡ ተቸግሬ ፡
ምን ፡ ሁን ፡ ትለኛለህ ፡ ስቀመጥ ፡ ታስሬ ፡
እንዴት ፡ ብዬ ፡ ልሂድ እንደ ፡ ምን ፡ አድርጌ
መልካም ነው ጕጠቱን ላምጣልህ ፡ ፈልጌ
(አባ ፡ ዮሐንስ ፡ ወደ ፡ ጓዳ ፡ ገባ) ።

#አባ_ሎራ ፡ (ብቻውን) ።
ከዡልዬት ፡ መቃብር ፡ ብቻዬን ፡ ገሥግሼ ፡
መዝጊያውን ፡ ልከፍተው ፡ በቶሎ ፡ ደርሼ
መድረስ ፡ ይገባኛል ፡ በቶሎ ፡ በቅጽበት
ጊዜው ፡ ደርሷልና ፡ የምትነሣበት ።
በተነሣች ፡ ጊዜ ፡ ሮሜዎን ፡ ስታጣ ፡
እንደ ፡ ምን ፡ ትረግመኝ ፡ በንዴት ፡ በቍጣ
አምጥቼ ፡ ላስቀምጣት ፡ በቤቴ ፡ ሸሽጌ ፤
ከዚያም ፡ እንደ ፡ ገና ፡ አንድ ፡ሰው ፡ ፈልጌ
ደግሞ ፡ ለሮሜዎ ፡ ሲሆን ፡ ዛሬ ፡ ማታ ፡
ጽፌለት ፡ ይመጣል ፡ ሁሉንም ፡ ሐተታ ።

(ፓሪስ ፡ ካሽከሩ ፡ ጋር ፡ አበባና 'መብራት ፡ ይዞ ፡ ወደ ፡ ዡልዬት ፡መቃብር ፡ መጣ) "

#ፓሪስ
መብራቱን አጥፋው እንግዲህ ይበቃል
ሰው የመጣ፡እንደሆን ምናልባት ማን ያውቃል
እዚህ ፡ ሰው ፡ እንዲያየኝ ፡ አልፈልግምና
በል ፡ ቅረብ ፡ተጠጋ ፡ አንተም ወደዚህ ፡ና።
ጀሮህን ፡ አቁመህ ፡ ተጠንቅቀህ ፡ ስማ ፤
ኰሽታ ፡ ስትሰማ ፡ ወይም ፡ የሰው ፡ ጫማ
ምልክት እንዲሆን አፏጭተህ አስታውቀኝ ፡
አስቀድሜ ፡ እንዳውቀው ፡ ፈጥነህ ፡ አስጠንቅቀኝ፤
በል ፡ እንግዲህ ፡ አሁን ፡ አበባውን ፡ ስጠኝ ።
(ፓሪስ ፡ ሄደ) ።

#አሽከር ፡ (ብቻውን) ።
የተሻለ ፡ ስፍራ ፡ ባገኝ ፡ ደግ ፡ ነበር ፤
ይህ ፡ ቦታ ፡ ቀፈፈኝ ፡አልወድም ፡ መቃብር
(እልፍ ፡ ብሎ ፡ ሄደ ) ።

#ፓሪስ ። (በዥልዬት ፡ መቃብር ፡ ላይ) ።
ይህንን ፡ አበባ ፡ መርጨ፡ ፈልጌ ፡
ላቀርብልሽ ፡ መጣሁ ፡ በረከት ፡ አድርጌ
ገጸ ፡ በረከቴ ፡ ጸጸት ፡ ነው ፥ አበባ ፤
ሐዘን ፡ ነው ፡ ለቅሶ ፡ ነው ፡ የመረረ ፡ እንባ
ትተሽኝ ፡ ብትሄጂ ፡ ብቻዬን ፡ ቀርቼ ፡
ልጐበኝሽ ፡ መጣሁ ፡ ሌሊት ፡ ተነሥቼ ።
(አሽከሩ ፡ አፏጨ) ።
እንሆ ፡ አፏጨ ፡ ሰማሁት ፡ አሽከሬ ፤
አሁን የሚመጣ ሰው፡ ነው ወይስ አውሬ ?
ሰላም ፡ የሚነሳኝ ማነው፡ ባሁን ፡ ሰዓት ?
እንዴት ? ደግሞ ፡ ያውም፡ይዟል ፡ በእጁ ፡ መብራት!
እስክረዳው ፡ ድረስ ፡ ምስጢሩን ፡ ዐውቄ ፡
ከለላ፡ፈልጌ፡ልየው ፡ተደብቄ (እልፍ፡ ብሎ ተደበቀ)

(ሮሜዎና ፡ ቤልሻጥር ፡ መብራትና ጉጠት ፡ ይዘው ፡ መጡ) ።

#ሮሜዎ
በል መብራቱን ስጠኝ፤ አንተ ግን ተመለስ
እገባለሁ ፡ እኔ ፡ መቃብሯ ፡ ድረስ ፤
አንተ ፡ ከዚህ ፡ ቦታ ፡ እንዳትንቀሳቀስ ፡
ዦሮህን ፡ አቁመህ ፡ ሰው ፡ ሲመጣ ፡ ስማ
ተደብቀህ ፡ ጠብቅ ፡ እዚህ ፡ በጨለማ ።
ያየህ ፡ እንደ ፡ ሆነ ፡ ሰው ወዲህ ሲመጣ፡
ከተደበቅህበት ፡ ቦታ ፡ ሳትወጣ ፡
በፉጨት ፡ ምልክት ፡ እኔን ፡ አስጠንቅቀኝ
ምናልባት ፡ ሰው ደርሶ ድንገት ፡ እንዳያየኝ
የዡልዬት ፡ ሬሳ ፡ ካለበት ፡ ገብቼ ፡
በመቃብሯ ፡ ውስጥ ፡ እሷን ፡ ተመልክቼ ፡
ካየኋት ፡ በኋላ ፡ ከልቤ ፡ አልቅሼ ፡
አንብቼ ፡ ሲያበቃኝ ፡ ሐዘኔን ፡ ጨርሼ ፡
የጣቷን ፡ ቀለበት ፡ አውልቄ ፡ ከሷ ፡ ላይ ፡
ልወስድ ፡አስቤያለሁ ላንድ ብርቱ ጕዳይ
ከወጣሁ ፡ በኋላ ፡ እኔ ፡ ከዚህ ፡ ቦታ ፡
ይህንን ፡ ደብዳቤ ፡ ጨምረህ ፡ ሰላምታ ፡
ላባቴ ፡ ስጥልኝ ፡ ነገር ፡ ግን ፡ ተጠንቀቅ ፤
ምን ፡ ይሠራል ፡ ብለህ፡ አሳቤን ፡ ለማወቅ
መሰለል ፡ አስበህ ፡ ወደ ፡ እኔ ፡ አትጠጋ ፤
ያገኝሃልና ፡ የመሞት፡ አደጋ ፡
በውነቱ ፡ ባገኝህ ፡ ይህንን ፡ ስትሠራ ፡
እጄም ፡ አያዝንልህ ፡ መንፈሴም ፡ አይራራ
ልብ ፡ በል ፥ተጠንቀቅ ለሕይወትህ ፡ ፍራ

#ቤልሻጥር
እኔ ፡ ከዚህ ፡ ቦታ ፡ አልንቀሳቀስም !
ስታስጠነቅቀኝ፡ትእዛዝ ፡ አላፈርህም። (ሮሜዎ'ሄደ)።

#ሮሜዎ ፡ (የዡልዩትን መቃብርዋን ' በር
ሊከፍት ፡ ይታገላል) ።
ከጥንት ፡ ጀምረህ ፡ ብትበላ ፡ ብትበላ ፡
ጠገብኩኝ ፡ የማትል ፡ ሆድህ ፡ የማይሞላ
መቃብር ፡የሚሉህ አንተ መጥፎ ከርሣም
ለወጣት ፡ አታዝን ፥ ለቆንዦ ፡ አትሣሣም
ዡልዬትን ፡ ከጥርስህ ፡ ፈልቅቄ ፡ ላወጣ ፡
መጥቻለሁና ፡ የዋጥከውን ፡ አምጣ ፡
አንዴ ፡ ልያትና ፡ እንባዬን ፡ አፍስሼ ፡
እርሜንም ፡ አውጥቼ ፡ ተራዬን ፡ አልቅሼ ፡
ሐዘኔን ፡ ገልጬ ፡ ከበቃኝ ፡ በኋላ ፡
እኔንም ፡ ከሷ ፡ ጋር ፡ አብረህ ፡ እንድትበላ

#ፓሪስ
መብራት ፡ በጁ ፡ ይዞ ፡ የመጣው ፡ ከደጅ
ሮሜዎ ፡ ይመስላል ፡ ያ የሞንታግ ፡ ልጅ፡
ጐበዙን ፡ ቲባልትን ፡ የዡልዬትን ፡ ዘመድ ፡
አሁን ፡ በቅርብ ፡ቀን ተጣልቶት ፡ በመንገድ
ገድሎ ፡ ተፈርዶበት ፡ ተሰዶ ፡ የወጣ ፡
አሁን ፡ ደግሞ ፡ እዚህ ፡ ምን ፡ ሊፈጥር፡ መጣ?

💫ይቀጥላል💫
#ሮሜዎና_ዡልዬት


#ክፍል_አስራ_አራት

ለክፋት ፡ ነው ፡እንጂ አልመጣም ፡ በደኅና
እንግዴህ ፡ ልያዘው ፡ ድንገት ፡ ልድረስና ።
(ቀረበ) ።
አንተ ፡ የሞንታግ ፡ ልጅ ፡ዐመፀኛ ፡ መጥፎ
በሰላም ፡ ጸጥታ፡ የተኛውን ፡ ዐርፎ ፡
ምን ፡ ልታደርግ ፡ ነው ፡ ትኵሱን ፡ ሬሳ ፡
ከመቃብሩ ፡ ላይ ፡ በል ፡ እጅህን ፡ አንሣ ፡
ና፡ ወዲህ ፡ ልያዝህ ፡ ከዚህ ፡ ቦታ ፡ ውጣ
ኣሳልፌ ፡ ልስጥህ ፡ በሞት ፡ ለሚቀጣ ።

#ሮሜዎ
አንተ መልካም ወጣት፡ዐርፈህ ሂድ በደኅና
እኔ ፡ ሞገደኛ፡ አጥፊ ፡ ሰው ፡ ነኝና ፡
መዘዜ፡ የበዛ ፡ አሳር ፡ የጐተተኝ፡
ሕይወቴን ፡ የጠላሁ፣ ኑሮ ፡ የታከተኝ፡
ሞትና ፡ መቃብር ፡ ጥፋት ፡ የሸተተኝ ፡
የከፋው ፡ ወንድ ፡ ነኝ ፡ ወደኔ ፡ አትጠጋ ፤ .
ጠብ ፡ አትፈልገኝ' ለሕይወትህ ፡ ሥጋ ።
ቲባልት ፡ እንደዚሁ ፡ ደርሶ : ሳይቸግረው ፡
በመጥፎ፡ ንግግር ፡ ሆዴን ፡ አሳረረው ፡
ሳልፈልግ ፡ ገደልኩት እሱ ባነሣው ፡ ጠብ
አሁን ፡ ደግሞ ፡ አንተ ይብቃህ ፡ አትሳደብ
ነፍሴን ፡ የጠላሁ፡ ሰው ፡ በመሆኔ ፡ ፍራኝ
ሳልወድ ፡ በግዴታ ፡ ዐመፅ ፡ አታሠራኝ ፡
የሚወጣው ፡ ምክር ፡ አሁን ፡ ከመላሴ ፡
አልሠራሁበትም ፡ እኔ ፡ እንኳ ፡ ለራሴ ፡
ስለዚህ ፡ ከራሴ ፡ አብልጬ ፡ ስወድህ ፡
እኔን ፡ አመስግነህ ፡ ይሻላል ፡ መሄድህ ፡
አንድ፡ እብድ ፡ ሰው ዛሬ የሰጠኝን ምክር
ሰምቼ ፡ ድኛለሁ ፡ ብለህ ፡ ይልቅ ፡ ፎክር ።

#ፓሪስ
እኔስ ፡ ኣለቅህም ፡ ከያዝኩህ ፡ በኋላ ፤
መስጠት ፡ ትችላለህ ፡ ምክርህን ፡ ለሌላ

#ሮሜዎ
መሞት ፡ ከፈለገህ ፡ እንቢ ፡ ብለህ ፡ በጄ ፡
እንግዲያው ሞክረኝ መልካም፡ነው ወዳጄ
(ይዋጉና'ፓሪስ ፡ ይወድቃል) ።.
ቲባልትና ፣ፓሪስ ፡ እኔን እያስቆጡ ፣
እኔ ፡ ሳልነካቸው ፡ በግድ ፡ እየመጡ፡
በእጄ ፡ እየተወጉ' ክዚህ ፡ ዓለም ፡ ወጡ ።
እንዲህ ፡ መሞታቸው ፡ ተናግረውኝ ፡ ክፉ
ተፈርዶባቸው ፡ ነው ፡ በኔ' እጅ እንዲጠፉ
እንደዚህ ፡ ከሆነ ፡ ፓሪስ ፡ ያንተም ፡ ዕጣ ፡
ጥፋቱ ፡ ያንተ ፡ ነው ፡ በኔ ፡ እንዳትቈጣ ፡
የዡልዬት ፡ ቁንዥና፡ ደምቆ እንደ ፡ ብርሃን
ጽርሐ አርያም ፡ መስሎ የሰማይ ፡ ውጋጋን
እያንጸባረቀ ፡ ከኮከብ ፡ ሲያበራ ፡
ግርማ፡ተጐናጽፎ፡ በታየበት፡ ስፍራ፡
እንሙት' ወዳጄ ፡ ኣብረን ፡ ከሷ ፡ ጋራ።
(ሮሜዎበዝልዬት፡መቃብር፡ላይየሐዘን ' ንግግር ፡ ያደርጋል)።
ይህችን ፡ ውብ ፡ አበባ ፡ ፍቅር ፡ አሳማሪ ፡
ውሏን ፡ የማትረሳ ፡ ቃል ፡ ኪዳን ፡ አክባሪ ፡
ትወድ ፡ የነበረች ፡ ቁም ፡ ነገር ፡ ጨዋታ፡
እዩልኝ ፡ ከዘመድ ፡ ከሰው ፡ ተለይታ ፡
የኔ ፡ ሆደ፡ ባሻ ፡ ብቻዋን ፡ ተኝታ፡
ተመልከቱት ፡ እጅዋ ፡ ተመልከቱት ፡ ፊቷ ፤
ወዟ ፡ ገና፡ አልጠፋም ። ከሠራ፡ አካላቷ፡
ግንባሯን ፡ ከንፈራን ፡ ተመልከቱ ፡ ጣቷን ፤
ይህን ፡ አበቃቀል ፡ ተክለ ፡ ሰውነቷን ፡
ገላዋ ፡ ያበራል ፡ በደም ፡ ተሸልሞ ፤
ዡልዬት ፡ሞት የነካት፡አትመስልም ፈጽሞ
እባካችሁ ፡ ሰዎች ፡ ሐዘን፡ ተካፈሉኝ፤
ዡልዬት ፡ አልሞተችም ፡ ተኝታለች ፡ በሉኝ
ታውቂ ፡ የነበርሽው ፡ ፍቅራዊ ፡ አቀባበል ፡
ሽቍጥቀጥ ፡እመቤት ባለመልካም ዐመል
ተወዳጁ ፡ ድምፅሽ ፡ ውብ ፡እንደ ፡ ሙዚቃ
በበገናው ፡ ቃሉ ፡ መንፈስ ፡ የሚያነቃ ፡
ዛሬ ፡ ወዴት ፡ ጠፋ? የት ፡ ቦታ ፡ ደረሰ ? .
ደግሞስ ዐይንሽ ፡ ቆቡን ስለ ምን ለበሰ ?
ዡልዩት ፡ ባትሞት ኖሮ፡ በውነት ፡ ባትቀበር
ሮሜዎ ፡ እዚህ ፡ ቆሞ ዝም አትልም ነበር
ባለም ፡ ላይ ፡ ብንሻ ፡ በውነቱ ፡ የት ፡ ኣለ ፡
ጨካኝ አረመኔ ፡ ሞትን ፡ የመሰለ ፡
ጥቂት ፡ አላዘነም ፡ አልሣሣም ፡ ጨርሶ ፡
ይችን ፡ ጽጌ ፡ ረዳ ፡ ሲጥላት ፡ በጥሶ :
ይችን ፡ አሳዛኝ ፡ ልጅ ፡ ትተዋት ፡ ሲሄዱ፡
በሩን ፡ የዘጋ ፡ ሰው ፡ እንዴት ፡ ቻለ ፡ ሆዱ
እይዋት ይችን ቄንጥ እይዋት ይችን ሎጋ
በባዶ፡ አዳራሽ ፡ በመቃብር ፡ ኣልጋ ፡
ወፍ ፡ በማይዞርበት ፡ ጭር ፡ ባለ ፡ ስፍራ ፡
ብቻዋን ፡ ቀርታለች ፡ አዲሷ ፡ ሙሽራ ።
በመከራ ፡ ቅመም ፡ ባሳር ፡ ተለውሶ :
ዡልዬት፡ ሕይወታችን ፡ መሮን ፡ እንደ ፡ኮሶ
ወጣን ፡ ከዚህ ፡ ዓለም ፡ ያላንድ ፡ ደስታ .
እንግዲህ ፡ እንኑር ፡ እዚህ ፡ በጸጥታ ።
ባለም ፡ ቦታ፡ ጠፍቶ ፡ ለመኖር'ተዋደን ፡
እዚህ ፡ ተገናኘን ፡ ካለም ፡ ላይ ፡ ተሰደን
አይቈጨን እንደዚህ ካለም መውጣታችን
በጣም ፡ ደስ ፡ይበለን ፡ በዛሬው ፡ ዕጣችን
ላለሙ ፡ ደስታ ፡ ለረዥሙም ፡ ዕድሜ ፡
ያው ሞት አይደለም ወይ የሁሉ ፍጻሜ ?
ገላዬን ፡ ከገላሽ ፡ ዐፅምሽን ፡ ካዕፅሜ ፡
ሥጋዬን ፡ ከሥጋሽ ፡ ደምሽን ፡ ከደሜ ፡
ቀላቅሎ ፡ የሚያኖር፡ ከተገኘ ፡ ቦታ ፡
ዡልዬት፡ ከዚህ ፡ ወዲያ ፡ ምን አለ ፡ ደስታ
ይቅር ፡ ደኅና ፡ ይሁን ፡ ዓለም ፡ ከነቂሙ ፤
እዚህ ፡ እኔና፡ አንቺ ፡ እስከ ፡ ዘላለሙ ፡
መቃብር፡ ሆኖልን ፡ የጸጥታ ፡ ገዳም ፡
ከዛሬ ፡ ጀምሮ ፡ እንኑር ፡ በሰላም ።
ከሚወዱት፡ጋራ፡ እንዲህ ፡ ጐን ፡ ለጐን ፡
ምንኛ ፡ መልካም ፡ ነው ፡ ዐፈር ፡ ትቢያ ፡ መሆን ።
(ሮሜዎ ፡ መርዝ ፡ ጠጥቶ ፡ ሞተ ።)

#አባ_ሎራ መብራትና፡ጕጠት፡ ይዞ ፡
ወደ፡መቃብሩ፡ ቦታ፡ መጣ ።

#አባ_ሎራ
ስፍራው ፡ አያስኬድም ፡ ሆነና ፡ መቃብር
እያደናቀፈ ፡ ያስቸግራል ፡ ለእግር ፡
አዬ ፡ መከራዬ ፡ በዚሁ ፡ ላይ ፡ ደግሞ ፡
ምንም ፡አይታየኝ ፡ዐይኔ ፡ በጣም ፡ ደክሞ
ማነህ አንተ እዚህ የቆምከው እንደ አጥር ?

#ቤልሻጥር
የሚያውቁኝ ፡ወዳጅዎ ፡እኔ፡ ነኝ ቤልሻጥር ።

#አባ_ሎራ
እግዚአብሔር ይባርክህ በል ልጄ ንገረኝ ፤
በሩቅ ፡ አላይ ፡ ብሎ ፡ ዐይኔ ፡ አስቸገረኝ፡
እዚያ ፡ በካፑሌ ፡ የመቃብር ፡ ስፍራ ፡
መብራት አይደለም፡ ወይ የማየው ፡ ሲበራ?

#ቤልሻጥር
አዎን ፡ ነው ፡ አባቴ ፡ ሄዷል ፡ እዚያ ፡ ቦታ ፡
ወዳጅዎ ፡ ሮሜዎ ፡ የኔ ፡ መልካም ፡ ጌታ

#አባ_ሎራ
ማን ፡ አልከኝ ?

#ቤልሻጥር
ሮሜዎ

#አባ_ሎራ
አዬ ፡ የእግዜር ፡ ቀጣ
ምን ፡ ያኽል ፡ ጊዜ ፡ ነው ፡ እሱ ፡ እዚህ ፡ ከመጣ ?

#ቤልሻጥር
ልክ ፡ እኩል ፡ ሰዓት ፡ ነው ።

#አባ_ሎራ
ና፡ እንሂድ፡ ወደ ፡ እሱ

#ቤልሻጥር
አልችልም ፡ አባቴ ፡ አስጠንቅቆ ፡ ራሱ ፡
ወደ ፡ መቃብሩ፡ እሱ ፡ ወዳለበት ፡
ከቶ ፡ እንዳልጠጋ ፡ ሥራውን ፡ ለማየት ፡
ከልክሎኛልና ፡ በሞት ፡ አስፈራርቶ ፤
ትእዛዙን ፡ ለመጣስ ፡ እኔ ፡አልችልም ፡ ከቶ

#አባ_ሎራ
በል ፡ ተወው፡ ልጄ ፡ ሆይ፡ ሠግቷልና፡ ልቤ
እስቲ ፡ ልመልከተው ፡ ብቻዬን፡ቀርቤ።(አባ፡ሎራሄደ)

#ቤልሻጥር ፡ (ብቻውን ) ።
ዛፍ ፡ ተደገፍኩና ፡ እንቅልፍ ወስዶኝ ፡ ኖሮ
በሕልማ፡ ሮሜዎ ፡ አድርጎ ፡ አምባጓሮ ፡
ውጊያ፡ገጠሙና ፡ የኔ ፡ ጌታ ፡ ሲጥል ፡
አየሁ፡ ደግሞ ፡ ዛሬ ፡ ሌላ ፡ ሰው ፡ ሲገድል

#አባ_ሎራ ፡(ብቻውን) ።
ይህ ፡ ደም ፡ ከየት ፡ መጣ ? ይህ ሻምላ ፡ ምንድነው?
እዚህ ፡ የወደቀ ፡ ባለቤት ፡ የሌለው ።
(ዡሊዬት ነቃች ፤ አባ ፡ ሎራ፡ ጥግ ፡ ይዞ ፡ ቆመ) ።

#ዡልዬት
ሮሜዎ ፍቅሬ ሆይ ማን አምጥቶ ጣለህ ?
ይኸ ፡ ደም ምንድነው ? ፓሪስ ፡ ማ፡ገደለህ ?
ጨርሰው ፡ አይሰሙም ፡ ሞተዋል ፡ እነሱ
ትንፋሽም ፡ የላቸው ፡ አይንቀሳቀሱ ፡
የእንቅልፍ ፡ የመኝታ ፡ የዕረፍት ፡ የጸጥታ :
መሆኑ ፡ ቀረና ፡ ሰላማዊ ፡ ቦታ ፤
ከእንቅልፌ ፡ ስነቃ ፡ አወይ ፡ መቃብሬ ፡
የጦር ፡
👍1