አትሮኖስ
281K subscribers
112 photos
3 videos
41 files
481 links
╔╦╦╦═╦╗╔═╦═╦══╦═╗
║║║║╩╣╚╣═╣║║║║║╩╣
╚══╩═╩═╩═╩═╩╩╩
ግጥሞች አዳዲስና ቆየት ያሉ የታዋቂ ደራሲያን መፅሐፍቶችን በ PDF እንዲሁንም
ያልተነበቡ ድርሰቶችን ግጥሞችን ታሪኮችን ያገኙበታል።


Contact. @atronosebot
please dont touch the leave button.😔😳😳
Download Telegram
#ሮሜዎና_ዡልዬት

#ክፍል_አራት

#ዡልዬት
ይቅርብኝ 'አትማል በውነትም ፡ በውሸት ፡
ደግሞም ፡ ልማል ፡ ብለህ፡አሳብህ ፡ ከጸና
ምን ጊዜም ፡ ጣዖቴ ፡ ፍቅሬ ፡ አንተ ፡ ነህና
በራስህ ፡ ማልልኝ ፡ የኔ ፡ ሁለንተና ።

#ሮሜዎ
እንግዲያውስ ፡ ስሚ ፡ እኔ ፡ አንቺን ፡ መውደዴ ፡

#ዡልዬት
ይቅር ፡ በቃ ፡ አትማል ፤ ተናወጠ ፡ ሆዴ ፡
ፈጥነህ ፡ ብትምልልኝ ፡ አሁን ፡ ዛሬ ፡ ማታ
ምንም ፡ አይሰማኝ ፡ ለልቤ ፡ ደስታ ፡
እንደዚህ ፡ በድንገት ፡ እንዲህ ፡ በችኰላ ፡
እንደዚህ ፡ በቶሎ ፡ የሆነ ፡ መሓላ ፡
መሠረት ፡ የለውም ፡ ይጠፋል ፡ ባንዳፍታ፤
አላፊ ፡ ነፋስ ፡ ነው ፡ የሰማይ ፡ ብልጭታ
የፍቅሩ፡ ቡቃያ ፡ ከዛሬ ፡ ጀምሮ ፡
ለምልሞ ፡ ይጠንክር ፡ በልባችን ፡ አድሮ ፡
እኛም ፡ እዚያ ፡ ድረስ ፡ሆነን ፡ ትዕግሥተኛ
ወደየቤታችን ፡ ገብተን ፡ እንተኛ ።

#ሮሜዎ
ልትሄጂ ፡ ነወይ ፡ ትተሽኝ ፡ በከንቱ ?

#ዥልየት
ይበቃል ፡ ለዛሬ ፡ መሽብን ፡ ሰዓቱ ።

#ሮሜዎ
ስጭኝ ፡ የሚያጠግብ፡አንድ ፡ ቃል ፡ የበቃ

#ዡልዬት
አንተ ፡ ሳትጠይቅ ፡ በፊት፡ዡልዬት ፡ዐውቃ
ሰጥታህ፡ወስደኸዋል፡የፍቅሯን፡ቃል ኪዳን
የተረፈው ፡ ይደር ፡ ለነገ ፡ እንዲረዳን ።

#ሮሜዎ
መልሰሽ ወስደሺው ፡'መልካሙን ፡ ስጦታ

#ዡልዬት
ቃሌን ፡ እሰጣለሁ ፡ ላንተ ፡ በችሮታ
የልቤ ፡ ደግነት ፡ ባሕር ፡ ነው ፡ ስፋቱ ፤
ፍቅሬም ፡ እንደዚሁ፡ ጥልቅ ፡ ነው ፡ ርቀቱ
መልካም ፡ ጠባዮቼ ፡ እነዚህ ፡ ሁለቱ ፡
ሰፊ ፡ ሀብት ፡ናቸው፡ ከሁሉም ፡ የላቁ ፤
ብሰጥህ ፡ ብሰጥህ ፡ ምን ፡ ጊዜም ፡ አያልቁ ።
(#ሞግዚቷ' #ጠራቻት ) ።
ጠሩኝ ፡ ድምፅ ፡ ሰማሁ ፡ በል ፡ ሄድኩኝ፡ደኅኖ፡እደር።
ሞግዚቴ ፡ እሺ ፡ መጣሁ ፤ ሮሜዎ ፡ አንድ ነገር ፡ አለ ፡ የምነግርህ፡አትሂድ፡ጠብቀኝ ፣ (ወደቤት'ግባች) »

#ሮሜዎ : (ብቻውን) "
የዛሬው ፡ ደስታ ፡ ምንኛ ፡ ደነቀኝ ።
ሕልም ፡ ነው ፡ ራእይ፡ ወይስ ' ደግሞ ቅዠት አልችልም ፡ ይህ ፡ ነገር ፡ ከቶ'ልደርስበት ፤
ፀሓዬ ፡ ጠለቀች ፡ ገባች ፡ ወደ ፡ ቤቷ ።
አሁን ፡ ተመልሳ ፡ ዳግም ፡ በመስኮቷ ፡
ብቅ ፡ እስክትል ፡ ድረስ ፡ ሆነብኝ ፡ ጨለማ ፡
ይኸው ፡ ተመለሰ ፡ የብርሃኗ ፡ ግርማ ።

#ዡልዬት ፡(ተመልሳ • መጣች
ሮሜዎ ፡ ልንገርህ ፡ የመጨረሻ ፡ ቃል ፤
እንደምታፈቅረኝ ፡ ዐወቅሁት ፡ ይበቃል ፡
ዳሩ ፡ ግን ፡ ፍቅራችን ፡ መሠረት ፡ አግኝቶ
በተክሊል ፡ ጋብቻ ፡ እንዲፈጸም ፡ ጸንቶ ፡
ትፈቅድ ፡ እንደ ፡ ሆነ ፡ እልካለሁና ፥
ነገ ፡ ሰው ፡ ወዳንተ ፡ ጒዳዩን ፡ ካጠናህ ፡
ካሰበ ፡ በኋላ ፡ መንፈስህ ፡ መርምሮ ፡
የተክሊሉ ፡ ሰዓት ፡ ይሁን ፡ በቀጠር ።
ወስነህ ፡ ላክብኝ ፤ ከዚያ ፡ በኋላ ፡ ግን ፡
ማመንታት ፡ ሳይኖረው ፡ ልቤ ፡ ሳይገነግን
ችግር ፡ ሳያግደኝ ፡ አደጋና ፡ ሞትም ፡
አንተን ፡ ተከትዬ ፡ እሄዳለሁ ፡ የትም ።
ነገር ግን ፡ ያንተ ፡አሳብ ከሌለው ፡ ንጽሕና
የማይሄድ ፡ ከሆነ ፡ እንደኔ ፡ ኅሊና ፡
አትምጣ፡ ወደኔ ፡ አትድከም ፡ በከንቱ
እንግዴህ ፡ ደኅና ፡ ሁን ፡ አለፈ ፡ ሰዓቱ '
ግባ ፡ ወደ ፡ ቤትህ ፡ ፍጠን ፡ አታመንታ ፤
ሊነጋ ፡ ነውና ፡ ይታያል ፡ ወገግታ ፡
ጨለማ ፡ ለቀቀ ፡ ብርሃን ፡ ተከፈተ ፡
ስንት ፡ ሰዓት ፡ ሲሆን ፡ ሰው ፡ ልላክ ፡ ወዳንተ ?

#ሮሜዎ
ሦስት ፡ ሰዓት ሲሆን መልክተኛሽ ፡ ይምጣ

#ዡልዬት
እንግዴህ ፡ ደኅና ፡ ሁን ፡ ፀሓይ ፡ ሳትወጣ
እንግባ ፡ ቤታችን ። (ሄደች)•

#ሮሜዎ
ዡልዬት ፡ ደኅና ፡ ሁኝ፤
ልቤ ፡ ካንቺ ፡ ጋራ ፡ መቅረቱን ፡ እመኝ ። (ሄዴ) •

#ሮሜዎና #ኣባ_ሎራ ፡ (ባባ ' ሎራ' ቤት)

#ሮሜዎ
እንደምን ፡ አድረዋል፡ አባቴ ፡ አባሎራ ?

#አባ_ሎራ
ከምሥራቅ ፡ ሳይታይ ፡ የፀሓይዋ ፡ ሥራ ፡
ማነህ ፡ በማለዳ ፡ የመጣህ ፡ ከቤቴ ?
በጣፋጩ ፡ ድምፅህ ፡ የምትል ፡ አባቴ ።
እረግ ! አንተ ፡ ነህ ፡ ወይ ፡ሮሜዎ ፡ ጐበዙ
ዐይኔ ፡ ደከመና ፡ አላየም ፡ በብዙ ፡
እንደ ፡ ምን ፡ አድረሃል ፡ የምወድህ ፡ ልጄ
ዐይንህ፡በጣም፡ቀልቷል፡ምን ነካህ ወዳጄ ?
አንድ ፡ ሰው ፡ እንደዚህ ፡ በጧት ፡ የሚነሣ
ነገር ፡ ሲያገኘው ፡ ነው ፡ እንቅልፍ ፡ የሚነሳ ፡
አሳብ ፡ የምንለው ፡ የሰላም ፡ መጋኛ ፡
መንፈሱን ፡ ሰፍሮበት ፡ እንቅልፍ ፡ የማይተኛ ፡
ሽማግሌ ፡ ሰው ፡ ነው ፤ ወጣት ፡ ግን ፡ በውኑ ፡
ከእንግዲህ ፡ ያለ ፡ ነገር ፡ ነጻ ፡ በመሆኑ ፡
ተኝቶ ፡ ያነጋል ፡ እንቅልፉን ፡ በሰላም ፤
ስለዚህ ፡ ይህ ፡ ዐይንህ ፡ በደኅናው ፡ አልቀላም ፡
ሮሜዎ ፡ ምን ፡ ሆኖ ፡ ሳይተኛ ፡ ያደረ ?
አለመተኛቱን ፡ ዐይኑ ፡ መሰከረ ።

#ሮሜዎ
እውነት ፡ ነው ፡ ነገር ፡ ግን ፡አርፌያለሁ ፡ በጣም

#አባ_ሎራ
ብታርፍማ ፡ ኖሮ ፡ በሌሊት ፡ አትመጣም ፡
ንገረኝ ፡ አትደብቅ ፡ ወዴት ፡ ነው ፡ ያደርከው ?

#ሮሜዎ
ድል ፡ አድራጊው : ፍቅሯ ፡ መንፈሴን ፡ ማረከው
አባቴ ፡ እጅዎ ፡ ተክሊሌን ፡ ይባርከው ።

#አባ_ሎራ
ያሰብከውን ፡ ነገር ፡ ንገረኝ ፡ አትፍራ ፤
ከመልካሟ ፡ እጮኛህ ፡ ከሮዛሊን ፡ ጋራ ፡
የተክሊል ፡ ቃል ፡ ኪዳን ፡ ዛሬ ፡ ልትሞላ ፡
የመጣህ ፡ መሰለኝ ፡ ሳስበው ፡ በመላ ።

#ሮሜዎ
ሮዛሊን ፡ ቀርታለች ፡ አያንሷት ፡ አባቴ ፡
ትናንትና ፡ ማታ ፡ ተመታ ፡ ደረቴ ፡
ባዲስ ፡ የፍቅር ፡ ጦር ፡ በሰላ ፡ ጐራዴ ፤
ከመውደዷ ፡ ጋራ ፡ ገጠመ ፡ መውደዴ፡
ስሜታችን ፡ እኩል ፡ ፍቅራችን ፡ የጋራ ፡
ሆኖ ፡ ከተገኘ ፡ አባቴ ፡ አባሎራ
ተክሊሉን ፡ ይሙሉልን ፡ በሥልጣንዎ ፡ ባርከው ፡
እኛ ፡ ቂም ፡ የለንም ፤

#አባ_ሎራ
መንፈሴን ፡ ኣወከው
ምን ፡ አመጣህብኝ ፡ የማላውቀው ፡ ምስጢር ፥
መላ ፡ መትቶ ፡ ያውቃል ፡ ብለህ ፡ አትጠርጥር ፤
አልገባኝምና ፡ ያሁኑ ፡ ንግግር ።
ይህን ፡ እንቆቅልሽ ፡ እንደ ፡ ሾላ ፡ ድፍን ፡
ትተህ ፡ ፡ ግለጥልኝ ፡ ነገሩን ፡ ሳትሸፍን ።

#ሮሜዎ
አባቴ ፡ አልደብቅም ፡ ሁሉንም ፡ ገልጬ ፡
ለርስዎ ፡ ልነግር፡ ነው ፡ የመጣ ፡ ሮጬ፡
የነካፑሌን ፡ ልጅ ዡለየትን ፡ ወድጄ ፤
ራሴ ፡ እስቲጠፋ ፡ በፍቅር አብጄ ፡
እሷም ፡ በጣም ወዳኝ፡አድርገን ፡ መሐላ ፡
ተስማምተን ተዋደን ከቈረጥ ኋላ ፡
አሁን 'የሚቀረን'ተክሊል ፡ የሚሞላ ፡
ካህን ፡ ስለ ፡ ሆነ የሚሰጥ፡ ቡራኬ ፡
ከሷ ጋር ፡ መጥቼ ፈትዎ' ተንበርክኬ ፡
ሞልተው 'ያሰናብቱን የተክሊሉን ፡ ሥርዐት
ሰዓቱን 'ይንገሩኝ መቼ እንደምጠራት ።

#አባ_ሎራ
አይጣል፡ነው፡እናንተ፡ የወጣቶች ፡ ወረት፤
ፍቅራቸው ፡ ቃላቸው ፡ የለውም መሠረት፡
የቀድሞ ፡ እጮኛህ ፡ ሮዛሊን 'ተረስታ፡
ሌላ ፡ ልጅ ፡ አግኝተህ አሁን ትናንት ፡ ማታ
እንዴት ተለወጠ፡ ኣሳብህ ፡ ባንድ ፡ አፍታ፡
በሮዛሊን ፡ ፍቅር ፡ ልብህ ፡ እንዲያ፡ግሎ ፡
ዘላለም ፡ የማይበርድ፡እውነተኛ፡መስሎ ፡
ታጫውተኝ ፡ ነበር አሁን ፡ ይኸውና ፡
ያ ፡ ሁሉ ፡ መውደድህ 'ከመቼው 'ቀረና ፡
መጣህ ' ባዲስ ፡ ፍቅር ፡ ልብህ ፡ ተብረክርኮ ፡
ለምታያት፡ሁሉ፡መንፈስህ ፡ ተማርኮ፡

💫ይቀጥላል💫
👍1
#ሮሜዎና_ዡልዬት

#ክፍል_አምስት

ከተሸንፍክማ ' በጕንጮቿ ፡ ቅላት '
በወገቧ ቅጥነት፡ በደረቷ፡ ሙላት'
አበድኩ ፡ ካልክማ፡ ለጥርሶቿ 'ንጣት '
ለባቷ፡ አቀራረጽ ለጠጕርዋ ፡ቀለም ፡
ፍቅርህ ፡ ባይንህ ፡ ላይ ፡ነው፤ በልብህ ፡ አይደለም ይቅር በለኝ፡ልጄ፡ ባሁኑ ፡ ወቀሣ
ለዚች ፡ ከንፈህላት፡ ያችን ' ስትረሳ ፡
አመዛዘንኩና' ሠጋሁ፡ ኣስተውዬ '
ይችንም ፡ እንደዚያች' ትረሳለህ ፡ ብዬ ።

#ሮሜዎ
አባቴ ፡ በፍጹም ፡ ይህን ፡ አይጠርጥሩ፤
የዚችና ፡ የዚያች ፡ ልዩ ፡ ነው ፡ ነገሩ
በምን ፡ ቃል ፡ ልናገር ፡ ይህን ፡ ለማሳመን
በግሪክ ፡ በሮማ ፡ በጥንታዊው ፡ ዘመን ፡
ያነቡ፡ እንደ'ነበር' የእንስሳውን ፡ ሞራ ፡
ይችሉ ፡ እንደ ፡ ሆነ ፡ አባቴ ፡ አባሎራ '
እርስዎም ፡ እንደዚሁ፡ የልቤን ፡ ብራና፡
በጥበብ ፡ አውጥተው ፡ገልጠው፡ያንቡና '
የወረት ፡ ምልክት ፡ ቢያገኙ፡ በውስጡ '
ያን ፡ ጊዜ 'ይገባል ፡ ቢንቁኝ ፡ ቢቈጡ ።

#አባ_ሎራ
መልካም ነው አመንኩህ ፡ግን ከዚህ ፡ በኋላ
አንድ ፡ ነገር ፡ አለ ፡ የሚያስቸግር ፡ ሌላ ፤
ካፑሌና ፡ ሞንታግ ፡ የናንተ ፡ አባቶች ፡ .
ወገኖቻቸውን ፡ ጨምረው ፡ ጠላቶች ፡
ባላንጦች ፡ ቂመኞች ፡ ደመኞች ፡ ሲሆኑ ፤
በየመንገዱ ፡ ላይ ፡ እንዳውሬ ፡ እያደኑ ፡
አንዱ ፡ አንዱን ፡ ሲገድለው ፡ ባይኑ ፡ ሲያየው፡ብቻ
እንዴት ፡ ሊፈጸም ፡ ነው ፡ የናንተ ፡ ጋብቻ ? .
ይኖሩ ፡ የለም ፡ ወይ ፡ ዘወትር ፡ በዘመቻ ፡
ዘለዓለም ፡ ለውጊያ ፡ ለጠብ ፡ ተሰልፈው ፡
ለቄስ ፡ ላስታራቂ ፡ ለዳኛ ፡ አሸንፈው ።

#ሮሜዎ
ይኸው፡አባቴ ሆይ ይህ ነው፡ ዋናው ነገር
በዚህ ፡ ላይ ፡ ይገባል ፡ በብዙ ፡ መማከር ፡
እውነት፡ ነው ፡ ቢኖሩ፡ ዘለዓለም ፡እነሱ፡
በጠብ ፡ ባምባጓሮ ፡ ደም ፡ እያፈሰሱ ፡
ለፍርድ ፡ ቢያስቸግሩ የቄስ ፡ ቃል ፡ ባይሰሙ ፡
እኔና ፡ ዡልዬት ፡ ግን ፡ንጹሕ ፡ ነን ፡ ከቂሙ፡
አለ ፡ ወይ ፡ አባቴ ፡ በሃይማኖት ፡ መንገድ
የሚከለክል ፡ ሕግ ፡ እኛ ፡ እንዳንዋደድ ፡
እንግዲህ ፡ አባቴ ፡ ይህንን ፡ ካወቁ ፡
ዘዴውን ፡ ለማግኘት ፡ እርስዎም ፡ ይጨነቁ ፡ቤተ ሰቦቻችን ወሬውን ፡ ሳይሰሙ
ተክሊሉን ፡ በምስጢር ፡ እርስዎ፡ ይፈጽሙ ።

#አባ_ሎራ
ይህንን ፡ ታልህማ ፡ ዘዴ ፡ ጠፍቶ ፡ ለርቁ ፡
ካህንም ፡ አልቀረም ፡ አብሮ ፡ መጨነቁ ፡
ለሁለቱ ፡ ወገን ፡ ሰላምን ፡ መልሶ ፡
ያባቶቻችሁን ፡ ክፉ ፡ ቂም ፡ ደምስሶ ፡
ስለታቸው ፡ ዘወትር ፡ የሰው ፡ ደም ፡ ከማፍሰስ ፡
እንዲቆም ፡ ለማድረግ ፡ ትንሽ ፡ እንዲታገሥ ፡
ለሻምላ ፥ ለጩቤ ፥ ለሰይፍ ፡ ለጐራዴ ፡
ከዚህ ፡ የተሻለ ፡ መች ፡ ይገኛል ፡ ዘዴ ።
የናንተ ፡ ጋብቻ ፡ ይህን ፡ ቂም ፡ አብርዶ ፤
ዕርቅ ፡ ይመሠረታል ፡ ሰላምን ፡ አውርዶ ።

#ሮሜዎ
እንግዴህ፡ አባቴ ፡ እንፍጠን ፡ በቶሎ ፡
ተክሊሉ ፡ ይፈጸም ፡ በዛሬ ፡ቀን ፡ ውሎ ፡
ጊዜና ሰዓቱን ፡ ካልተሻማን ፡ በጣም :
እንዲህ ፡ ያለ ፡ ፍቅር ፡ ዕንቅፋት ፡ አያጣም

#አባ_ሎራ
እንግዲያው ፡ መልካም ፡ ነው ፡ ኑና ፡ ባሥር ፡ ሰዓት፡
ትፈጽማላችሁ ጋብቻችሁን በስራት

#የዡዬየት_ሞግዚትና #ሮሚዎ

#ሞግዚት
መልሱን ፡ ተቀብለሽ ፡ እንድትመጪ ' ብላ
ልካኝ' እመቤቴ ፡ በቶሎ ፡ አስቸኵላ '
ይኸው ፡ መጥቻለሁ፡ መልሱን ፡ ለመቀበል ፤
ቸኩያለሁና ፡ ንገረኝ፡ ቶሎ ፡ በል ።

#ሮሜዎ
ምላሴ 'ያሞግስ ፡ አፌም ፡ ያመስግናት ፤
በውነት' ያንቺ ፡ እመቤት ፡ የተባረከች ፡ ናት
ዐመሏ ' ጠባይዋ ፡ በለጠ ' ከመልኳ፤
ቃሏን ፡ ፈጸመችው ፡ አንቺን ፡ በመላኳ
ዥሮቼ ፡ ተከፍተው 'እሰማለሁና፡
እንግዴህ ፡ ንገሪኝ የዡልዬትን ፡ ዜና ።

#ሞግዚት
ለተነጋገርነው ፡ ትናንትና ፡ ማታ ፡
እንድትልክብኝ' ያሳብህን ፡ ሁኔታ ፡
በመጠበቅ ፡ ላይ ፡ ነኝ ፡ አስታውቀኝ ፡ በቶሎ ፤
በዪና፡ ንገሪው ፤እንደዚህ ፡ ነው፡ ብሎ ፡
አሳቡን ፡ ሲነግርሽ ፡ ተቀብለሽ ፡ አምጪ፡
ብላኝ ' መጥቻለሁ ።

#ሮሜዎ
መልሴን ፡ ስትሰጪ '
እንግዲያው ፡ ንገሪያት ፡ ሮሜዎ ፡ ከልቡ ፡
ይወድሻል ፡ ብለሽ ፡ መንፈሱም ፡ አሳቡ ፡
ወዳንቺ ፡ ነው ፡ በያት ፡ ንገሪያት ፡ አደራ ፤
እስቲ ፡ ልለምንሽ ፡ እባክሽ ፡ ሳልፈራ ፡
እኔ ፡ እንደምወዳት፡ እንደዚሁም ፡ እሷ'
ትወደኝ ፡ እንደሆን ፡ ዡልዬት፡ በመንፈሷ፡
ታውቂዋለሽና ፡ እባክሽ ፡ ንገሪኝ ፡
አሳቧን ፡ ጠባይዋን 'እንዳውቀው ፡
ምከሪኝ ።

#ሞግዚት
ምንም ፡ አልደብቅህ ፡ ልንገርህ ፡ ካንዠቴ
አንተን ፡ ስታፈቅር ፡ ዝልዬት ፡ እመቤቴ'
እመነኝ ፡ ልንገርህ ፡ በውነት ፡ ከልቧ' ነው
የመስፍኑ ዘመድ፡ፓሪስ የሚባለው፡
ሊያገባት፡ ፈልጎ ፡ መሞቱ ፡ ነው ፡ ደክሞ ፡
ጨርሳ ፡ አትወደውም፡ እሷ ፡ ግን ፡ ፈጽሞ
አታንሡ፡ትላለች ፡ የሱን ፡ ስም ፡ ከፊቴ ፤
ትቈጣለችና ፡ ስቈይ ፡ እመቤቴ ፡
ልመለስ ፡ እባክህ ፡ መልሱን ፡ ስጠኝና ፤

#ሮሜዎ
አቀርብልሻለሁ'በሰፊው ፡ ምስጋና ።
እንደዚህ ' በዪና ፡ መልሱንም ፡ ንገሪያት ፤
ከቀትር ፡ በኋላ ፡ ዛሬ ፡ ባሥር ፡ ሰዓት ፡
አባ 'ሎራ፡ ድረስ ፡ አስፈቅዳ ፡ ትምጣ፤
ተናዘን ፡ ተባርከን ፡ የተክሊሉን ፡ጣጣ፡
ደብቀው ፡ በሙሉ ፡ ሊፈጽሙ፡ ቄሱ ፡
ተስማምተናል ፡ በያት ፡ ዛሬ ፡ ሊጨርሱ ።

#አባ_ሎራ #ዡልዬት #ሮሜዎ

#አባ_ሎራ
የናንተ ፡ ጋብቻ ፡ ፍጻሜው ፡ እንዲያምር ፡
ፈጣሪ ፡ ጸጋውን ፡ ምሕረቱን ፡ ይጨምር ።

#ሮሜዎ
አሳቤ ' ሞላልኝ ፡ እንግዲህ ፡ አባቴ ፡
ይህ ፡ ብቻ፡ ነበረ ፡ የቀረኝ ፡ ምኞቴ ።
ከሷ'ጋራ ፡ መጥቼ ፡ ቀርበን ፡ ከመንበሩ፡
ሥራቱን ፡ ከሞላን ፡ አለቀ ፡ ነገሩ ፡
እንግዲህ ፡ ግድ ፡ የለም የመጣ ፡ ቢመጣ

#አባ_ሎራ
ልጄ ፡ ሆይ ፡ ብዙ ነው የዚህ ዓለም ፡ ጣጣ
ለደስታ ፡ ሐዘን ፡ ለማር ፡ አለው ፡ እሬት ፤
ጠፊ ፡ ካጥፊው ፡ ጋራ ፡ ይኖራል ፡ በመሬት
ስለዚህ ፡እግዚአብሔር መጥፎውን ፡ አርቆ
ልጄ ፡ ያኑራችሁ ፡ በሰላም ፡ ጠብቆ ።

(ዡልዩት ፡ መጣች) ።

ፍቅሯንና ፡ ጌጧን ፡ በልቧ ፡ ሸፍና ፡
አልማዟ ፡ ማስተዋል ፡ ወርቋ ፡ ትሕትና ፡
ምስጢሯን ፡ ባሳቧ ፡ በጥበብ ፡ ሰውራ ፡
ይኸው ፡ መጣችልን ፡ መልካሟ ፡ ሙሽራ

#ዡልዬት
ሰላም ፡ ለርስዎ ፡ ይሁን ፡ ኣባቴ ፡ አባ ሎራ

#አባ_ሎራ
ደኅና ፡ ነሽ ወይ? ልጄ። ወጣት ፡ ሴት ፡ ወይዘሮ ፤
መልካም ፡ ጊዜ ፡ መጣሽ ፡ ልክ ፡ በቀጠሮ

#ዡልዬት
አመሰግናለሁ ፡ ለኔም ፡ ለሮሜዎ ፡
አባቴ ፡ ስለ ፡ እኛ ፡ በመቸገርዎ ።

#ሮሜዎ
እንዳንቺ ፡ እንደ ፡ እኔ ፡ በፍቅር ፡ ተሳስረው
ለመጡ ፡ ወጣቶች ፡ ሥራቱን ፡ አክብረው
ፍቅራቸውን ፡ ባርኮ ፡ በእጁ ፡ ሊቀድሰው ፡
ምን ፡ ጊዜም ፡ ሥራው ፡ ነው ፡ ካህን ፡ የሆነ ፡ሰው።

#አባ_ሎራ
እጆቹን ፡ ዘርግቶ ፡ ካህን ፡ ይጠብቃል ፤
እውነት ፡ ነው ፡ ሮሜዎ ፡ የተናገረው ፡ ቃል'
ከቤተ ፡ ክርስቲያን ፡ እንግባና ፡ በሉ ፡
ሳይዘገይ ፡ በቶሎ ፡ ይፈጸም ፡ ተክሊሉ ።

(ቤተ ፡ ክርስቲያን'ገቡ)

(#በቬሮና #ከተማ' #መንገድ) •

#ሜርኩቲዎ #ቤንቮሊዎ ፡ አንድ ፡ የእልፍኝ #አሽከር

#ቤንቮሊዎ
ሜርኩቲዎ ፡ እንሂድ ፡ የካፑሌ ፡ ሰዎች ፡
ይጠፉ ፡ አይመስለኝም በነዚህ መንደሮች
ድንገት ፡ ብንገናኝ ፡ ኋላ ፡ ጠብ ፡ ይነሣል ፤
ደግሞ ፡ ጠብ ሲነሣ ፡ ጸጥታ ፡ ይፈርሳል ፡
ብንሸሽ ፡ ይሻላል ፡ ከዚህ ፡ ሁሉ ፡ ጣጣ ።

#ሜርኩቲዎ
እነሱም ፡ አስበው ፡
👍1
#ሮሜዎና_ዡልዬት


#ክፍል_ስምንት


#ሞግዚት
የተሠራውን ፡ ጉድ ፡ እንግዲህ ፡ ዕወቂው
እርገሚው ፡ ሮሜዎን ፡ ከልብሽም ፡ ናቂው
በቀልሽን ፡ ቂምሽን ፡ አድርጊው ፡ የጸና ፤
በውነቱ ፡ ሮሜዎ ፡ ሰው ፡ አይደለምና ።
አብነት ፡ ይሁንሽ ፡ ይህ ፡ መጥፎ ፡ ደመኛ
ሰውን ፡ አትመኝ ፡ እንግዲህ ፡ ዳግመኛ ፡
ፍቅሩም ፡ደግነቱም ፍሬ ቢስ ፡ ነው ፡ ከንቱ
ፈጽሞ ፡ ሰው ፡ የለም መጥፎ ፡ነው ፡ ሰዓቱ
እንዲህ ፡ ያለ ፡ ነገር ፡ ሮሜዎ ፡ ሲሠራ ፡
ማነው ፡ የሚታመን ? ማነው ፡ ባለአደራ ?

#ዡልዬት
ምንም ፡ አልተገኘ ፡ የሚበጀኝ ፡ ለኔ ፤
ሁለት ፡ ስለት ፡ ያለው ፡ ሰይፍ ፡ ነው ፡ ኀዘኔ
ቲባልት ፡ ባይሞት ኖሮ ሮሜዎ ፡ ይሞታል፤
ቲባልት ፡ ባይሸነፍ ፡ ሮሜዎ ፡ ይረታል!
ሮሜዎን ፡ ከልብሽ ፡ ትይኛለሽ ፡ ጥዪው ፤
ምነው ልቤን ገብተሽ መርምረሽ ብታዪው
ለኔም ፡ገዳይ ፡ ቢሆን ፡ ለናቴም ፡ ላባቴ ፡
ሮሜዎን ፡ ለመጥላት አይችልም ፡አንጀቴ
ቲባልትም ፡መጥፎ ነህ ፡ሮሜዎም አትረባ
መሪር ፡ ነው ፡ ከናንተ ፡ የሚተርፈኝ ፡ እንባ
ባሌ ፡ ካገር' ወጣ ፤ቲባልት ፡ ሞተ ፡ በፊት፤
ሐዘኔ ፡ ዐጓጕል ፡ የሌለው ፡ መድኀኒት ፡
እንደ ምን ፡ አድርጌ ደግሞስ ፡ እስከ መቼ
እኖራለሁ ፡ እኔ ፡ እናንተን ፡ አጥቼ ፡
ከቲባልት ፡ መሞት ፡ ሮሜዎ ፡ ስደቱ ፡
ከሮሜዎ ፡ ስደት ፡ ቲባልት ፡ መሞቱ ፡
ቢሆን ፡ ምን ፡ ቸግረው ፡ ሐዘኔ ፡ በተራ ፤
ለማንኛው ፡ ላልቅስ ፡ ወይ ፡ የኔ ፡ መከራ !
ዛሬ ፡ በሠርጌ ፡ ቀን ፡ ደስ ፡ብሎኝ ፡ መዋሌ
ቀረና ፡ ሰው ፡ ገድሎ ፡ እንዲሰደድ ፡ ባሌ '
ቲባልትም ፡ እንዲሞት ፡ አድርጎ ፡ ዕድሌ ፡
ሐዘን ፡ ከሆነ ፡ ለኔ ፡ የደገሰው ፡
ልቤ ፡ ሳያደላ ፡ እንባዬን ፡ ላፍስሰው ።

#ሞግዚት
በእውነት፡ሴት ልጅ ባሏን፡ከወደደች አይቀር
እንዳንች ፡ አድርጎ ፡ ነው ከልቡና ማፍቀር
ከልብ ፡ አዘንኩልሽ ፡ በጣሙን ፡ አድርጌ ፤
አለበት ፡ ገብቼ ፡ ሮሜዎን ፡ ፈልጌ ፡ .
እኔ ፡ አመጣዋለሁ ፡ እንባሽን ፡ አድርቂው
እመኝታ ፡ ቤትሽ ፡ ግቢና ፡ ጠብቂው ።
በስደተኛነት ፡ ሳይሄድ ፡ ነገ ፡ ርቆ ፡
ተሰነባበቱ ፡ ይምጣ ፡ ተደብቆ ።

#ዡልዬት
መልካም ፡ ነው ፡ ሞግዚቴ ፡ሙሽራ ፡ ሲገባ
አጊጦ ፡ ታጅቦ ፡ በዘፈን ፡ ባበባ ፡
በወግ ፡ በማዕርግ ፡ ባለም ፡ በደስታ ፡
በክብር ፡ ነበረ ፡ በብዙ ፡ እልልታ ፤
ሌሊት ፡ ጨለማውን ፡ ከለላው ፡ አድርጎ ፡
የኔ ፡ ሙሽራ ፡ ግን ፡ ይግባ ፡ ተሸሽጎ ።
እንቢ ፡ ብሎ ፡ እንዳይቀር ፡ጠርተሽ ፡ ስታመጪው
እንቺ ፡ ለምልክት ፡ቀለበቴን ፡ ስጪው ፡
(ቀለበቷን ፡ ሰጠቻት)

#አባ_ሎራ (ባባ ሎራ ፡ ቤት)
ሮሜዎ ፡ ብቅ ፡ በል ፡ውጣ ፡ ከጨለማ ፤
የፍርዱን ፡ ቃል ፡ ይዤ ፡ መጣሁ ልጄ ስማ

#ሮሜዎ
ሳልሰማው ፡ ቢዘገይ ፡ ይሻለኝ ፡ ነበረ ፤
ፍርዱ ፡ ምን ፡ ዐይነት ነው ? ልቤ ፡ ተሸበረ

#አባ_ሎራ
መስፍኑ ፡ ፈቀደ ፡ በቀላል ፡ ሊቀጣ ፤
የሞት ፡ ፍርድ ፡ ቀርቶ ፡ካገር ፡ እንድትወጣ

#ሮሜዎ
ጨካኝ ፡ ቅጣት ፡ እንጂ ፡ ከሞትም ፡ የከፋ
ይህ ፍርድ መሪር ነው ያስቈርጣል ፡ ተስፋ
ዥልዬት ፡ ካለችበት ፡ ከተማ ፡ ወጥቼ ፡
ስደተኛ ፡ ሆኜ ፡ አገሬንም ፡ ትቼ ፡
የምኖረው ፡ ኑሮ ፡ እንደ ፡ ምን ፡ ይገፋል ፣
ቀኑና ፡ ሰዓቱ ፡ ደቂቃው ፡ መች ፡ ያልፋል ፡
እንዴት ፡ እችላለሁ ፡ ዡልዬትን ፡ ለመርሳት
ሲኦል ፡ ነው ፡ ኵነኔ ፡ ሞት ፡ገሃነመ ፡ እሳት

#አባ_ሎራ
ደስታህ ፡ ቀረና ፡ በማመስገን ፡ ፈንታ ፡
ለምን ፡ ትረሳለህ ፡ የእግዜርን ፡ ውለታ ፡
ዐዋጁ ፡ የሚያዘው ፡ የሞት፡ ቅጣት ፡ ነበር'
ለምን ፡ አታስብም ፡ ይህን ፡ ትልቅ ፡ ነገር ፡
ሄደህ ፡ ብትቀመጥ ፡ በማንቱ ፡ ከተማ ፡
አገሩ ፡ ጥሩ ፡ ነው ፡ በጣም ፡ የሚስማማ
ልጄ ሆይ ፡ ቅጣቱ ፡ በጣም ፡ የቀለለ ፡
ጥሩ ፡ ነው ፡ ሺ ፡ ጊዜ ፡ ከሞት ፡ የተሻለ ።

#ሮሜዎ
ያስቡት ፡ አባቴ ፡ ነገሩን ፡ ያስተውሉት ፤
ምኑን ፡ ነው እርስዎ ቀላል ነው ፡ የሚሉት

#አባ_ሎራ
ብስጭት ፡ አታብዛ ፡ በጣም ፡ አትናደድ ፤
ከመሞት ፡ ይሻላል ፡ ሺ ፡ ጊዜ ፡ መሰደድ
ልጄ ፡ ዓለም ፡ሰፊ ፡ ነች ወጥተህ ከቬሮና
የትም ፡ ሄደህ ፡ መኖር ፡ ትችላለህና ።

#ሮሜዎ
ወጥቼ ፡ ከሄድኩኝ ፡ እኔ ፡ ከቬሮና ፡
ውሸት ፡ ነው ፡ አባቴ ፡ ምን ፡ዓለም ፡ አለና፡
ሕይወት ፡ ነው ፡ አይበሉት የምኖረው ኑሮ
ዓለም ፡ እዚህ ፡ ቀረ ፡ ከሚስቴ ጋር አብሮ'
ሰው ነህ እንስሳ ዕንጨት አበባና ፡ቅጠል ፡
ፀሐይ ፡ ተከልሎ ፡ አየር ፡ ሳይቀበል ፡
የኖረ ፡ እንደ ፡ ሆነ ፡ ይሞታል ፡ ይደርቃል፤
ለኔም ፡ እንደዚህ ነው ፡ ስደት የሚሉ፡ ቃል
አገሬ ፡ ንብረቴ ፡ አየሬ ፡ ፀሓዬ ፡
ዓለሜ ፡ ትንፋሼ ፡ ሕይወቴ ፡ ሰማዬ ፡
የነበረችውን ፡ ዝልዬትን ፡ አጥቼ ፡
እሷ ፡ ካለችበት ፡ ከተማ ፡ ወጥቼ ፡
መሄዴ ፡ ከሆነ ፡ እሷም ፡ ከኔ ፡ ርቃ ፡
ነጣጥለው ፡ ከለዩን ፡ የኔ ፡ ነገር ፡ በቃ ።
ሕይወቴም ፡ ኑሮዬም ፡ ሞተ ፡ ተበላሸ ፤
ደስታ ፡ ተለየኝ ፡ ከኔ ፡ ርቆ ፡ ሸሸ ፡
እንግዲህ ፡ መቆሜ ፡ ለምንም ፡ አይበጅ ፤
ይህን ፡ኑሮ ፡አይበሉት መናወዝ ነው እንጅ
ፍርድ ፡ ማሻሻያ ፡ የተባለው ፡ ዘዴ ፡
ከመርዝም ፡ ይብሳል ፡ ከጦር ፡ ከጐራዴ '
ስደት ፡ የሚሉ ፡ ቃል ፡ ጨለማ ነው ፡ ገደል
እኔን ፡ አስጨንቆ ፡ መጣ ፡ ለመግደል ።

#አባ_ሎራ
እረ ፡ ስማኝ ፡ ልጄ ፡ ምክሬንም ፡ ተቀበል ፡
ሞትና ፡ መሰደድ ፡ እኩል ፡ ነው ፡ አትበል

#ሮሜዎ
ተመልሰው ፡ ስደት ፡ ወደሚባለው ፡ ቃል ፡
ሊመጡ ፡ ነውና ፡ አባቴ ፡ ይበቃል ፡
ምን ፡ አደከመዎት ፡ በቃ በዚህ ፡ ዓለም ፡
እኔን ፡ የሚያጥናና ፡ ምንም ፡ ነገር ፡ የለም
ከሞት ፡ የባሰ ፡ ነው ፡ የመከራ ፡ ጭቃ ፤
የሮሜዎ ፡ ነገር ፡ ተከተተ ፡ በቃ ።

#አባ_ሎራ
ዐውቃለሁ ፡ እንዲሆን ፡ ስደትህ ፡ መራራ ፤
ግን ፡ መድኀኒት ፡ አለው ለዚህ ፡ ለመከራ'
ዕረፍት ፡ እንድታገኝ ፡ ባሳብ ፡ በኅሊና ፡
የደረሰብህን ፡ ጭንቅህን ፡ እርሳና ፡
ልብህን ፡ መልሰው ፡ ወደ ፡ ፍልስፍና ።

#ሮሜዎ
ዡልዬትን ፡ ፈጥሮልኝ ካልሰጠኝ ፡ አምጥቶ
የመስፍኑን ፡ ብይን ፡ በጥበብ ፡ አጥፍቶ ፡
እኔን ፡ ካላዳነኝ ፡ የርስዎ ፡ ፍልስፍና ፡
ለምንም ፡ አይበጀኝ ፤ የለውም ፡ ርባና ።
(የዡልዬት'ሞግዚት'ከደጅ'ሆና'በር መታች)

#አባ_ሎራ
ተነሣ ፡ ሮሜዎ ፡ ግባ ፡ ወደ ፡ ጓዳ ፤
ስማ ፡ በር ፡ ይመታል ፡ መጣብን ፡ እንግዳ
ተደበቅ ፡ በቶሎ ፡ ጥግ ፡ ይዘህ ወደ ፡ ጐን
ይይዙሃልና ፡ ያገኙህ ፡ እንደሆን ።
(በሩ ይመታል)

#ሮሜዎ
በስደት ፡ ከሆነ ፡ እኔ ፡ የምቀጣ ፡
ምን ፡ ያስጨንቀኛል ፡ የፈቀደው ፡ ይምጣ

#አባሎራ
ለምን ፡ ትሆናለህ ፡ አንተ ፡እንደዚህ ፡ ደረቅ
እባክህ ፡ ግባና ፡ በቶሎ ፡ ተደበቅ ፡ (ሮሜዎ ሄደ)
እንዲህ ፡ ባሁን ፡ ሰዓት ፡ የመጣ ፡ በማታ ፡
ማነው ፡ በጨለማ ፡ በሬን ፡ የሚመታ ?

#ሞግዚት
መጥቻለሁና ፡ ልካኝ ፡ እመቤቴ ፤
የዡልዬት ፡ ሞግዚት ፡ ነኝ ያስገቡኝ ፡ አባቴ

#አባሎራ
እንኳን ፡ ደኅና መጣሽ ፡ ነይ ግቢ ወዳጄ፤
(ከፍተውላት ገባች)

#ሞግዚት
ሮሜዎን ፡ አጣሁት ፡ ብፈልገው ፡ ሄጄ ።
ይንገሩኝ ፡ አባቴ ፡ ከመሸ ፡ አሁን ፡ ማታ
አይተው ፡ እንደ ፡ ሆነ ፡ ያለበትን ፡ ቦታ ፡

#አባሎራ
በሐዘኑ ፡ ሰክሮ ፡ ያለቅሳል
👍1
#ሮሜዎና_ዡልዬት


#ክፍል_ዘጠኝ


#አባ_ሎራ
ለምን ፡ ታስባለህ ፡ እንዲህ ፡ ያለ ፡ ነገር ፤
ብላሽ ፡ ሰው ፡ አትሁን ፡ ሲመክሩህ ፡ ተመከር ,እንደ ፡ ሴት ፡ አታልቅስ ፡ እንዳውሬ ፡ አትቈጣ
እንደ፡እብድ፡አትበሳጭ ፥ ከሰው፡ ግብር፡ አትውጣ
ትመስለኝ ፡ ነበረ ፡ በውነቱ ፡ ጠንካራ ፤
ሰው ፡ ለምን ፡ ይረባል ፡ ካልቻለ ፡ መከራ
መቀጣት ፡ ከወደድህ ፡ በገዛ ፡ እጅህ ፡ ሞተህ ፡
ስለምን ፡ ገደልከው ፡ ቲባልትን ፡ ተዋግተህ ?
በገዛ ፡ እጅህ ፡ ብትሞት ፡ ባለማመዛዘን ፡
መግደልህ ፡ እኮ ፡ ነው ሚስትህን ፡ በሐዘን '
ለዚህ ፡ ነው ፡ ልጄ ፡ ሆይ ፡ ኅሊናና ፡ አእምሮ ፡
ከእግዜር ፡ የተሰጠ ፡ ለሰው ፡ ልጅ ፡ ተፈጥሮ'
ዡልዬት ፡ ጠልታኛለች ፡ ብለህ ፡ ስትሠጋ፡
ሰው ፡ ልካ ፡ ጠራችህ ምሕረትን ፡ አድርጋ
ቲባልት ፡ ሊገድልህ ፡ ቢመጣ ፡ ደንፍቶ ፡
በገዛ ፡ ጥጋቡ ፡ ወደቀ ፡ ተወግቶ "
ባንተም የሞት ቅጣት ሊወድቅ የነበረው
በስደት ፡ ለውጦ ፡ መስፍናችን ፡ ሻረው '
ብትመለከተው : በውነቱ ፡ የት ፡ አለ ፤
እንዳንተ ፡ የቀናው ፡ በጣም ፡ የታደለ ፡
ተጠንቀቅ ፡ በውነቱ ፡ ልጄ ፡ በጣም ፡ ሥጋ
ሳታውቀው ፡ ብትቀር ፡ የደስታን ፡ ዋጋ ፡
ኑሮህ ፡ይበላሻል ፡ አለመጠን ፡ ፍራ ፡
ምን ፡ጊዜም ፡ አይለቅህ ፡ ጭንቅና ፡ መከራ ።
ሚስትህን ምከራት ፡ እንዳትሞት ፡ አልቅሳ
መምሸቱ፡ነውና፡ በል ቶሎ ፡ ተነሣ፡
ነገ ፡ ግን ፡ ለመሄድ ፡ ልብህ ፡ይሰናዳ ፤
ውጣ ፡ ከቬሮና ፡ ሌሊት ፡ በማለዳ
ተዛውረህ ተቀመጥ ፡ ሄደህ ፡ ወደ ፡ ማንቱ
እኛ ፡ ጊዜ ፡ አግኝተን ፡ ሲመቸን ፡ ሰዓቱ ፡
ወገኖቻችሁን ፡ በምክር ፡ አስታርቀን ፡
ጋብቻችሁንም ፡ በገሃድ ፡ ኣስታውቀን ፡ .
ላንተም ፡ ከመስፍኑ ፡ ምሕረትን ፡ ጠይቀን
እንጣጣራለን ፡ ቶሎ ፡ እንድትመለስ
እግዜር ፡ይጠብቅህ በል እስከዚያ ፡ ድረስ
አሁን ፡ ወደ ፡ ዡልዬት ፡ በቶሎ ሂድ ፡ ተነሥ

የካፑሌ ሚስት #ካፑሌ #ፓሪስ

#ፓሪስ
ጉዳዩ ዘገየ ፡ በመዋል' በማደር ፤
ታዲያስ እንዴት ፡ ሆነ ፡የጋብቻው ፡ ነገር ?

#ካፑሌ
ነገሩን ፡ ለዡልዬት ፡ ሳልነግር ፡ መቅረቴ ፡
ወድጄን ፡ አይደለም ፡ እንዲህ ፡ መዘግየቴ
በቲባልት ፡ መሞት ፡ አዝናለች ፡ በብርቱ ፤
ታፈቅረው ፡ ነበረ ፡ ከልቧ ፡ በውነቱ ፡
ስለዚህ ፡ ሐዘኑ ፡ ጥቂት ፡ ሳይረሳ ፡
አልቻልኩም ፡ ጕዳዩን ፡ ለጊዜው ፡ ላነሣ ፡
አድርግልኝና ፡ ከልብህ ፡ ይቅርታ ፤
እኔ ፡ እጨርሳለሁ ፡ ነገሩን ፡ አንድ ፡ አፍታ

#ፓሪስ
እውነት ፡ ነው ሐዘኑ ፈጽሞ ፡ አልተመቸም
ተስማምተንበታል ይህን ጕዳይ ፡ መቼም
እሷም እንቢ እንዳትል ፡ እናንተ ፡ አስቡበት

#የካፑሌሚስት _ ።
ግድ የለም ሠርጋችሁ ይሆናል በፍጥነት

#ካፑሌ
ፓሪስ ሆይ አትሥጋ አይዞህ ይህን ጕዳይ
መሄድ ፡ ትችላለህ ፡ ጥለኸው ፡ በኔ ፡ ላይ
እንዴት ፡ ትወጣለች ፡ ከኔ ፡ ፈቃድ ፡ ልጄ ፤
ያቀረብኩላትን ፡ መርጬ ፡ ወድጄ
ያላንድ ፡ ቅሬታ ፡ አለባት ፡ መቀበል ፤
እንዲያውም ፡ እንፍጠን ፡ ዛሬ ነገ ፡ አንበል
በይ ፡ ፍጠኝ ፡ ሚስቴ ፡ ወደ ፡ ልጅሽ ፡ ሂጂ
በዘዴ ፡ በርጋታ፡ነገሩን አስረጂ ፡
መልካሙ ፡ ልጃችን 'ፓሪስ ፡ አንቺን ፡ ወዶ ፡
እኔም ፡ ደስ ፡ ብሎኝ ፡ አባትሽም ፡ ፈቅዶ ፡
ይኸው ፡ በዚህ መሰሞን ሊያገባሽ ፡ ነውና
ተዘጋጂ፡ በያት ፡ በሙሉ ፡ ልቡና '
በል ፡ አንተም ፡ ንገረኝ ፡ እንደምትፈልገው
ሰርጉ ፡ እንዲፈጸም ለመቼ እናድርገው ?

#ፓሪስ
እንደ ፡ እኔ ፡ ሰርጋችን ፡ የራቀ ፡ ከሚሆን ፡
ቢፈጸም ፡ ይሻላል ፡ አሁን ፡ በዚህ ፡ ሰሞን

#ካፑሌ
እንግዲያው መልካም ነው ባጭር እንደግስ
ተክሊሉም ፡ ይፈጸም ፡ በሚመጣው ፡ ኀሙስ ፡
ጃጃታ ፡ አላበዛም ብዙም ፡ ሰው ፡ አልጠራ ፤
ልጄን ፡ እድራለሁ ፡ ብዬም ፡ አላወራ ፡
ሐዘን ፡ ስለ ፡ ሆነ ፡ቲባልት፡ በመሞቱ ፡
ቅር ፡ ያሰኛልና ፤ ዘመድ ፡ በጥቂቱ ፡
በድብቅ ፡ እንጥራ ፡ ነገር ሳናበዛ ፤
እንደዚህ 'ብናደርግ ፡ ወሬው ፡ ሳይነዛ ፡
ጉዳያችን'ያልቃል፡ያግር፡ ሰው ፡ ሳይሰማ ፤
እንግዲህ ፡ መልካም ፡ ነው ፤ በዚሁ 'እንስማማ ።

#ፓሪስ
እኔም ፡ እስማማለሁ ፡ ይሁን ፡ በዚሁ ፡ ቀን
በሉ ፡ እስከዚያው፡ድረስ፡እግዜር፡ይጠብቀን ። (ሄዳ).

#ካፑሌ ፡ (ለሚስቱ )
እንደዚህ ፡ ያለ ፡ ባል ፡ ትልቅ ፡ ሰው ፡ የበቃ
ቢሄዱ ፡ አይገኝም ፡ እግር ፡ እስቲነቃ ፡
በይ ፡ ቶሎ ፡ ፍጠኚ ፡ ወደ ፡ ልጅሽ ፡ ሂጂ ፤
ነገ ፡ ጧት ፡ አሳቧን ፡ ልቧን ፡ አዘጋጂ ።

#ሮሜዎና #ዡልዬት ፡ (በዥልዬት ' መኝታ ፡ ቤት) ።

#ዡልዬት
አይዞህ፡አትቸኵል ፡ አልነጋም ፡ ሌሊቱ ፤
ቁጭ ፡ በል ፡እናውጋ ፡ ገና ፡ ነው ፡ ሰዓቱ ፡
ተመልከት ጨለማ መሬቱን
ሲሸፍን ፡
የሰማናትም ፡ ወፍ ፡ አሁን ፡ ስትዘፍን ፡
ዞትር ፡ ልማዴ ፡ ነው ፡ ሌሊቱ ፡ ሳይነጋ ፡
መጮህ ፡ ትወዳለች ፡ እመነኝ ፡ አትሥጋ

#ሮሜዎ
ይህች ፡ የንጋት ፡ ወፍ ፡ ነች ፡ አሁን ፡ የጮኸችው ፤
ትክክል ፡ ይታያል ፡ ዡልዬት ፡ ተመልከችው
ሰማይ ወገግ፡ አለ ፡ ያው በምሥራቅ በኩል ፤
ሰዓቱ ፡ ደረሰ ፡ እንግዴህ ፡ ልቸኵል ፡
በቬሮና ፡ አድሬ ፡ ቢያገኙኝ ፡ ሳልወጣ ፡
መስፍኑ ፡ ፈርደዋል ፡ በሞት ፡ እንድቀጣ ፡
ልዳን ፡ ያልኩ ፡ እንደሆን ፡ ሕይወቴን ፡ ወድጄ ፡
መሄድ ፡ ይገባኛል ፡ አሁን ፡ ተሰድጄ ።

#ዡልዬት
እኔ ፡ መች ፡ አጣሁት ፡ ይህ ፡ ያሁኑ ፡ ብርሃን ፡
የሰማይ ፡ ፋና ፡ ነው ፡ የኮከብ ፡ ውጋጋን
ሌሊት ፡ በጨለማ ፡ ሳይነጋ ፡ ሌሊቱ ፡
ለምን ፡ ትሄዳለህ ፡ አሁን ፡ ወደ ፡ ማንቱ ፡
አይዞህ ፡ እንጫወት ሌቱ ፡ አልነጋም ፡ ገና
ጊዜ ፡ አለን ፡ እስኪታይ ፡ የንጋቱ ፡ ፋና ።

#ሮሜዎ
ዘፈኑ ፡ ሲወጣ ፡ አልሰማንም ፡ ካፍ
አልነጋም ፡ ሌሊቱ ፡ አልጮኸችም ፡ ወፍ፡
ይህም ፡ በሰማይ ላይ የሚታይ ፡ ውጋጋን አይደለም ፡ የመጣ ፡ ከፀሓይዋ ፡ ብርሃን ፡
ብለን ፡ እንካደው ፤ አምኜ፡ ልቀበል !
ሳልወጣ ፡ ይያዙኝ ፡ ተይዤም ፡ ልገደል "
ካንቺ ፡ ተለይቼ ፡ የሐዘን ፡ ኵነኔ ፡
ከሚያገኘኝ፡ መሞት ፡ እመርጣለሁ ፡ እኔ ።
አልፈራም ፡ ፈጽሞ ፡ በሞት ልቀጣ
ዡልዬት ፡ ከፈቀደች ፡ የፈለገው ፡ ይምጣ ፡
ወፎች አልተንጫጩም ሌሊቱም ፡ አልነጋ
ዡልዬት ጨዋታ አምጪ እንግዴህ እናውጋ፡

#ዡልዬት
እኔ ፡ ብዬ ፡ ነበር ፡ ገና ፡ ነው ፡ ሌሊቱ፤
አሁን ፡ ገና ፡ታየኝ ፡ ትክክል ፡ መንጋቱ ፡
ንጋት ፡ ነው ፡ የመጣው ፡ ሂድ ፡ ቶሎ ፡ ተነሣ፤
አምልጠህ ፡ ሽሽ ፡ ቶሎ ፡ ብረር ፡ በግሥገሣ ፡
እየው ፡ ተመልከተው ፡ የንጋት ፡ ወገግታ፤
ጨለማውን ቀዶ፡ ሄደ ፡ እየበረታ ፡
አስተውለው ፡ መሬቱ ፡ ሲታየን ፡ ተገልጦ ፤
አሞኘችኝ፡ ወፏ ድምፅዋ ፡ ተለውጦ ፡
ፍጠን ፡ ቶሎ ውጣ እየው፡እንደ፡ ነጋ ፤
ተነሥ ፡ ቶሎ ፡ ጥፋ፤ አይንካህ ፡ አደጋ ።

#ሞግዚት
እናትሽ ፡ ነቅተዋል' እመቤቴ ፡ ዕወቂ፤
መንጋቱ ፡ ነውና ' በጣም' ተጠንቀቂ "
ደኅና ሰንብት ፡ ልበል ፡ እኔው ፡ አስቀድሜ
እንግዴህ ፡ ደኅና'ሁን'ሮሜዎ ፡ ወንድሜ ።

#ሮሜዎ
ዡልዬት ደኅና ሁኝ ፡ ደኅና ሰንብች ፡ ፍቅሬ

#ዡልዬት
አደራ ፡ እንዳገኘው ፡ እኔ ፡ ያንተን ፡ ወሬ ፡
ሁል ፡ ጊዜ ጻፍልኝ ፡ መሆንህን ፡ ጤና ፤
መቼ ፡ እንደማገኝህ ፡ አላውቀውምና ።

#ሮሜዎ
መቼም ፡ ቢሆን ፡ ካንቺ ፡ አይለይም ፡ ልቤ
እጽፍልሻለሁ ፡ ሁል ፡ ጊዜ ፡
#ሮሜዎና_ዡልዬት


#ክፍል_አስራ_አንድ

#አባ_ሎራና#ዡልየት

#ዡልዬት
ይዘኑልኝ ፡ በጣም ፡ አባቴ ፡ አባሎራ
በኔ ፡ ላይ ፡ ዘንድሮ ፡ የመጣው ፡ መከራ ፡
ፍጻሜ ፡ የለውም ፡ ቈርጫለሁ ፡ ተስፋ፤
ይርዱኝ ፡ እባክዎ ፡ ጨርሼ ፡ ሳልጠፋ ።

#አባ_ሎራ
አዝኛለሁ ፡ ልጄ ፡ ነገሩን ፡ ሰምቼው ፤
አሁን ፡ መጥቶ ፡ ነበር ፡ፓሪስን ፡ አግኝቼው
ተክሊሉን ፡ ለናንተ ፡ ኀሙስ ፡ እንድሞላ ፡
ለምኖኝ ፡ ነበረ ፡ እንዲህ ፡ በችኰላ ፡
እንደ ፡ ምን ፡ ይሆናል ፡ብዬ ፡ መለስኩለት፤
በነገሩ ፡ በጣም ፡ አዝኛለሁ ፡ በውነት ።

#ዡልዬት
እንግዲያው ፡ ከሰሙት ፡ እንሆ ፡ ችግሬ ፤
ሥቃዬ ፡ የጠና ፡ ብርቱ ፡ ነው ፡ አሳሬ
እሄድ ነበር በውነት ሴት፡ ባልሆን' ጠፍቼ
ለፓሪስ ፡ ሊድሩኝ፡ቈርጠው 'ዘመዶቼ
አስጨንቀው ያዙኝ'ይኸው ፡በግዴታ፤
አባትም እናትም የምድር'ሁሉ፡ ጌታ ፡
እግዜር ' የዳረውን ፡ አይችልም ሊያፋታ ።
እኔና 'ሮሜዎን ፡ ሁለቴ ' ሲድረን '
በፊት፡ በጥበቡ' ከልብ' አፋቀረን ፤
ቀጥሎ ፡ በርስዎ ፡ በካህኑ' ሥልጣን ፡
ባርኮ ፡አገናኘን' በተክሊል ፡ ቃል፡ ካዳን ።
አባቴና እናቴ ፡ ይህን ፡ አላወቁ ፤
ለፓሪስ ፡ ሊድሩኝ 'እንሆ 'ታጠቁ '
እንግዴህ ፡ አባቴ ፡ እርስዎ ፡ ከግዜር ፡ ጋራ
በርትተው ፡ ያድኑኝ ፡ ከዚህ ፡ ከመከራ ፡
የማይቻል ፡ ሆኖ ፡ ካልተገኘ ፡ ዘዴ !
ብልሃቱን ፡ መፈለግ ፡ አለብኝ ፡ በግዴ ፡
ይኸው ፡ በዚህ ፡ ጩቤ ፡ ሆዴን ፡ እቀድና ፡
እገላገላለሁ ፡ ከዚህ ፡ ከፈተና

#አባ_ሎራ
ኀጢአቱ ፡ትልቅ ነው ከነፍስ ፡ የሚያስቀጣ
በገዛ ፡ እጅሽ ፡ መሞት ባሳብሽ ፡ አይምጣ
ፓሪስን ለማግባት ልብሽ ፡ ካልፈቀደ
ይህን 'ያኽል፡ በውነት ፡ ሆድሽ ፡ ካልወደደ
ግልጥ ፡ አድርጊና ፡ ንገሪኝ አትፍሪ

#ዡልዬት
እግዚአብሔር ብቻ ነው መንፈስን መርማሪ
ፓሪስን ፡ ከማግባት ፡ በውነቱ ፡ አባቴ ፡
አሁን ባሁን ፡ ፈጥኖ፡ ይምጣ ጊዜ፡ ሞቴ ፡
ልገረፍ ልሰቀል ፥ በሥቃይ ፡ ልገደል ፤
ወስዳችሁ ፡ ወርውሩኝ ጣሉኝ ወደ ፡ ገደል
የትም ፡ ተረስቼ ፡ ልዋረድ ፡ ልጕላላ ፤
ብትፈልጉ ፡ ዳሩኝ ፡ ለዱር ፡ ወሮ ፡ በላ '
ከዥብ ፡ ጋራ ፡ እሰሩኝ ፡ ከነብር ፡ ካንበሳ ፤
ካፅም 'ጋራ ፡ ቅበሩኝ፣ ከትኵስ'ሬሳ፡
እሳት አንድዳችሁ፡ አሁን ፡ ከቶ ፡ ነፍሴ ፡
አቃጥሉኝ ፡ በቁሜ ፡ ከእግር እስከ ፡ ራሴ
ወደ ፡ አራዊት ፡ ጐሬ ጣሉኝ ፡ ወዶ ፡ ዋሻ ፣
ሮሜዎ ከቀረ ምንም ፡ ባል እልሻ

#አባ_ሎራ
እኔም ፡ ባንቺ፡ነገር፡እጅግ፡ተጠብቤ
ልጄ ፡ ሆይ ፡ሐዘንሽ ተሰማኝ፡ ለልቤ ፡
የሚቻልሽ ፡ ቢሆን ፡ ልብሽ ፡ የሚደፍር ፡
አድምጭኝ ልጄ ሆይ ልስጥሽ አንድ ምክር
አሁን ፡ ተመልሰሽ ፡ ስትገቢ ፡ ከቤትሽ ፡
እንደዚህ ፡ በዪና ፡ ንገሪው ፡ ላባትሽ ፡
« ፈቃድህን ፡ ልፈጽም ፡ ፓሪስን ፡ አግብቼ፡
« መጥቻለሁና ፡ ይኸው ፡ ተጸጽቼ ፡
« እንግዴህ ፡ ይደገስ ፡ ሰርጉ ፡ ይሰናዳ »
አባትሽ ፡ ይህነን ፡ ነግረሽው ፡ ሲረዳ '
ይታረቃል ፡ ካንቺ ፡ መንፈሱም ፡ ይረጋል ፤
ከንዴቱ ፡ በርዶ ፡ ይቅርታ ፡ ያደርጋል ።
እኔም ፡ የምሰጥሽ ፡እግዚአብሔር ፡ ቢረዳ
አንድ፡ መድኀኒት ነው ምንም ፡ የማይጎዳ ፡
ልብስሽን ፡ አውልቀሽ ፡ ስትተኝ ፡ ማታ ፡
ደብቀሽ ፡ ሰው ፡ ሳያይ ጠጪው ፡ በቀስታ
ሌሊቱን ፡ ሳትሰሚ ፡ መድኀኒቱ ፡ ሠርቶ ፡
ነገ ፡ ጧት ፡ ከእንቅልፍሽ መነሣትሽ ፡ ቀርቶ
ሞተሽ ፡ ትገኛለሽ ፡ ትንፋሽሽም ፡ ጠፍቶ ፡
ወስደው ፡ ይቀብሩሻል ፡ ሞታለች ፡ ተብሎ
ለቤተ ፡ ሰባችሁ ፡ በሰፊው ፡ ተንጣሎ ፡
አምሮ ፡ በተሠራው ፡በመቃብር ፡ ቤት ፡
ተኝተሽ ፡ ቈይተሽ ፡ ቀንና ፡ ሌሊት ፡
ታዝኖ ፡ ተለቅሶልሽ ፡ ካለቀ ፡ በኋላ ፡
ዐውቀሽ ፡ ትነሻለሽ ፡ አንድ ፡ ቀን ፡ ሲሞላ
እስከዚያ ፡ እሠራለሁ ፡ እኔ ፡ ግን ፡ ተግቼ ፤
ደብዳቤ ፡ እጽፍና ፡ ሮሜዎን ፡ ጠርቼ ፡
እሱም ፡ በቬሮና ፡ ተደብቆ ፡ ገብቶ ፡
ወዳንቺ ፡ መቃብር ፡ ከኔ ፡ ጋራ ፡ መጥቶ ፡
አንቺ ፡ ሳትነሺ 'አጠገብሽ 'ደርሰን ፡
በምስጢር ፡ በፍጥነት ፡ ልብስሽን ፡ አልብሰን አንቺና ፡ ሮሜዎ ከዚህ ፡ ከከተማ
ማንም ሳይጠረጥር ማንም ሰው ሳይሰማ
ወጥታችሁ ፡ሄዳችሁ የትም ፡ በሌላ ፡ አገር
ዕረፍት ፡ አግኝታችሁ ፡ ያለ ፡ ክፉ ፡ ነገር
ኑሩልኝ ፡ በሰላም ፡ በፍጹም ፡ ደስታ ፡
ከናንተ ጋር ይሁን የእግዚአብሔር እርዳታ
ትጠጭው ፡ እንዲሆን ፡ ዡልዬት ፡ ሳትፈሪ'
አስቢና ፡ ቶሎ ፡ ገልጠሽ ፡ ተናገሪ ፡
እኔም ፡ መድኒቱን ልስጥሽ አሁን ፡ ሳልቈይ
ከዚህ በቀር ፡ ዘዴ ፡ የለኝም ፡ ልጄ ፡ ሆይ ።

#ዡልዬት
መልካም ፡ ነው ፡ አባቴ ፡ ያላንድ' ቅሬታ' .
ሳልፈራ፡እጠጣለሁ፡ በትልቅ ፡ ደስታ "
እባ፡ ሎራ ፡ ገብተው ጓዳ መድኀኒቱን በብልቃጥ አመጡ
ዶግሞስ በገዛ እጁ ለመሞት ሲቃጣ ከዚህ የተሻለ ምን ዘዴ ሊመጣ ።
እንግዲያውስ፡እንቺ ፡ ይኸው ፡ መድኀኒቱ :
እግዚአብሔር ልብሽን ፡ ያድርግልሽ ብርቱ

#ዡልዬት
አዝነው ፡ ስለ ፡ ረዱኝ ፡ ልብዎ ፡ ስለ ፡ ራራ
እግዚአብሔር ይስጥልኝ ፡ አባቴ አባ ሎራ

#አባ_ሎራ
ግድ ፡ የለሽም ፡ ልጄ ፡ ሳልዘገይ ፡ ፈጥኜ ፡
እንደ ፡ ምንም ፡ ብዬ ፡ አንድ ፡ ቄስ ፡ ለምኜ
ወደ ፡ ሮሜዎ ፡ ዘንድ ፡ጒዳዩን ፡ ሸሽጌ፥
ደብዳቤውን ፡ ጽፌ ፡ በምስጢር ፡ አድርጌ
እልክለታለሁ ፡ በቶሎ ፡ እንዲመጣ '
ዡልዬት ፡ በኔ ፡ ጣዪው ፤ የቀረውን ፡ ጣጣ

#ካፑሌ#የካፑሌ_ሚስት #ዡልዬት
(ዡልዬት ' ከውጭ መጣች)

#ካፑሌ
በጣም ያሳዝናል ባሕሪሽ ፡ ተበላሸ ፤
ወዴት ሄደሽ ኖሯል ደግሞ ፡ እንዲህ ፡ ከመሽ

💫ይቀጥላል💫
#ሮሜዎና_ዡልዬት


#ክፍል_አስራ_ሁለት

#ሞግዚት
ሞታለች ፡ ሞታለች ፡ ጕድ ፡ ነው ፡ የሚያስደንቅ ,

#የካፑሌ_ሚስት
ምን ፡መድኀኒት ላምጣ ወዴት ስፍራ ሄጄ

#ካፑሌ
ቆዩ፡እስቲ፡እኔ፡ልያት፡ የታለች፡ ቀዝቃዛ ፡ (እየዳበሳት).
ፈጽማ ፡ ሞታለች ፡ በምን ፡ ጕዴ በዛ
ሌሊት፡ በጨለማ ፡ ፀሓይዋ፡ ሳትወጣ ፡
ልጄ ፡ አበባዬ ፡ ወድቃለች ፡ ተቋርጣ ።

#ሞግዚት
የተረገመ ፡ ነው ፡ አወይ ፡ የዛሬው ቀን ፤

#የካፑሌ_ሚስት
ምነው ፡ ብንቀበር ፡ ሁላችንም ፡ አልቀን !

#ካፑሌ
ምንም ፡ አልናገር' ምላሴ 'ታሰረ
ልሳኔ ፡ በሐዘን 'ተቁልፎ ፡ ቀረ ።
(አባ ' ሎራና 'ፓሪስ ' በሙዚቃ ገቡ ።)

#አባ_ሎራ
ወደ ፡ ቤተ ፡ ክርስቲያን እንሂድ ፍጠኑ
ሙሽራዋን ጥሩ እናንተም ቶሎ'ኑ ።

#ካፑሌ
ጉድ ሆነናል ዛሬ ይተዉ አባቴ
ጕድ ፡ ለማየት ፡ ኖሯል ፡ የቈየች ፡ ሕይወቴ
እኔ ፡ ወዴት ፡ ልድረስ ፡ የት ፡ አባቴ ፡ ልግባ
ሞተች ፡ ተቀጠፈች ፡ ልጄ ፡ የኔ ፡ ኣበባ ።
እናቷ ፡ ሳታስብ ፡ ኣባቷ ፡ ሳይሰማ ፡
ሞት ፡ የሚባል ፡ ሌባ ፡ ሌሊት በለጨለማ
ለካ ፡ ከቤታችን ፡ ገብቶ ፡ ተደብቆ ፡
ይዟት ፡ ሄዶ ፡ ኖሯል ፡ ልጃችንን ፡ ሰርቆ ፤
እንዴት ፡ ጉድ፡ ሆነናል ፡ እንዲህ ፡ ተደግሶ
ሰርጓ ሐዘን ፡ ሆነ ደስታችን ለቅሶ ።

#ፓሪስ
እኔ ፡ ዕድለ ፡ ቢሱ፡ እንዴት፡ ያለ ፡ መርዶ፡
እንዴት ፡ ያለ ፡ሐዘን ፡ ጠበቀኝ ፡ ተወልዶ

#የካፑሌ_ሚስት
የተረገመ ፡ ነው ፡ አወይ ፡ የዛሬ ፡ ቀን
ቀረን ፡ እኮ ፡ ሰዎች ፡ እንደዚህ ፡ ተሳቀን ፡
ያይኖቼ ፡ ማረፊያ ብትኖረኝ አንዲት ፡ ልጅ
ያንድ ፡ ቀን 'ደስታ' ለማየት'ስዘጋጅ፡
ለማን ኣቤት ልበል ፡ ሞት ፡ ይዞብኝ ፡ ሄደ
ሆዴ ተቃጠለ አንጀቴ ፡ ነደደ

#አባ_ሎራ "
ይብቃ ፡ ለሐዘኑ ፡ አድርጉለት ፡ መጠን ፤
አስቡ ፡ ይችን 'ልጅ' እግዜር ፡ ነው' የሰጠን
አሁንም ፡እግዚአብሔር ወሰዳት መልሶ :
ሐዘናችሁ ፡ አይሁን ፡ ያረመኔ ፡ ለቅሶ ፡
ቀረባት ፡ ብላችሁ ፡ የመሬት ፡ ደስታ ፡
ጸጸታችሁ ፡ አይሁን ፡ በጣም ፡ የበረታ ፡
የመሬት ፡ ደስታ ፡ ምንም ፡ የለው ፡ ዋጋ ፤
ይልቅ አይበልጥም ወይ የሰማይቤት ጸጋ፡
ከሚያልፍ ፡ዓለም ወጥታ፡ ከዘለዓለም ቤቷ
መተላለፍ፡ ነው ፡ በሰላም ፡ መግባቷ ፡
መሆኑ ፡ ቀረና፡ ሰርጓ በመሬት ላይ፤
ብርሃን ፡ ወዳለበት፡ሄደች፡ ወደ ፡ ሰማይ ፡
እናድርጋት ፡ ስንል ፡ ምድራዊት ፡ ሙሽራ ፡
አይሆናትም ፡ ብሎ ፡ የመሬት ፡ መከራ ፡
ሺሕ ፡ ጊዜ ፡ የላቀ ፡ ደስታ፡ አዘጋጅቶ ፡
እግዚአብሔር ፡ ወሰዳት ፡በፈቃዱ ፡ ጠርቶ
የሰርግ ልብሷን ለብሳ እንዳማረች በክብር
በሉ ፡ ያዟትና ፡ እንሂድ ፡ መቃብር ።

#ሮሜዎ ። (በተሰደደበት ፡ አገር 'ሆኖ)
መሠረት ፡ ቢኖረው ፡ የኔ ፡ ሕልም፡ ዛሬ ፡
አገኝ ፡ ይመስለኛል ፡ ደስ የሚያሰኝ ፡ ወሬ
ዡልዬት ፡ ስትመጣ ፡ ስታገኘኝ ፡ ሞቼ ፡
አልቅሳ ፡ ስትስመኝ ፡ እኔ ፡ ተዘርግቼ ።
ኋላም ፡ በሷ ፡ ትንፋሽ ፡ ሕይወቴን ፡ አድሼ
ከሞት ፡ ተነሥቼ ፡ አየሁኝ ፡ ነግሼ ።
በጣም ፡ ደስ ፡ ብሎኛል ፡ ዛሬ ጧት፡ጀምሮ
ሰላም ፡ ይሰማኛል ፡ የመንፈስ ፡ የአእምሮ
(ቤልሻጥር ቦት ጫማ አድርጎ፡ መጣ)
ቤልሻጥር ፡ጐበዙ፡ እንኳን ፡ ገባህ ፡ ደኅና'
ምን ወሬ ይዘህ መጣህ ዛሬ ከቤሮና ?
ዡልዬት ደኅናነች ወይ አባቴስ እንዴት ነው ?
እሷ ፡ ደኅና፡ ብትሆን ፡ግድ የለም የቀረው
ዡልዬት ፡እንደ ፡ምን ነች ? አሁንም አድሼ
ልጠይቅህ ፡ በጣም ሺሕ ፡ ጊዜ ፡ መልሼ

#ቤልሻጥር
ደኅና ፡ ነች ፡ ልበልህ ፡ አልነካትም ፡ ዐፈር
እንደሌላው ፡ ፍጥረት ፡ መሬት ፡ ሳትቀበር
ከመቃብሩ ፡ ቤት፡ ሠርተው ፡ አባቷ
ካዘጋጁት ፡ ገብታ ፡ እግሮቿም ፡ እጆቿ ፡
ታስረው ፡ ሳትገነዝ ፡ በማዕርግ ፡ ተንጋላ ፡
ተኝታ ፡ ኣየናት ፡ ያንቀላፋች ፡ መስላ ።
እንዲህ ፡ በጌትነት ፡ ዡልዬት ፡ ተቀበረች ፤
በቃ ፡ የሷ፡ ነገር ፡ እንደ ፡ ዘበት ፡ ቀረች ።
ነፍሷ ፡ ግን ወደ እግዜር ዐረገች ወደ ላይ
ዐርፋ ፡ ከዚህ ዓለም ወጣች ፡ ወደ ሰማይ

#ሮሜዎ ። (በድንጋጤ ፊቱ ተለወጠ)
ምን ፡ አገኛትና ? በምን ፡ የተነሣ ?

#ቤልሻጥር
ጧት፡ ባልጋዋ ፡ ላይ ፡ በድን ሆና ሬሳ፡
ተገኘች ፡ ከእንቅልፍ፡ ሳትነቃ ፡ ሞታ ፤

#ሮሜዎ
እንደዚህ ፡ ከሆነ 'የዡልዬት ፡ ሁኔታ ፡
ደግ ፡ ነው መልካም ፡ ነው ፤ ብዕር፡ቀለም፡ኣምጣ፡
ፈረሶች ፡ ተከራይ ፈጥነህ መንደር ፡ውጣ
ማንም ሰው ሳያየኝ ማንም ሰው ሳይሰማ
መሄዴ' ነውና ፡ ሌሊት ፡ በጨለማ ።

#ቤልሻጥር
እባክህ ፡ ጌታዬ ፡ ፊትህ ፡ ተለወጠ ፤
ደምህም ፡ ጠቈረ ፡ ልቤ ፡ ደነገጠ '
ቻለው ፡ ሐዘንህን ፡ ከትዕግሥት ፡ ጋራ

#ሮሜዎ
አትሥጋ ፡ ግድ የለም ፡ ቤልሻጥር አትፍራ
የማይሆን አይሆንም የሚሆን ፡ ይሆናል !

ይልቅ ፡ቶሎ ፡ ፍጠን ፡ ጊዜው ፡ ያልፍብናል
(ቤልሻጥር ሄደ፤ ሮሜዎ'ብቻውን) »
እንገናኛለን ፡ ዥልዬት ፡ ዛሬ ፡ ማታ ፤
ወዳንቺ ፡ ለመድረስ ፡ ቶሎ ፡ በደስታ ፡
መንገዱን ፡ መፈለግ ፡ አለብኝ ፡ ግዴታ ፡
መድኀኒት ፡ የሚሸጥ ፡ አንድ ፡ ጎረቤቴ ፡
መኖሩን ፡ ዐውቃለሁ ፥ እኔ ፡ በሕይወቴ ፡
አይቼ ፡ አላውቅም ፡ ችግረኛ ፡ እንደ ፡ እሱ
ሁል ፡ ጊዜ ፡ ያደፈ፡ ቀዳዳ ፡ ነው ፡ ልብሱ ፡
የተጐዳ ፡ ሰው ፡ ነው ፡ ድህነት ፡ ያጠቃው
ሰውነቱ ፡ ከስቷል ፡ የመደብር ፡ ዕቃው ፡
አሮጌ ፡ ብቻ ፡ ነው ፡ ቈሻሻ ፡ ሰባራ ፤
ተጠርጎ ፡ የማያውቅ ፡ የለበሰ ፡ ዐቧራ ።
ከሱቁ ፡ ስገባ ኔም አስተውዬ
እሱን ፡ባየሁ ቍጥር አሰብኩ እንዲህ ብዬ
በማንቱ ፡ ከተማ ፡ ለሰው ፡ መርዝ ፡ የሸጠ
በምንም ፡ አኳኋን ፡ አውጥቶ ፡ የሰጠ ፡
ምንም ፡ እንኳ፡ የሚያዝ ፡ በሞት ፡ እንዲቀጣ ፡
ኀይለኛ ፡ ዐዋጅ ፡ ቢኖር ፡ ተጽፎ ፡ የወጣ ፡
መርዝ ፡ የሚፈልግ ፡ ሰው ፡ ብዙ ፡ ገንዘብ ፡ ሰጥቶ ፡
ይህን ችግረኛ፡ ቢጠይቀው ፡ መጥቶ ፡
አይጠረጠርም : እንቢ ፡ እንደማይለው ፤
ስለዚህ ፡ ጠርቼ ፡ እስቲ ፡ ልሞክረው ፡
አንተ ፡ መድኀኒት ፡ ሽያጭ፡ እባክህ ፡ ወዲህ ፡ ና ።

#መድኀኒት_ሽያጭ
ምነው ፡ ሮሜዎ አይዶለም ወይ ፡ ደኅና ?

#ሮሜዎ
ሰው ፡ አንተን ይሻሃል ባጣ ፡ ጊዜ ፡ ጤና፡
አንድ ፡ ነገር ፡ አሁን ፡ ልንገርህ ፡አድምጠኝ
ቶሎ ፡ የሚገድል ፡ ብርቱ ፡ መርዝ ፡ ስጠኝ፡
አርባ ፡ ዱካ ፡ ልስጥህ ለመርዝህም ዋጋ
አንተም ፡ ትሆናለህ ፡ በዚህ ፡ ባለጸጋ ፡
አንተን ፡ ለመሰለ ፡ በጣም ፡ ለተጐዳ ፡
ይህ ፡ ብዙ ፡ ገንዘብ ነው በጣም የሚረዳ

#መድኅኒት ፡ ሽያጭ ።
ኀይለኛ ፡ መርዝ አለኝ በመደብሬ ውስጥ
ግን ፡ ባዋጅ ፡ ክልክል ነው፡ለማንም፡ እንዳልሸጥ ።

#ሮሜዎ
ሞኝ ፡ ነህ ፡ መሰለኝ ፡ ዐዋጅ ፡ብሎ ፡ ጣጣ
ራብ ፡ ለገደለህ ፡ ዐጥንትህ ' ለወጣ'
ላንተ ፡ ምን ' ጠቀመህ ይልቅ ስጠኝ' ቶሎ
ድኽነት ፡ ይታያል ፡ በመልክህ ፡ ተሥሎ'
ጒዳት ፡ አቈራምዶ፡ ችግር ፡ ያሸነፈህ

💫ይቀጥላል💫
👍1
#ሮሜዎና_ዡልዬት


#ክፍል_አስራ_ሶስት

#በአባ_ሎራ_ቤት

አባ ፡ ዮሐንስ ፡ (ከውጭ ፡ መጣ) ።
ወዴት ፡ ነው ፡ ያለኸው ፡ አባቴ ፡ አባሎራ ?

#አባ_ሎራ
ተሳሳትኩ ፡ ብዬ ፡ በልቤ ፡ ባልፈራ ፡
በድምፅህ ፡ መሰልከኝ ፡ የኛ ፡ አባ ፡ ዮሐንስ ።

#አባ_ዮሐንስ
ዐውቀሃል ፡ እኔ ፡ ነኝ ።

#አባ_ሎራ
አንተ ፡ እስክትመለስ ፡
እጠብቅህ ፡ ነበር ፡ ቸኩዬ ፡ ባሳቤ ፡
ፈጥነህ ፡ ደረስክልኝ ፡ ስሥጋ ፡ በልቤ ፡
መልሱን ፡ ከሮሜዎ ፡ ለጻፍኩት ፡ ደብዳቤ አመጣህልኝ ፡ ወይ ?እስቲ ቶሎ ፡ ስጠኝ፤

#አባ_ዮሐንስ
የሆንኩትን ፡ ነገር ፡ ልንገርህ ፡ አድምጠኝ
ደብዳቤህን ፡ ቶሎ ፡ ለመስጠት ፡ ወስጄ
አንዱን ፡ የኛ ፡ ካህን ፡ ልፈልገው ፡ ሄጄ ፡
ወደ ፡ ሮሜዎ ቤት፡ እንዲወስድኝ መርቶ :
እሱም ፡ እሺ ፡ ብሎ ፡ ሊወስደኝ ፡ ተነሥቶ
ዘበኞች ፡ መጡና ፡ ከቤት ፡ እንዳንወጣ ፡
ዘግተውብን ፡ ሄዱ፤ ከውጭ ፡ የመጣ ፡
በሽታ ፡ ስላለ ማንም ፡ ከሌላ ፡ አገር፡
ሲመጣ ፡ አስቀድሞ ፡ ለካ ፡ እስቲመረመር
ለብቻው ፡ እንዲሆን ፡ የመጣው ፡ ሥራቱ፡
የሚያስገድድ ፡ ኖሮ ፡ ሳልሄድ ወደ ፡ማንቱ
ሮሜዎን ፡ ሳላገኝ ፡ ሳላየው ፡ ደርሼ
ያንተንም ፡ ደብዳቤ ፡ አመጣሁ ፡ መልሼ
ልልከው ፡ አስቤ ፡ ብሞክር ፡ ብለፋ:
ብጠይቅ ባስጠይቅ የሚላክ ሰው ፡ ጠፋ፡
አልሆንልህ ፡ አለኝ ፡ ነገር ፡ አልሳካ ፤
ይቅርታ ፡ አድሮግልኝ ፡ ደብዳቤህን፡እንካ ። (ሰጠው)

#አባ_ሎራ
ምንኛ ፡ መጥፎ ፡ ነው ፡ያመጣኸው ወሬ !
አይ ፡ አባ ፡ ዮሐንስ ፡ ጉድ ሰራኸኝ ፡ ዛሬ ።
መልክቴ ፡ በውነቱ፡ ትልቅ ጕዳይ ፡ ነበር ፤
በጣም ፡ የከበደ ፡ ከፍ ያለ'ቁም ፡ ነገር ፡
ባለመፈጸሙ ፡ የመልክቴ ፡ አደራ ፡
እጅግ ፡ የሚያሳዝን በጣም የሚያስፈራ፡
ነገር ፡ ለማስከተል ፡ ይችላል ፡ ወዳጄ ፤
ጽፌ ፡ የሰጠሁህ ፡ ያ ፡ ወረቀት ፡ በእጄ ፡
ለሮሜዎ ፡ ቶሎ ፡ መድረስ ፡ ነበረበት ፤
አይ ፡አባ ዮሐንስ ጕድ ሠራኸኝ በውነት !
እባክህ ፡ አሁንም ፡ ቶሎ ፡ እንረዳዳ ፤
ጕጠት ፡ ፈልግና ፡ አምጣልኝ ፡ ከጓዳ ።

#አባ_ዮሐንስ
ሳልችል ፡ ቀርቼ ፡ ነው ፡ በጣም ፡ ተቸግሬ ፡
ምን ፡ ሁን ፡ ትለኛለህ ፡ ስቀመጥ ፡ ታስሬ ፡
እንዴት ፡ ብዬ ፡ ልሂድ እንደ ፡ ምን ፡ አድርጌ
መልካም ነው ጕጠቱን ላምጣልህ ፡ ፈልጌ
(አባ ፡ ዮሐንስ ፡ ወደ ፡ ጓዳ ፡ ገባ) ።

#አባ_ሎራ ፡ (ብቻውን) ።
ከዡልዬት ፡ መቃብር ፡ ብቻዬን ፡ ገሥግሼ ፡
መዝጊያውን ፡ ልከፍተው ፡ በቶሎ ፡ ደርሼ
መድረስ ፡ ይገባኛል ፡ በቶሎ ፡ በቅጽበት
ጊዜው ፡ ደርሷልና ፡ የምትነሣበት ።
በተነሣች ፡ ጊዜ ፡ ሮሜዎን ፡ ስታጣ ፡
እንደ ፡ ምን ፡ ትረግመኝ ፡ በንዴት ፡ በቍጣ
አምጥቼ ፡ ላስቀምጣት ፡ በቤቴ ፡ ሸሽጌ ፤
ከዚያም ፡ እንደ ፡ ገና ፡ አንድ ፡ሰው ፡ ፈልጌ
ደግሞ ፡ ለሮሜዎ ፡ ሲሆን ፡ ዛሬ ፡ ማታ ፡
ጽፌለት ፡ ይመጣል ፡ ሁሉንም ፡ ሐተታ ።

(ፓሪስ ፡ ካሽከሩ ፡ ጋር ፡ አበባና 'መብራት ፡ ይዞ ፡ ወደ ፡ ዡልዬት ፡መቃብር ፡ መጣ) "

#ፓሪስ
መብራቱን አጥፋው እንግዲህ ይበቃል
ሰው የመጣ፡እንደሆን ምናልባት ማን ያውቃል
እዚህ ፡ ሰው ፡ እንዲያየኝ ፡ አልፈልግምና
በል ፡ ቅረብ ፡ተጠጋ ፡ አንተም ወደዚህ ፡ና።
ጀሮህን ፡ አቁመህ ፡ ተጠንቅቀህ ፡ ስማ ፤
ኰሽታ ፡ ስትሰማ ፡ ወይም ፡ የሰው ፡ ጫማ
ምልክት እንዲሆን አፏጭተህ አስታውቀኝ ፡
አስቀድሜ ፡ እንዳውቀው ፡ ፈጥነህ ፡ አስጠንቅቀኝ፤
በል ፡ እንግዲህ ፡ አሁን ፡ አበባውን ፡ ስጠኝ ።
(ፓሪስ ፡ ሄደ) ።

#አሽከር ፡ (ብቻውን) ።
የተሻለ ፡ ስፍራ ፡ ባገኝ ፡ ደግ ፡ ነበር ፤
ይህ ፡ ቦታ ፡ ቀፈፈኝ ፡አልወድም ፡ መቃብር
(እልፍ ፡ ብሎ ፡ ሄደ ) ።

#ፓሪስ ። (በዥልዬት ፡ መቃብር ፡ ላይ) ።
ይህንን ፡ አበባ ፡ መርጨ፡ ፈልጌ ፡
ላቀርብልሽ ፡ መጣሁ ፡ በረከት ፡ አድርጌ
ገጸ ፡ በረከቴ ፡ ጸጸት ፡ ነው ፥ አበባ ፤
ሐዘን ፡ ነው ፡ ለቅሶ ፡ ነው ፡ የመረረ ፡ እንባ
ትተሽኝ ፡ ብትሄጂ ፡ ብቻዬን ፡ ቀርቼ ፡
ልጐበኝሽ ፡ መጣሁ ፡ ሌሊት ፡ ተነሥቼ ።
(አሽከሩ ፡ አፏጨ) ።
እንሆ ፡ አፏጨ ፡ ሰማሁት ፡ አሽከሬ ፤
አሁን የሚመጣ ሰው፡ ነው ወይስ አውሬ ?
ሰላም ፡ የሚነሳኝ ማነው፡ ባሁን ፡ ሰዓት ?
እንዴት ? ደግሞ ፡ ያውም፡ይዟል ፡ በእጁ ፡ መብራት!
እስክረዳው ፡ ድረስ ፡ ምስጢሩን ፡ ዐውቄ ፡
ከለላ፡ፈልጌ፡ልየው ፡ተደብቄ (እልፍ፡ ብሎ ተደበቀ)

(ሮሜዎና ፡ ቤልሻጥር ፡ መብራትና ጉጠት ፡ ይዘው ፡ መጡ) ።

#ሮሜዎ
በል መብራቱን ስጠኝ፤ አንተ ግን ተመለስ
እገባለሁ ፡ እኔ ፡ መቃብሯ ፡ ድረስ ፤
አንተ ፡ ከዚህ ፡ ቦታ ፡ እንዳትንቀሳቀስ ፡
ዦሮህን ፡ አቁመህ ፡ ሰው ፡ ሲመጣ ፡ ስማ
ተደብቀህ ፡ ጠብቅ ፡ እዚህ ፡ በጨለማ ።
ያየህ ፡ እንደ ፡ ሆነ ፡ ሰው ወዲህ ሲመጣ፡
ከተደበቅህበት ፡ ቦታ ፡ ሳትወጣ ፡
በፉጨት ፡ ምልክት ፡ እኔን ፡ አስጠንቅቀኝ
ምናልባት ፡ ሰው ደርሶ ድንገት ፡ እንዳያየኝ
የዡልዬት ፡ ሬሳ ፡ ካለበት ፡ ገብቼ ፡
በመቃብሯ ፡ ውስጥ ፡ እሷን ፡ ተመልክቼ ፡
ካየኋት ፡ በኋላ ፡ ከልቤ ፡ አልቅሼ ፡
አንብቼ ፡ ሲያበቃኝ ፡ ሐዘኔን ፡ ጨርሼ ፡
የጣቷን ፡ ቀለበት ፡ አውልቄ ፡ ከሷ ፡ ላይ ፡
ልወስድ ፡አስቤያለሁ ላንድ ብርቱ ጕዳይ
ከወጣሁ ፡ በኋላ ፡ እኔ ፡ ከዚህ ፡ ቦታ ፡
ይህንን ፡ ደብዳቤ ፡ ጨምረህ ፡ ሰላምታ ፡
ላባቴ ፡ ስጥልኝ ፡ ነገር ፡ ግን ፡ ተጠንቀቅ ፤
ምን ፡ ይሠራል ፡ ብለህ፡ አሳቤን ፡ ለማወቅ
መሰለል ፡ አስበህ ፡ ወደ ፡ እኔ ፡ አትጠጋ ፤
ያገኝሃልና ፡ የመሞት፡ አደጋ ፡
በውነቱ ፡ ባገኝህ ፡ ይህንን ፡ ስትሠራ ፡
እጄም ፡ አያዝንልህ ፡ መንፈሴም ፡ አይራራ
ልብ ፡ በል ፥ተጠንቀቅ ለሕይወትህ ፡ ፍራ

#ቤልሻጥር
እኔ ፡ ከዚህ ፡ ቦታ ፡ አልንቀሳቀስም !
ስታስጠነቅቀኝ፡ትእዛዝ ፡ አላፈርህም። (ሮሜዎ'ሄደ)።

#ሮሜዎ ፡ (የዡልዩትን መቃብርዋን ' በር
ሊከፍት ፡ ይታገላል) ።
ከጥንት ፡ ጀምረህ ፡ ብትበላ ፡ ብትበላ ፡
ጠገብኩኝ ፡ የማትል ፡ ሆድህ ፡ የማይሞላ
መቃብር ፡የሚሉህ አንተ መጥፎ ከርሣም
ለወጣት ፡ አታዝን ፥ ለቆንዦ ፡ አትሣሣም
ዡልዬትን ፡ ከጥርስህ ፡ ፈልቅቄ ፡ ላወጣ ፡
መጥቻለሁና ፡ የዋጥከውን ፡ አምጣ ፡
አንዴ ፡ ልያትና ፡ እንባዬን ፡ አፍስሼ ፡
እርሜንም ፡ አውጥቼ ፡ ተራዬን ፡ አልቅሼ ፡
ሐዘኔን ፡ ገልጬ ፡ ከበቃኝ ፡ በኋላ ፡
እኔንም ፡ ከሷ ፡ ጋር ፡ አብረህ ፡ እንድትበላ

#ፓሪስ
መብራት ፡ በጁ ፡ ይዞ ፡ የመጣው ፡ ከደጅ
ሮሜዎ ፡ ይመስላል ፡ ያ የሞንታግ ፡ ልጅ፡
ጐበዙን ፡ ቲባልትን ፡ የዡልዬትን ፡ ዘመድ ፡
አሁን ፡ በቅርብ ፡ቀን ተጣልቶት ፡ በመንገድ
ገድሎ ፡ ተፈርዶበት ፡ ተሰዶ ፡ የወጣ ፡
አሁን ፡ ደግሞ ፡ እዚህ ፡ ምን ፡ ሊፈጥር፡ መጣ?

💫ይቀጥላል💫
#ሮሜዎና_ዡልዬት


#ክፍል_አስራ_አራት

ለክፋት ፡ ነው ፡እንጂ አልመጣም ፡ በደኅና
እንግዴህ ፡ ልያዘው ፡ ድንገት ፡ ልድረስና ።
(ቀረበ) ።
አንተ ፡ የሞንታግ ፡ ልጅ ፡ዐመፀኛ ፡ መጥፎ
በሰላም ፡ ጸጥታ፡ የተኛውን ፡ ዐርፎ ፡
ምን ፡ ልታደርግ ፡ ነው ፡ ትኵሱን ፡ ሬሳ ፡
ከመቃብሩ ፡ ላይ ፡ በል ፡ እጅህን ፡ አንሣ ፡
ና፡ ወዲህ ፡ ልያዝህ ፡ ከዚህ ፡ ቦታ ፡ ውጣ
ኣሳልፌ ፡ ልስጥህ ፡ በሞት ፡ ለሚቀጣ ።

#ሮሜዎ
አንተ መልካም ወጣት፡ዐርፈህ ሂድ በደኅና
እኔ ፡ ሞገደኛ፡ አጥፊ ፡ ሰው ፡ ነኝና ፡
መዘዜ፡ የበዛ ፡ አሳር ፡ የጐተተኝ፡
ሕይወቴን ፡ የጠላሁ፣ ኑሮ ፡ የታከተኝ፡
ሞትና ፡ መቃብር ፡ ጥፋት ፡ የሸተተኝ ፡
የከፋው ፡ ወንድ ፡ ነኝ ፡ ወደኔ ፡ አትጠጋ ፤ .
ጠብ ፡ አትፈልገኝ' ለሕይወትህ ፡ ሥጋ ።
ቲባልት ፡ እንደዚሁ ፡ ደርሶ : ሳይቸግረው ፡
በመጥፎ፡ ንግግር ፡ ሆዴን ፡ አሳረረው ፡
ሳልፈልግ ፡ ገደልኩት እሱ ባነሣው ፡ ጠብ
አሁን ፡ ደግሞ ፡ አንተ ይብቃህ ፡ አትሳደብ
ነፍሴን ፡ የጠላሁ፡ ሰው ፡ በመሆኔ ፡ ፍራኝ
ሳልወድ ፡ በግዴታ ፡ ዐመፅ ፡ አታሠራኝ ፡
የሚወጣው ፡ ምክር ፡ አሁን ፡ ከመላሴ ፡
አልሠራሁበትም ፡ እኔ ፡ እንኳ ፡ ለራሴ ፡
ስለዚህ ፡ ከራሴ ፡ አብልጬ ፡ ስወድህ ፡
እኔን ፡ አመስግነህ ፡ ይሻላል ፡ መሄድህ ፡
አንድ፡ እብድ ፡ ሰው ዛሬ የሰጠኝን ምክር
ሰምቼ ፡ ድኛለሁ ፡ ብለህ ፡ ይልቅ ፡ ፎክር ።

#ፓሪስ
እኔስ ፡ ኣለቅህም ፡ ከያዝኩህ ፡ በኋላ ፤
መስጠት ፡ ትችላለህ ፡ ምክርህን ፡ ለሌላ

#ሮሜዎ
መሞት ፡ ከፈለገህ ፡ እንቢ ፡ ብለህ ፡ በጄ ፡
እንግዲያው ሞክረኝ መልካም፡ነው ወዳጄ
(ይዋጉና'ፓሪስ ፡ ይወድቃል) ።.
ቲባልትና ፣ፓሪስ ፡ እኔን እያስቆጡ ፣
እኔ ፡ ሳልነካቸው ፡ በግድ ፡ እየመጡ፡
በእጄ ፡ እየተወጉ' ክዚህ ፡ ዓለም ፡ ወጡ ።
እንዲህ ፡ መሞታቸው ፡ ተናግረውኝ ፡ ክፉ
ተፈርዶባቸው ፡ ነው ፡ በኔ' እጅ እንዲጠፉ
እንደዚህ ፡ ከሆነ ፡ ፓሪስ ፡ ያንተም ፡ ዕጣ ፡
ጥፋቱ ፡ ያንተ ፡ ነው ፡ በኔ ፡ እንዳትቈጣ ፡
የዡልዬት ፡ ቁንዥና፡ ደምቆ እንደ ፡ ብርሃን
ጽርሐ አርያም ፡ መስሎ የሰማይ ፡ ውጋጋን
እያንጸባረቀ ፡ ከኮከብ ፡ ሲያበራ ፡
ግርማ፡ተጐናጽፎ፡ በታየበት፡ ስፍራ፡
እንሙት' ወዳጄ ፡ ኣብረን ፡ ከሷ ፡ ጋራ።
(ሮሜዎበዝልዬት፡መቃብር፡ላይየሐዘን ' ንግግር ፡ ያደርጋል)።
ይህችን ፡ ውብ ፡ አበባ ፡ ፍቅር ፡ አሳማሪ ፡
ውሏን ፡ የማትረሳ ፡ ቃል ፡ ኪዳን ፡ አክባሪ ፡
ትወድ ፡ የነበረች ፡ ቁም ፡ ነገር ፡ ጨዋታ፡
እዩልኝ ፡ ከዘመድ ፡ ከሰው ፡ ተለይታ ፡
የኔ ፡ ሆደ፡ ባሻ ፡ ብቻዋን ፡ ተኝታ፡
ተመልከቱት ፡ እጅዋ ፡ ተመልከቱት ፡ ፊቷ ፤
ወዟ ፡ ገና፡ አልጠፋም ። ከሠራ፡ አካላቷ፡
ግንባሯን ፡ ከንፈራን ፡ ተመልከቱ ፡ ጣቷን ፤
ይህን ፡ አበቃቀል ፡ ተክለ ፡ ሰውነቷን ፡
ገላዋ ፡ ያበራል ፡ በደም ፡ ተሸልሞ ፤
ዡልዬት ፡ሞት የነካት፡አትመስልም ፈጽሞ
እባካችሁ ፡ ሰዎች ፡ ሐዘን፡ ተካፈሉኝ፤
ዡልዬት ፡ አልሞተችም ፡ ተኝታለች ፡ በሉኝ
ታውቂ ፡ የነበርሽው ፡ ፍቅራዊ ፡ አቀባበል ፡
ሽቍጥቀጥ ፡እመቤት ባለመልካም ዐመል
ተወዳጁ ፡ ድምፅሽ ፡ ውብ ፡እንደ ፡ ሙዚቃ
በበገናው ፡ ቃሉ ፡ መንፈስ ፡ የሚያነቃ ፡
ዛሬ ፡ ወዴት ፡ ጠፋ? የት ፡ ቦታ ፡ ደረሰ ? .
ደግሞስ ዐይንሽ ፡ ቆቡን ስለ ምን ለበሰ ?
ዡልዩት ፡ ባትሞት ኖሮ፡ በውነት ፡ ባትቀበር
ሮሜዎ ፡ እዚህ ፡ ቆሞ ዝም አትልም ነበር
ባለም ፡ ላይ ፡ ብንሻ ፡ በውነቱ ፡ የት ፡ ኣለ ፡
ጨካኝ አረመኔ ፡ ሞትን ፡ የመሰለ ፡
ጥቂት ፡ አላዘነም ፡ አልሣሣም ፡ ጨርሶ ፡
ይችን ፡ ጽጌ ፡ ረዳ ፡ ሲጥላት ፡ በጥሶ :
ይችን ፡ አሳዛኝ ፡ ልጅ ፡ ትተዋት ፡ ሲሄዱ፡
በሩን ፡ የዘጋ ፡ ሰው ፡ እንዴት ፡ ቻለ ፡ ሆዱ
እይዋት ይችን ቄንጥ እይዋት ይችን ሎጋ
በባዶ፡ አዳራሽ ፡ በመቃብር ፡ ኣልጋ ፡
ወፍ ፡ በማይዞርበት ፡ ጭር ፡ ባለ ፡ ስፍራ ፡
ብቻዋን ፡ ቀርታለች ፡ አዲሷ ፡ ሙሽራ ።
በመከራ ፡ ቅመም ፡ ባሳር ፡ ተለውሶ :
ዡልዬት፡ ሕይወታችን ፡ መሮን ፡ እንደ ፡ኮሶ
ወጣን ፡ ከዚህ ፡ ዓለም ፡ ያላንድ ፡ ደስታ .
እንግዲህ ፡ እንኑር ፡ እዚህ ፡ በጸጥታ ።
ባለም ፡ ቦታ፡ ጠፍቶ ፡ ለመኖር'ተዋደን ፡
እዚህ ፡ ተገናኘን ፡ ካለም ፡ ላይ ፡ ተሰደን
አይቈጨን እንደዚህ ካለም መውጣታችን
በጣም ፡ ደስ ፡ይበለን ፡ በዛሬው ፡ ዕጣችን
ላለሙ ፡ ደስታ ፡ ለረዥሙም ፡ ዕድሜ ፡
ያው ሞት አይደለም ወይ የሁሉ ፍጻሜ ?
ገላዬን ፡ ከገላሽ ፡ ዐፅምሽን ፡ ካዕፅሜ ፡
ሥጋዬን ፡ ከሥጋሽ ፡ ደምሽን ፡ ከደሜ ፡
ቀላቅሎ ፡ የሚያኖር፡ ከተገኘ ፡ ቦታ ፡
ዡልዬት፡ ከዚህ ፡ ወዲያ ፡ ምን አለ ፡ ደስታ
ይቅር ፡ ደኅና ፡ ይሁን ፡ ዓለም ፡ ከነቂሙ ፤
እዚህ ፡ እኔና፡ አንቺ ፡ እስከ ፡ ዘላለሙ ፡
መቃብር፡ ሆኖልን ፡ የጸጥታ ፡ ገዳም ፡
ከዛሬ ፡ ጀምሮ ፡ እንኑር ፡ በሰላም ።
ከሚወዱት፡ጋራ፡ እንዲህ ፡ ጐን ፡ ለጐን ፡
ምንኛ ፡ መልካም ፡ ነው ፡ ዐፈር ፡ ትቢያ ፡ መሆን ።
(ሮሜዎ ፡ መርዝ ፡ ጠጥቶ ፡ ሞተ ።)

#አባ_ሎራ መብራትና፡ጕጠት፡ ይዞ ፡
ወደ፡መቃብሩ፡ ቦታ፡ መጣ ።

#አባ_ሎራ
ስፍራው ፡ አያስኬድም ፡ ሆነና ፡ መቃብር
እያደናቀፈ ፡ ያስቸግራል ፡ ለእግር ፡
አዬ ፡ መከራዬ ፡ በዚሁ ፡ ላይ ፡ ደግሞ ፡
ምንም ፡አይታየኝ ፡ዐይኔ ፡ በጣም ፡ ደክሞ
ማነህ አንተ እዚህ የቆምከው እንደ አጥር ?

#ቤልሻጥር
የሚያውቁኝ ፡ወዳጅዎ ፡እኔ፡ ነኝ ቤልሻጥር ።

#አባ_ሎራ
እግዚአብሔር ይባርክህ በል ልጄ ንገረኝ ፤
በሩቅ ፡ አላይ ፡ ብሎ ፡ ዐይኔ ፡ አስቸገረኝ፡
እዚያ ፡ በካፑሌ ፡ የመቃብር ፡ ስፍራ ፡
መብራት አይደለም፡ ወይ የማየው ፡ ሲበራ?

#ቤልሻጥር
አዎን ፡ ነው ፡ አባቴ ፡ ሄዷል ፡ እዚያ ፡ ቦታ ፡
ወዳጅዎ ፡ ሮሜዎ ፡ የኔ ፡ መልካም ፡ ጌታ

#አባ_ሎራ
ማን ፡ አልከኝ ?

#ቤልሻጥር
ሮሜዎ ።

#አባ_ሎራ
አዬ ፡ የእግዜር ፡ ቀጣ
ምን ፡ ያኽል ፡ ጊዜ ፡ ነው ፡ እሱ ፡ እዚህ ፡ ከመጣ ?

#ቤልሻጥር
ልክ ፡ እኩል ፡ ሰዓት ፡ ነው ።

#አባ_ሎራ
ና፡ እንሂድ፡ ወደ ፡ እሱ

#ቤልሻጥር
አልችልም ፡ አባቴ ፡ አስጠንቅቆ ፡ ራሱ ፡
ወደ ፡ መቃብሩ፡ እሱ ፡ ወዳለበት ፡
ከቶ ፡ እንዳልጠጋ ፡ ሥራውን ፡ ለማየት ፡
ከልክሎኛልና ፡ በሞት ፡ አስፈራርቶ ፤
ትእዛዙን ፡ ለመጣስ ፡ እኔ ፡አልችልም ፡ ከቶ

#አባ_ሎራ
በል ፡ ተወው፡ ልጄ ፡ ሆይ፡ ሠግቷልና፡ ልቤ
እስቲ ፡ ልመልከተው ፡ ብቻዬን፡ቀርቤ።(አባ፡ሎራሄደ)

#ቤልሻጥር ፡ (ብቻውን ) ።
ዛፍ ፡ ተደገፍኩና ፡ እንቅልፍ ወስዶኝ ፡ ኖሮ
በሕልማ፡ ሮሜዎ ፡ አድርጎ ፡ አምባጓሮ ፡
ውጊያ፡ገጠሙና ፡ የኔ ፡ ጌታ ፡ ሲጥል ፡
አየሁ፡ ደግሞ ፡ ዛሬ ፡ ሌላ ፡ ሰው ፡ ሲገድል

#አባ_ሎራ ፡(ብቻውን) ።
ይህ ፡ ደም ፡ ከየት ፡ መጣ ? ይህ ሻምላ ፡ ምንድነው?
እዚህ ፡ የወደቀ ፡ ባለቤት ፡ የሌለው ።
(ዡሊዬት ነቃች ፤ አባሎራ፡ ጥግ ፡ ይዞ ፡ ቆመ) ።

#ዡልዬት
ሮሜዎ ፍቅሬ ሆይ ማን አምጥቶ ጣለህ ?
ይኸ ፡ ደም ምንድነው ? ፓሪስ ፡ ማ፡ገደለህ ?
ጨርሰው ፡ አይሰሙም ፡ ሞተዋል ፡ እነሱ
ትንፋሽም ፡ የላቸው ፡ አይንቀሳቀሱ ፡
የእንቅልፍ ፡ የመኝታ ፡ የዕረፍት ፡ የጸጥታ :
መሆኑ ፡ ቀረና ፡ ሰላማዊ ፡ ቦታ ፤
ከእንቅልፌ ፡ ስነቃ ፡ አወይ ፡ መቃብሬ ፡
የጦር ፡
👍1
#ሮሜዎና_ዡልዬት


#ክፍል_አስራ_አምስት(የመጨረሻ
ክፍል)

#ሁለተኛ_ዘበኛ
ይኸው ፡ አገኘነው ፡ የሮሜዎን ፡ አሽከር ።

#የመጀመሪያ_ዘበኛ
መስፍኑ ፡ እስቲመጡ፡ እንዳይመረመር ።
(ሦስተኛ ፡ ዘበኛ ፡ ከአባ ' ሎራ፡ጋራ፡ መጣ)

#ሦስተኛ_ዘበኛ
እያንቀጠቀጠው ፡ ጥግ ፡ ይዞ ፡ ሲያለቅስ
ይኸውና ፡ ደግሞ ፡ አገኘሁ ፡ አንድ ፡ ቄስ ፡
ለምን ፡ እንደ ፡ ያዘው ፡ አልታወቀም፡ ከቶ ፡
ጕጠቱን ፡ ቀማነው ፡ በእጁ ፡ ላይ ፡ተገኝቶ

#የመጀመሪያ_ዘበኛ
መስፍኑ ፡ እስቲመጡ ፡ እሱን ፡ አትልቀቁ ፤
የሚጠረጠር ፡ ነው ፡ ይዛችሁ ፡ ጠብቁ ።
(መስፍኑ ፡ ታጅቦ ፡ መጣ) ።

#መስፍን
እኔን ፡ የሚያስጠራ ፡ ሳይነጋ ፡ ሌሊቱ ፤
ምንድነው ፡ንገሩኝ ፡ እስቲ ፡ ምክንያቱ ? ..
(ካፑሌ ' ፤ ሚስቱና ሌሎች ሰዎች መጡ)

#ካፑሌ
ምስጢሩ ፡ ምንድነው ፡ የሰዉ ጫጫታ ?

#የካፑሌ_ሚስት
እረ ፡ እንዲህ ፡ አይደለም ፡ የሕዝቡ ጋጋታ ፡
ግማሹ ፡ ሮሜዎ ፡ ግማሹ ፡ ዡልዬት ፡
ግማሾቹም ፡ ፓሪስ ፡ እያሉ ፡ በጩኸት ፡
ወደ ፡ እኛ ፡ መቃብር ፡ ገቡ ፡ እየተጋፉ ።

#መስፍን
ነገሩን ፡ ንገሩኝ፡ ደግም ፡ ሆነ፡ ክፉ ።

#የመጀመሪያ_ዘበኛ
ልዑል ፡ ሆይ ፡ ያስተውሉ'ፓሪስን ፡ተገድሎ
እዩት ፡ ሮሜዎ ፡ መሬት ፡ ላይ ፡ ተንጋሎ ፡
ቀድሞ ፡ የሞተችው ፡ ዡልዬት ፡ ተመልሳ፣
እይዋት ፡ እሷ ፡ ደግሞ ፡ በደም ተለውሳ ።

#መስፍን
ይህ ፡ ዐመፅ ፡ እንደ፡ምን ፡ ሆኖ ፡ እንደ ፡ ተሠራ ፍጠኑ ፡ በቶሎ ፡ይደረግ ፡ ምርመራ

#የመጀመሪያ_ዘበኛ
የሮሜዎ ፡ ሎሌ ፥ ካንድ ፡ ካህን ፡ ጋራ ፡
እነሆ ፡ ተገኝቷል ፡ አሁን ፡ በዚህ ፡ ስፍራ ።

#ካፑሌ
ሚስቴ ፡ ተመልከቺ ፡ ልጃችን ፡ ተኝታ ፥
እዪው ፡ ደሟ ፡ ሲፈስ ሆዷ ላይ ፡ ተወግታ
አስተውዪው ይህ ጩቤ ከመጣበት ፡ ቦታ
ከሞንታግ ልጅ ላይ ነው ተመልከች አፎቱ
ባዶውን ፡ ይታያል ፡ ይግባሽ ፡ ምክንያቱ ።

#የካፑሌ_ሚስት
እባክህን ፡ ተወኝ ፡ እኔ ፡ አልችልም ፡ ማየት
ወይ፡ልጄ ፡ ወይ ልጄ ፡ ወይ፡ ልጄ ፡ ዝልዬት
ሐዘን ፡ ጨፈለቀኝ ፡ ውሃ ፡ ሆንኩኝ ፡ እኔ ፤
ይህንን ፡ ትልቅ ፡ ጕድ ፡ ይህንን ፡ ጭካኔ፡
ኣይችልም ፡ አይችልም። ሊመለከት ዐይኔ
(ሞንታግና ፡ ሌሎች ፡ ሰዎች ፡ መጡ) "

#መስፍን
ሞንታግ ፡ ወዲህ ፡ ቅረብ ፡ ተመልከተው ፡ አንተ ፡ልጅህን ፡ አስተውለው ፥ እየው ፡ እንደ ፡ ሞተ ።

#ሞንታግ
የልጅዋ ፡ መሰደድ ፡ ሆኖባት ፡ በሽታ ፡
ሚስቴ ፡ ሌሊት ፡ ሞተች በሐዘን ተጐድታ
ያሁን ፡ ሐዘኔ ፡ ግን በጣም ፡ ትልቅ መዓት
የባሰ ፡ ጐዳት፡ ነው ፡ የመጣ ፡ ለቅጣት ።

#መስፍን
እንባህን ፡ አግደው ፡ አትቸኵል ፡ ለማልቀስ
በፊት ፡ ምርመራውን ፡ ይገባል ፡ መጨረስ
ያመፁን ፡ ምክንያት፡ ምንጩን ፡ እንወቀው
ምርመራው ይጀመር አብረን ፡ እንዝለቀው
የተያዙት ፡ ሰዎች ፡ በፍጥነት ፡ ይቅረቡ ።

#አባ_ሎራ
እዚህ ፡ ያላችሁት ፡ አሁን ፡ ስታስቡ ፡
እኔ ፡ መገኘቴ ፡ በዚህ ፡ ዐመፅ ፡ ቦታ ፡
ያስጠረጥረኛል ፡ ገፍቶ ፡ በግዴታ ፡
ዳሩ ፡ ግን ፡ ነገሩን ፡ ልናገረውና ፡
ተረዱት ፡ ዕወቁት ፡ የኔን ፡ ንጽሕና ።

#መስፍን
ታሪኩን ፡ እንስማ ፡ በሉ ፡ ይናገሩ ።

#አባ_ሎራ
ሐተታ ፡ አላበዛም ፡ ልናገር ፡ ባጭሩ ፤
ረዥም ፡ አይደለም ፡ቀላል፡ ነው ምስጢሩ
መልካሙ ፡ ሮሜዎ ፡ ይህ አሁን ፡ የሞተው ለዡልዬት ፡ባሏ ነው በተክሊል ተጋብተው
ቃል ኪዳን ሞልተዋል ቈርበው እንደ ሕጉ
በሃይማኖት ሥራት ቃል፡ ኪዳን ሲያደርጉ
የተክሊሉን ፡ ሥራት ፡ ባርኮ ፡ የቀደሰው ፡
እኔው ፡ ራሴ ፡ ነኝ፤ አይደለም ፡ ሌላ ፡ ሰው
በዚያው ቀን ቲባልትን ቢገድለው ፡ ተፈርዶ
ከዚህ ፡ አገር ፡ ወጣ ፡ ሮሜዎ ፡ ተሰዶ፡
ዡልዬት ፡ ዘመዶቿ ፡ ይህንን ፡ ሳያውቁ ፡
ለፓሪስ ፡ ሊድሯት ፡ እሷን ፡ ቢያስጨንቁ ፡
በሐዘን ፡ አልቅሳ ፡ ነገረችኝ ፡ መጥታ ፤
ዘዴ ፡ ካልተገኘ ፡ በገዛ ፡ እጅዋ ፡ ሞታ ፡
ልትድን ፡ አሰበች ፡ ካገኛት ፡ ፈተና ፤
እኔም ፡ በዚህ ፡ ነገር ፡ በጣም ፡ አዘንኩና ፡
መድኀኒት ፡ ሰጠኋት ሕይወት ፡ አጠውልጎ
እንቅልፍ ፡ የሚያስተኛ እንደ ሞት ፡ አድርጎ
ከዚያም ፡ ለሮሜዎ ፡ ወረቀት ፡ ጽፌለት ፡
እንዲመጣ ፡አዘዝኩት ገሥግሦ በፍጥነት
ከእንቅልፋ፡ ስትነቃ የመርዙ ኃይል ፡ አልቆ
እንዲወስዳት ፡ ነበረ ውጭ ፡ አገር ፡ ደብቆ
የኔንም ፡ ወረቀት ፡ የወሰደልኝ ፡ ሰው ፡
የኛ ፡ ካህን ፡ ነበር ፤ እሱም ፡ ሳያደርሰው ፡
እክል፡ ስላገኘው ፡ በሄደበት ፡ ቦታ ፡
መልሶ ፡ አመጣልኝ ፡ ትናንትና ፡ ማታ ።
የዡልየት ፡ መነሻ ፡ ሌሊት ፡ ስለ ፡ ነበር ፡
እኔም ፡ በጨለማ ፡ መጣሁ ፡ ስደናበር ፡
አሳቤ ፡ ነበረ ፡ ሮሜዎ ፡እስቲመጣ ፡
ደብቄ ፡ ላቆያት ፡ ከቤት ፡ ሳላስወጣ ፡
ዳሩ፡ግን ፡ ገሥግሼ ፡ እኔ ፡ ከዚህ ፡ ስደርስ
ወድቀው ፡ አየኋቸው ፡ ሮሜዎና፡ ፓሪስ ።
እሷም ፡ ነቃችና ፡ ወዲያው ፡ ስትነሣ ፡
እግዜር ፡ ያመጣውን ፡ ብትቀበል ፡ ታግሣ
የሚሻል ፡ መሆኑን ፡ ላስረዳት ፡ ሞክሬ ፡
ከደጅ ፡ ድምፅ ሰማሁ ሳጥናናት በምክሬ
ለመንኳት ፡ እንድትሄድ ፡ እኔን ፡ ተከትላ ፥
ምክሬን ፡ አልሰማችም ቀረች እንቢ ፡ ብላ
እኔም ፡ የመጣውን ፡ ለማየት ፡ በኋላ ፤
ወጥቼ ፡ መጣሁኝ ፡ ይኸው ፡ እዚህ ፡ ቦታ
ያስረዳ፡ ነበረ ፡ የዡልዬት ፡ ሁኔታ ፡
ሐዘኗ ፡ መሆኑን ፡ በጣም ፡ የበረታ ።
ከዚያ በኋላ ፡ ግን ፡ የሆነውን ፡ ነገር ፡
አላየሁምና ፡ አልችልም ፡ መናገር ፡
ዡልዬት ፡ ሮሜዎን በተክሊል ፡ ማግባቷን
ታውቀዋለችና ፡ ጠይቁ ፡ ሞግዚቷን ፡
እንግዴህ ፡ ልቀጣ ፡ ቃሌ ፡ ቢገኝበት ፡
በውስጡ ፡ የገባ ፡ ሐሰትና፡ ውሸት

#መስፍን
ጻድቅ ፡ሰው ኣድርገን ፡እርስዎን ከማክበር
አቋርጠን ፡ አናውቅም የሮሜዎን ፡ አሽከር
በፍጥነት ፡ አቅርቡት ፡ ያየውን ፡ ይናገር ።

#ቤልሻጥር
የዡልዬትን ፡ መሞት ፡ ጌታዬ ፡ ብነግረው ፡
መርዶውን ፡ ሲሰማ ፡ ሐዘን ፡ አሰከረው ፡
ወዲያው ፡ ተነሣና ፡ እየገሠገሠ ፡
ሌሊት ፡ እዚህ ፡ ቦታ ፡ ከኔ ፡ ጋር ፡ ደረሰ ።
ይህንን ፡ ደብዳቤ ፡ ላባቴ ፡ ስጥ ፡ ብሎ ፡
እኔን ፡ እንዳልገባ ፡ በብርቱ ፡ ከልክሎ ፡
ትእዛዙን ፡ ባልፈጽም ፡ በሞት ፡ አስፈራርቶ
አየሁት ፡ ሲገባ ፡ እኔን ፡ እዚህ ፡ ትቶ ።

#መስፍን
ደብዳቤውን ፡ ስጠኝ እስቲ ፡ ልመልከተው
የፓሪስም ፡ አሽከር ፡ ይጠራ ወዴት ፡ ነው ?
(የፓሪስ • አሽከር ፡ ቀረበ) ።
ሌሊት ፡ በጨለማ ፡ ደግሞ ፡ ያንተ ፡ ጌታ ፡
እዚህ ፡ ለምን ፡ መጣ ፡ እመቃብር ፡ ቦታ ?

#የፓሪስ_አሽከር
አበባ ፡ ሊያስቀምጥ ፡ እመቃብሯ ፡ ላይ ፡
መጣና ፡ እኔንም ፡ እዚሁ ፡ ሁኜ ፡ እንዳይ ፡
አዞኝ ፡ እንድጠብቅ ፡ እዚህ ፡ እንድቀመጥ
ሰው ፡የመጣ እንደሆን ምልክት እንድሰጥ
ስጠብቅ አንድ፡ ሰው፡ መብራት ይዞ መጣ
አፍጨሁ ፡ ጌታዬም ፡ ከመቃብር ፡ ወጣ ።
ሁለቱ ፡ ሲዋጉ ፡ ይኸው ፡ እዚህ ፡ ስፍራ ፡
ቶሎ ፡ ሮጬ ፡ ወጣሁ ፡ ዘበኛ ፡ ልጠራ ።

#መስፍን
አምነን ፡ ለመቀበል ፡ እኛ ፡ የቄሱን ፡ ቃል ፡
ተመልክቼዋለሁ ፥ ደብዳቤው ፡ ይበቃል ።
የፍቅራቸው ፡ ነገር ፡ የዡልዬትም ፡ መሞት
ይኸው ፡ ይነበባል ፡ በደብዳቤው ፡ ጽፎት
ሁሉንም ፡ ገልጦታል ፤ ከዡልዬትም ፡ ጋራ
ለመሞት መምጣቱን ይኸው እዚህ ስፍራ
መድኀኒት የሚሸጥ ድኻ ሰው ፡ አግኝቶ
መርዝ
👎1