አትሮኖስ
270K subscribers
110 photos
3 videos
41 files
435 links
╔╦╦╦═╦╗╔═╦═╦══╦═╗
║║║║╩╣╚╣═╣║║║║║╩╣
╚══╩═╩═╩═╩═╩╩╩
ግጥሞች አዳዲስና ቆየት ያሉ የታዋቂ ደራሲያን መፅሐፍቶችን በ PDF እንዲሁንም
ያልተነበቡ ድርሰቶችን ግጥሞችን ታሪኮችን ያገኙበታል።


Contact. @atronosebot
please dont touch the leave button.😔😳😳
Download Telegram
#በፍቅር_ላይ_ሾተላይ


#ክፍል_አርባ_ሁለት


#ድርሰት_በትክክል_ገና

#ክፍል_ሶስት

#ትንሣኤ
በሁለቱ መንግስታት መካከል በተደረሰው ስምምነት መሠረት የምርኮኞች ልውውጥ የሚጀመርበት የመጀመሪያው ምዕራፍ......
የድሬዳዋ ከተማ አሸብርቃለች፡፡ ገንደቆሬ፣ ገንደገራዳ፣ መጋላ፣ ከዚራ፣ ለገሀሬ፣ ..... መንደሮች በሙሉ በደስታ ስቀዋል፡፡
በየመንገዱ ግራና ቀኝ ተተክለው ቀዝቃዛና፤ ነፋሻማ አየርን የሚረጩት ዛፎች በደስታ ተውጠው የሚደንሱ ይመስላሉ፡፡ በዚያች ምድር ላይ የተካሄደው ቀውጢ ጦርነት አልፎ፤ ያንን የመሰለ የሰላም አየር መተንፈስ መቻል ዳግማዊ ልደት ነው፡፡
በሐረርጌ ምድር፡፡ በደገሀቡር፣ ቀብሪደሀር፣ መራራሌ፣ በሺላቦ፣
ደቦይን፣ በቆራሄ አሸዋማ ሜዳ፣ በኦጋዴን በረሃ፣ በካራማራ ተራሮችና በሌሎችም ሺህ ሌሊት ሺህ መአልት የፈሰሰው ደም፣ የተከሰከሰው አጥንት፣ያስገኘው ውጤት፡፡
በዚያን ቀውጢ ሰዓት ላይ ለዳር ድንበር ሲሉ ከጠላት ጋር እየተናነቁ አኩሪ ገድል የፈጸሙት፤ በደማቸው ማህተም፤ በአጥንታቸው ክስካሽ፤ ምድሪቱን ያቀሉት...የመስዋዕትነት ፈርጦች! የሚጠበቁበት ዕለት......

ሰማዩ በዚያን ቀውጢ የጦርነት ወቅት በኢትዮጵያ አየር ሃይል የተሠራውን አስደናቂ ትርኢትና ተአምር አፍ አውጥቶ ሊናገር፣ የታሪክ ምስክርነቱን ሊሰጥ፣ የተዘጋጀ ይመስል አጉረመረመ፡፡ ለሚወዷት እናት አገራቸው ዳር ድንበር ሲሉ የተፋለሙና ልዩ ልዩ ጀብድ ከፈጸሙ በኋላ በጠላት እጅ ወድቀው በባእድ ሀገር በምርኮኝነትና፤ በእስረኝነት ለበርካታ
አመታት ከቆዩ በኋላ በሁለቱ መንግስታት መካከል በተደረሰው ስምምነት መሰረት ዛሬ ወደሚያፈቅሯትና፤ ወደሚወዷት፤ እናት አገራቸው የሚመለሱበት እለት ስለሆነ፤ እነዚህን ውድ የሀገር አለኝታዎችና፤ ጀግኖች፤በልዩና፤ በደማቅ አቀባበል ፤ ሊቀበል ህዝቡ የአውሮፕላን
ማረፊያውን አካባቢ አጥለቅልቆታል....
ማርሽ የሚያሰማው ሠራዊት በተጠንቀቅ ቆሞ ይጠባበቃል።ባንዲራዎች ይውለበለባሉ፡፡ ህዝቡ ይሯሯጣል፡፡ ይራወጣል። ሰማይ ሰማዩን እያንጋጠጠ ይመለከታል፡፡
አንዳንድ ጊዜ ትላልቅ አሞራዎች ያሳስታሉ፡፡ የሁሉም ልብ ተንጠልጥሏል፡፡ እነማን ይሆኑ?! ሞቱ ተብለው ደረት
የተመታላቸው፣ ተዝካር የተበላላቸው፣ ማን ያውቃል? በህይወት ሊገኙ
ይችሉ ይሆናል፡፡ ይህ ጦርነት በተካሄደባቸው ብዙ አገሮች በተደጋጋሚ
የታየ ክስተት ነው፡፡
ሰዓቱ ደረሰ፡፡ ሰማዩ እንደገና በከፍተኛ ድምፅ አጉረመረመ፡፡አውሮፕላኗ በርቀት ታየች፡፡ ከዚያም እየጐላች ፤እየጐላች፤ መጣችና፤በማረፊያው ላይ እየዞረች፤ ማንዣባብ ጀመረች።
የሰው ጩኸት ሁካታ... ግርግር... ትርምሱ...ሌላ ሆኗል፡፡ማርሽ በረጅሙ ይሰማል፡፡ አውሮፕላኗ አዘቀዘቀች..... ከዚያም አኮበኮበችና አረፈች፡፡
ጀግኖች የታደሙባት አውሮፕላን! ለዳር ድንበሯ ሱሉ ደማቸውን ያፈሰሱላትን፣ በእስር የማቀቁላትን፣ ጥለው የወደቁላትን፣ ታስረው የተገረፉላትን፣ የጦር ምርኮኞችን ይዛ ይሄውና አውሮፕላኗ መሬት ላይ አረፈች....
የአውሮፕላኗ በር ተከፍቶ አንድ ረጅም፧ ቀጭን፤ መነጽር ያደረገና በአየር ኃይሉ ውስጥ በጦር ጄት የጠላትን ሃይል ድባቅ
በመምታት በደማቅ ቀለም ታሪክ ያስመዘገበ ምርኮኛ ብቅ አለ፡፡ማርሹ ይሰማል፡፡ እልልታው ቀለጠ!! ግማሹ በሲቃ ያለቅሳል፣ይፈነድቃል፡፡ ምርኮኞቹን ለማየት ሰው በሰው ላይ ይንጠላጠላል፣
ትዕይንቱ ብዙ ነው፡፡ ከዚያም የተዘጋጀውን እቅፍ አበባ ምርኮኛው ተቀበለ፡፡
ምርኮኞቹ ከአውሮፕላኗ እንደወረዱ መሬቷን ይስማሉ። አፈሯን ይልሳሉ፡፡ ያለቅሳሉ፣ ይንከባለላሉ፡፡ የደስታ እንባ... የናፍቆት እንባ... የትዝታ እንባ...
ላለፉት አስራ አንድ ዓመታት ከአገር፤ ከወገን፣ ከቤተሰብ ጋር ተለያይተው ፤ የብቸኝነትንና የመከራ ኑሮን ሲገፉ ከቆዩ በኋላ፤የሚወዱትንና፤ የሚያፈቅሩትን፤ ህዝብና አገር መቀላቀል ዳግም መወለድ
ነውና፤ ምርኮኞች ዳግም የተወለዱ ያህል በደስታ ሰከሩ። እንደዚያ ዳር ድንበርዋን ሊያስከብሩላት፤ ከጠላት ጋር አንገት ለአንገት ተናንቀው፡ ሳንጃ ለሳንጃ ተሞዣልቀው፡ ጥለው የወደቁላት፡ የውድ ሀገራቸውን ለም አፈር ለማሽተት በመቻላቸው በደስታ የሚሆኑትን አጡ ...ህዝቡም በእልልታና በሆታ የጀግና አቀባበል አደረገላቸው፡፡ ደስ የሚል ከህሊና የማይጠፋ የአቀባበል ሥነ ሥርዓት......
ለተወሰኑ ቀናቶች በድሬዳዋ ከተማ እረፍት አድርገው ከቆዩና መንፈሳቸው ከተረጋጋ በኋላ፣ በየክፍለ ሀገሩ የሚገኙ ዘመዶቻቸውን ሊቀላቀሉ የቸኮሉት ቀድመው ተንቀሳቀሱ፡፡


እለተ ቅዳሜ! አዲስ አበባ!! የኢትዮጵያ ዋና ከተማ! ቀዝቃዛ ንፋስ ይነፍስባታል ። በተለይ የባህር ማዶው ዛፍ ለቅዝቃዜው የራሱን ከፍተኛ ድርሻ አበርክቷል፡፡
ባቡሩ መንገደኞቹን ጣቢያው አራገፈ፡፡ ግፊያው ለጉድ ነው፡፡ግማሹ ሲመጣ ግማሹ ሲሄድ... የገቢና ወጪ መንገደኞች ምልልስ የማያቋርጥበት አምባ......
ጊዜው ለዐይን ያዝ ማድረግ የጀመረበት ሰዓት ነው፡፡
አንድ ቁመቱ ረዘም ያለ፣ ሰውነቱ በበረሃ ግርፋትና በእስር ስቃይ ምክንያት የተለበለበ ግንድ ቢመስልም፤ በሰላሙ ጊዜ ማራኪ መልክና ቁመና እንደነበረው አሁንም በግልጽ የሚታየው ትክለ ሰውነቱ
ዐቢይ ምስክርነቱን የሚሰጥለት፤ ከሲታ ሰው ከባቡሩ ወረደ፡፡
ደረቱ ሰፋ ያለ፣ ፀጉረ ዞማና ዐይኖቹ ጐላ ጐላ ብለው የሚታዩ ረጅም ሰው ነው፡፡ ሻንጣ አንጠልጥሏል፡፡ ከተሰጠው የኪስ ገንዘብ ውስጥ አብዛኛውን ያዋለው ለሁለት ሴቶችና፤ ለአንድ ወንድ የሚሆኑ ልብሶችን በመግዛት ነው፡፡ ከባቡሩ ወርዶ፤ በአምባሳደር ቲያትር በኩል መጥቶ ፤ ወደ ኦርማ ጋራዥ አቀና፡፡ የሚራመደው በደመነፍስ ዐይነት ነው፡፡
በህልም ዓለም የሚራመድ ይመስላል፡፡
እሱ እራሱ የሚያየው ነገር እውነት መሆኑን ተጠራጥሯል።ግራና ቀኙን በዓይኑ ያማትራል፡፡ ሰዎችን ይቃኛል፡፡ ምናልባት የማውቀው ሰው ካገኘሁ በሚል ግምት ነው፡፡ ግን ማንም የሚያውቀው ሰው አላገኘም፡፡ ድሮ የሚያውቁት ሲያዩት እንኳን፤ በቀላሉ ሊለዩት አይችሉም፡፡ ተለውጧል፡፡ ተጉሳቁሏል፡፡
መንገዶቹ የጠበቡ፣ ቤቶቹም ከምዕተ ዓመት በፊት የነበሩ መስለው ታዩት፡፡ በየመንገዱ ላይ ከሚያያቸው ሰዎች ውስጥ ሶስት ሰዎችን ለማግኘት በናፍቆትና በጉጉት ደጋግሞ ይቃኛል፡፡
የሱ ብርቅዬ፤ ድንቅዬዎች፡፡ ልዩ የህይወቱ ቅመሞች፡፡ የተዳፈነ የናፍቆቱ እምቅ ሊፈነዳ ተቃረበ፡፡ ልቡ ተሸበረ... እየተቃረበ ሲመጣ ልቡ ድው ድው የሚል ድምጽ ሰጠ፡፡ ትንፋሽ አጠረው፡፡
እጅግ አስገራሚ ነው! አስደናቂ
የማይጠበቀው ሰው ፤ እንደዚህ ባልተጠበቀ ሰዓት ከች! ሲል፤ እነሱ
ከአንጀቱ የሚያፈቅራቸው፣ የሚወዳቸው፣ የሚሞትላቸው ቤተሰቦቹ እንዴት ሆነው ይሆን? የሚወዳት ሚስቱ፣ የሚወዳቸው ልጆቹ እንዴት ሆነው ይሆን? ሲለያቸው በነበራቸው ዕድሜ ላይ አስራ አንድ ዓመት ሲጨመርበት የትየለሌ ነው፡፡ ምን መስለው ይሆን?
አቤቱ ፈጣሪ ያንተ ተአምር እንዴት ተወርቶ ያልቅ ይሆን? አደራህን ሁሉንም ለአንድ ቀን እንኳን ቢሆን ዐይናቸውን አይቼው
እንድሞት እርዳኝ፡፡ አንተ ታውቃለህ፡፡
ወባ እንደያዘው ሰው እየተቃረበ መጣ፡፡ ቤቱ ጋ ሲደርስ ሰውነቱ ተንዘፈዘፈበት :: ልቡ በፍጥነት ይመታ ጀመር፡፡
ግቢው ...ያ ...ግቢ የሚወደው ግቢ...እዚያ ውስጥ ያሉት እነ.. መራመድ አልቻለም፡፡ ቆመ፡፡ እንደሀውልት ተገትሮ ቀረ፡፡ ከዚያም ለዘመናት በወስጡ ሲንተከተክ የነበረው እንባ በድንገት ገንፍሉ ወጣ፡፡
ከደስታ ብዛት ስቅስቅ ብሎ አለቀሰ፡፡ ቤቱን አየው፡፡ ልጆቹን አቅፎ የሳመበትን፣ ከሚያፈቅራት ባለቤቱ ጋር ደስታን ያሳለፈበትን፣ በመጨረሻም ወደ ጦርነት ሲሄድ ከቤተሰቦቹ ጋር ተላቅሶ
#የፍቅር_ሰመመን


#ክፍል_ሶስት


#ድርሰት_ሲዲኒ_ሼልደን


#ትርጉም_ብርሃኑ_በላቸው


...የሴንቸሪ ሲቲ መንገዶች በሙሉ ውር ውር በሚሉ መኪናዎች ቢሞላም የእግረኛ መንገዶቹ ግን ጭር ያሉ ነበሩ ምክንያቱም ብዙውን ጊዜ ሰዎች
በሎስ አንጀለስ በእግራቸው አይሄዱም፤ በተለይ ደግሞ በዝናብ ውስጥ መሄዱ የማይታሰብ ነገር ነው። እርግጥ የሚጠብቃት ሴት አንድ አንዴ
በእግር ትጓዛለች፡፡ “ዛሬስ ምናልባት በእግሯ ወደ ቤቷ መሄድ ብትችልስ?

“በይ ውጭ እኮ ውጭ የት ነው ያለሽው?” እያለ በውስጡ ሲያመላልስ
በድንገት ሴትየዋ ከህንፃው ስትወጣ ልቡ ደነገጠ፡፡ ምክንያቱም አልተዘጋጀም
ነበር፡፡ ልቡ በደንብ እየደለቀም እሷን መመልከት ጀመረ፡፡

ኮቷንም በቀበቶዋ ሸብ አድርጋ እና ራሷን አቀርቅራ በፍጥነት ወደ መንገዱ መሸጋገሪያ የምትሄደውን ሴት እየተመለከተ “እርዱኝ!” እያለ ጮኸ፡፡
በእርግጥ ድምፁ ያን ያክል ይሰማት አይሰማት እርግጠኛ አይደለም።
ቢሆንም ግን ዛሬ ይህቺ ሴት ልትሰማው ይገባል “ኧረ እርዱኝ!” አለ በድጋሚ፡፡

ይሄኔም ሊዛ ፍላንገን ወደ እሱ ዞር አለች ከቆሻሻው መጣያ አጠገብ አንድ ቀጭን ልጅ ይሁን ትልቅ ሰው መሆኑ የማይለይ ሰው አጎንብሶ ቁጢጥ ብሏል፡፡ ወደ እሱ ስትራመድ ስላያትም “እባክሽን 911 ደውይልኝ! ፖሊስ ጥሪልኝ፡፡ የሆነ ሰው በጩቤ ወግቶኛል።” አላት፡፡

እሷም “በእግዚአብሔር ስም” ብላ ስልኳን አወጣች እና እየደወለች ወደ
ልጁ ቀረበች፡፡ “ምን ሆነህ ነው? ደህና ነህ?” ብላ ጠየቀችው። ልጁ አጎንብሶ
ሆዱን በማጠፍ እጁን ሆዱ ላይ አስቀምጦታል፡፡ ኮፍያ ያለው ሹራብ ነው
የለበሰው:: ሹራቡ ላይ የዘነበበት ዝናብም ፊቱን እና ፀጉሩን አርሶታል።

“የአደጋ ጊዜ ተጠሪ ምን ነበር የፈለጉት?”

“ፖሊስ ይድረስልኝ፡፡” ብላ ሊዛ በማስከተል “ አምቡላንስም ጭምር” አለች እና አናቱን በእጇ እየነካች “አይዞህ እርዳታ እየመጣልን ነው። ምንህን ነው
የተጎዳኸው?” ብላ ጠየቀችው፡፡
ልጁም ፈገግ ብሎ ሲያያት ሊዛ የልጁን ፊት አይታ በጣም ቀፈፋት እና ለማስታወክ ዳዳት ከሹራብ ኮፍያው ሥር ያለው የልጁ ፊት የሰው አይመስልም፡፡ ፊቱ ፍፁም አረንጎዴ ከመሆኑም በላይ አጥንቱ ገጧል። ይባስ
ብሎም ተቆራርጠው የተንጠለጠሉ የበሰበሱ ነገሮች ከፊቱ ተንጠልጥለዋል። ልትጮህ አፍዋን ብትከፍትም አንድም
ሊወጣላት አልቻለም።
911 ላይ የሚያወራት ሰውም “የእኔ እመቤት የት እንዳለሽ ልትነግሪኝ
ትችያለሽ?” ብሎ ጠየቃት። ባለ አረንጎዴው ፊትም በድንጋጤ የተከፈተውን የሊዛን አፍ እየተመለከተ ከሆዱ ስር ስለታም ጩቤ አወጣ እና ሆዷ ላይ ሰመጠጠው። ይሄኔም አየሩን የሚሰነጥቅ የእሪታ ድምፅ ከሊዛ አፍ ሊወጣ በቃ። በድጋሚም ስለቱን ከሆዷ ነቅሎ በጣም በሀይል ሲሰመጥጥባት እጁ ከጩቤው ጋር ተያይዞ ወደ ውስጥ ስለገባ የሆነ የሚሞቅ ርጥበት እጁ ላይ
ተሰማው።

“እባኮትን ያናገሩኝ? ይሰማዎታል? ምንድን ነው የተከሰተው? የት ቦታ
እንደሚገኙ ሊነግሩኝ ይችላሉ?” መሬት ላይ ከእጇ አምልጦ ከወደቀው ስልክ
የሚወጣ የ911 ሰውዬዋ ድምፅ ነው። ዶ/ር ኒኪ ሮበርትስ የX ክላስ
መርሴዲስ መኪና የሌዘር ወንበር ላይ ተለጥጣ የገራጁ በር እስኪከፈት
እየጠበቀች ትገኛለች፡፡ መንገዱ ክፍት ከሆነ በሀያ ደቂቃ ውስጥ ብሬንትውድ
ውስጥ ወደሚገኘው መኖሪያ ቤቷ ትደርሳለች። ምንም እንኳን ረጅም እና
ባዶ የሆነ ህይወት ቤቷ ውስጥ ቢጠብቃትም ቴሌቪዥን በማየት በአንድ
ጠርሙስ አልኮል ባዶ ህይወቷን ትሞላለች:: እንኳን አንድ ምሽት፣ ሁሉ
ነገር ያልፍ አይደል?

ኒኪ መኪና ውስጥ እንዳለች የዛሬው ውሎዋ ላይ ሊዛን በሙሉ ልቧ ስላላደመጠቻት የጥፋተኝነት ስሜት ተሰምቷታል። ታካሚዋን ብትወደውም
ሆነ ብትጠላው ስራዋን በአግባቡ ሰርታ ስላልወጣች በእውነትም ቅር ብሏታል። የገራዥ በር በቀስታ መከፈት እንደጀመረ ኒኪ ወደ በሩ ነዳች እና ከህንፃው ወጥታ ወደ ጠባቡ መንገድ ገባች።

ሊዛ የበሩን መከፈት እና መዘጋት ድምፅን እና የመኪና ሞተር ድምፅ ስትሰማ በነበረበት ጊዜ ከሆዷ እና ከደረቷ ደሟ እንደጎርፍ ይወርድ ነበር።
መሮጥም ሆነ መቆም አልቻለችም:: ማድረግ የምትችለው አንድ ነገር ቢኖር
ጉሮሮዋ እስኪሰነጠቅ ድረስ መጮህ ነበር። በስለት የወጋት ሰው በስለቱ
እጇን፣ ጡቷን እና ጭኗን ጭምር ደግሞ ደጋግሞ ይቆራርጣታል። ቶሎ
ሊገድላት አልፈለገም እና ልክ ድመት የያዘችውን አይጥ እያሰቃየች
እንደምትዝናና ሁሉ እሱም የሚያደርገው ያንን ነበር።

የመኪናው ሞተር ድምፅ እየጨመረ መምጣትን ስትሰማ ግን በተስፋ
ተሞልታ ትንፋሿን ሰበሰበች። ከዚያም በህይወቷ ጮሀ የማታውቀውን
ጩኸት ጮኸች። በጩኸቷ መሀል ላይ ደሟ ጉሮሮዋ ውስጥ ሲንተከተክ
ታውቋታል፡፡ አይኗም ተጎልጉሎ የሚወጣ ሁላ መስሏታል።
የመኪናው መብራት ወደ እነርሱ አቅጣጫ አበራ። ይሄኔም የሚወጋት ሰውዬ እሷን የመውጋት ስራውን አቆመ፡፡ የመኪናው ሞተርም ድምፁ ጠፋ።

ሊዛ ዶ/ር ሮበርትሰን አይታኛለች ከዚህ ነፍሰ ገዳይም ታተርፈኛለች ብላ
እረፍት ተሰማት። ነፍሰ ገዳዩም የያዘውን ጩቤ መሬቱ ላይ ጣለው፡፡ የልብ
ምቷ ቀስ እያለ ሲመታ ይሰማታል፡፡ ባለጩቤው ሰው ግን ጥሏት ሊሮጥ
አልቻለም። የመኪናው በርም ሲከፈት አልሰማችም::

ሁለት... አምስት... አስር ሰኮንዶች አለፉ፡፡ ምንም የተከሰተ ነገር ግን አልነበረም፡፡ “እንዴ... ምንድን ነው ነገሩ?”

የመኪናው ሞተር ድምፅ በድጋሚ ተሰማት፡፡ አይሆንም! ጠባቡን መታጠፊያ የመኪናው መብራት አጥለቀለቀው፡፡
“አይሆንም! አይሆንም! እባክሽን ድረሺልኝ! ስለእግዚአብሔር ብለሽ
ድረሺልኝ!!
የኒኪ ብርማ መርሴዲስ መኪና በጎን በኩል አለፋቸው እና ወደ ዋናው
መንገድ ውስጥ ገባ፡፡የበሰበሱ አጥንታማ እጆችም የሊዛ አንገት ላይ ተጠመጠሙ። ከፊት ለፊቷ አብረቅራቂው የገዳይ ጩቤ በእሷ ደም ጨቅይቶ ይታያታል።

ሊዛ “የት ነበር ያቆምነው?” ብሎ ገዳዩ ሰው እየገለፈጠ የተናገራት ንግግር እና አስቀያሚ ሳቁን ለመጨረሻ ጊዜ ነበር የሰማችው።
።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።
ታች እንግዳ ማረፊያ ክፍሉ ስለሚጠብቁት ሁለቱ ታጣቂ የግል
ጠባቂዎች እያሰበ ጥሩ ስሜት እንዲሰማው ፈለገ። አልሰራም፡፡ ጥሩ ስሜት አልተሰማውም፡፡ በመቀጠል ደግሞ ቴራፒስቷን ራቁቷን አሰባት። ይሄ
ሳይሻል አይቀርም፡፡ ዶ/ር ኒኪ ሮበርትስ ስሜታዊ ሰው ነች ብሎ ያስባል።
ግራጫ አጭር ቀሚሷን ወደ ላይ ገፋ አድርጎ ዳሌዋን... አሰበ። ቦዲዋ
ተከፍቶ... “ኡፍ ደስ የሚል ነገር ነው...

ካርተር ከእኔ ጋር ነህ?” የሚለው ድምፅ ከሀሳቡ አነቃው። ድምፅዋን ሲሰማ ፊቱ ቀላበት፡፡ በመቀጠል ደግሞ ግራ ተጋባ፤ ለጥቆም ኮስተር አለ፡፡ስኬታማ የኢንቨስትመንት ባንከር፣ ወጣት የተማረ እና በጣም ሀብታም ሰው ነው። ሥራ ቦታው እና ሌሎች ቦታዎች ላይ ሁሉ ካርተር ሰዎችን በትዕዛዝ ቁጭ ብድግ ያስደርጋቸዋል፡፡ የሚፈልገውን ነገርም ሊያሟሉለት የሚራኮቱለት አይነት ሰው ነው። በተለይ ደግሞ ሴቶችን በሙሉ ስልጣን ውስጥ ሆኖ ነው የሚያዛቸው፡፡ አሁን እዚህ ቦታ ላይ ግን ልክ እንደ አንድ
ረባሽ ተማሪ ስሙን ስትጠራው ምቾት አልተሰማውም።
“ትላንት ማታ ምን አየሁ ብለህ እንዳሰብክ ደግመህ ንገረኝ እስቲ” “ሀሳቤ አይደለም! እንዴ እኔ ያየሁትን ነገር አይቼያለሁ። እኔ እብድ አይደለሁም!”
ብሎ ተበሰጫጨ እና ጥቅጥቅ ቡናማ ፀጉሩን ሞነጫጨረው፡፡

“እኔ እንደዛ አላልኩም” ብላ ድምፅዋን በማለስለስ ቀጠለች እና “አንዳንዴ ጤነኛ የሆኑ ሰዎች ሁሉ እንደዚህ አይነት ነገር ሊገጥማቸው ይችላል። እኔ እራሴ አንዳንዴ እንደዚያ
#ያልታበሱ_እንባዎች


#ክፍል_ሶስት


#ድርሰት_በአሰፋ_በቀለ_ገየሱስ


....ዕለቱ የህዳር ወር የመጨረሻው ማክሰኞ ነው የአስቻለው ከንፈሮች ከሔዋን ከንፈሮች ጋር ከተገናኘ ሃምሳ ሁለተኛ ቀን። ሔዋን ቀጠሮ አክብራ ከቀኑ ስምንት ሰዓት ላይ ከአስቻለው ቤት ደረሰች፡፡ አስቻለው ሔዋንን ከወስጥ አድርጎ ቤቱን ሲዘጋ ተሰምቶት የነበረ ደስታ አይረሳም።

በዚያ ዕለት ሔዋንን እንደ እንግዳ ወንበር ላይ ቁጭ በይ አላላትም፣
አንገቷን እቅፍ አድርጎ በቀጥታ ወደ አልጋ ወሰዳት፡፡ አልጋ ላይ ቁጭ ብለው ትንሽ ከተሟሟቁ በኋላ ስሜት በራሱ ሀይል ሲገፋቸው አንገት ለአንገት እንደተቃቀፋ፥ከንፈር ለከንፈር እንደተያያዙ ወደ ኋላ ከንብል አሉ፡፡ ጫማዎቻቸውን አወላልቀው
ወደ መሀል አልጋው ወጡና በሰፊው የፍቅር ሜዳ ላይ ሰፈሩ፡፡
ጉዞው ቀጠለ፡፡ ከንፈሮች በስራ ተጠመዱ፡፡ ዓይኖች ተስለመለሙ ትንፋሽ በረከተ፡፡ ገላጋይ የማያስፈልገው ትንቅንቅ ተጀመረ፣ የአስቻለው ቀኝ እጅ የሔዋንን
አንገት አቅፎ ግራው ደግሞ ሌላ ሥራ ያዘ። ከሔዋን ፀጉር ጀምሮ ማጅራቷን ይጎበኝና በወገቧ ላይ እየተስለክለክ ወደ ዳሌና ጭኖቿ ይወርዳል። ላይ ላዩን እንደ
ወረደ ሁሉ ወስጥ ውስጡን ለመመለስ በማሰብ ቀሚሷን ሰብሰብ እያደረገ ወደ
መሀል ጭኖቿ ጎራ ሊል ይቃጣዋል፡፡ ነገር ግን የሔዋን ጭኖች ወይ ፍንክች!!እንደገና ከላይ ይጀምራል፡፡ ይወርድ ይወርድና በአሰበው መንገድ ለመመሰስ ሲሞክር አሁንም ተቃውሞ ይገጥመዋል፡፡ ለሶስተኛ ጊዜ ሞከረ:: የሔዋን ጭኖች ግን
አልበገር አሉ።
በአራተኛው ጊዜ ከንፈሮችም ድንገት ተላቀቁ:: ሔዋን ወደ ቀልቧ ተመልሳ ኖሮ ድንገት ፍንጥር ብላ በመነሳት አልጋው ላይ ቁጭ አለች። አስቻለውም አልዘገየም፣ ሔዋን በተነሳችበት ቅፅበት እሱም ፍንጥር ብሎ ጭራሽ ከአልጋው ላይ ወደ መሬት ወረደ:: ፊትለፊቷ ቆሞ በነጭ ካኒተራው ላይ ደረቱን እያሻሽ
"ስሜቱ አልገባሽም አይደል ሔዩ" አላት በስሜት ውስጥ ሆኖ
ቅልስልስ እያል፡፡
"ገብቶኛል"
"ታዲያ ለምን ታስጨንቂኛለሽ?"
"እኔም ስለጨነቀኝ፡፡
«እንዴት?"»
«የእናት እደራና የእህት ማስጠንቀቂያ ስላሉበኝ»
“አልገባኝም ሐዩ!
«ና ቁጭ በል ልንገርህ»
አስቻለው ፈጥኖ ከአጠገቧ ቁጭ አለ። በመሀል ሔዋን በሀሳብ ጭልጥ ብሳ ሄደች:: ያኔ በነሐሴ ወር አጋማሽ ላይ ከሸዋዬ ጋር ጠዋት ከክብረ መንግሥት ወደ
ዲላ ሊመጡ ሲሉ ማታ በዝግጅት ላይ በነበሩበት ወቅት ሽዋዩ ሔዋንን እፊቷ ቁጭ አድርጋ ከእናቷ ጋር የተነጋገሩት ነገር።
ስሚ እማዬ » ብላ ነበር ሽዋዬ ወሬ የጀመረችው። «ይቺን ሔዋንን
ከአሁኑ ምክሪልኝ:: ዲላ የቡና አገር ነው ሀብታም ሁሉ ሰው በገንዘብ መግዛት ይፈልጋል:: እሷ ደሞ ቆንጆ ስለሆነች በገንዘብ እያታለሉ ትምህርቷን አስትተው ብልግና ሊያስተምሯት ይችላሉ፡፡ ይህ ከሆነ ደግሞ ህይወቷ ሊበላሽ ይችላል። እኔም ብሆን እንኳን ብልግና ፈጽማ ፡ የወንድ እጅ ጨበጠች ያሉኝ ዕለት ባለጌሽን አምጥቼ አስረክብሻለሁ።» ብላቸው ነበር፡፡ እናቷ ከተል እንዲህ ዓይነት ብልግና ትፈጥማለች ብዬ አልገምትም::
ያን ያህል ለፍቼ አሳድጌታለሁና
ክብሯን ጠብቃ ወግ ማረግ ታሳየኛለች ብዬ እጠብቃለሁ፡፡ ያ
ሳይሆን ቀርቶ ብልግና ፈጥማ አንቺ ወደኔ ብታመጫት እኔም የዚያኑ ዕለት ገደል ገደል ገብቼ እሞትና ቀብረሽኝ ትመለሻለሽ በማለት ተናግረው ነበር። ሔዋን ይህን የናቷን አደራና የእህቷን የማስጠንቀቂያ ቃል በሀሳቧ እያዳመጠች በነበረችበት ወቅት
«እስቲ ያስጨነቀሽን ነገር ንገሪኝ ሲል አስቻለሁ ከሀሳቧ ቀሰቀሳት፡፡
«ለመኑ ገርል መሆኔን ታውቃለህ?» አለችው ድንግል
መሆኗን ስትገልፅለት፡፡

«ኦ!» አለ አስቻለው ያላሰበው ነገር ሆኖበት።
«አትጠራጠር»። አለችውና ሔዋን እናቷ የጣለችባትን አደራና እህቷ ሸዋዬ የሰጠቻትን ማስጠንቀቂያ በዝርዝር አስረዳችው፡፡
ያ እንደ ብረት ግለ" የነበረ የአስቻለው ሰውነት ድንገት ቅዝትዝ ብርድ! ስንፍናና አለ።
«አደራ የምልህ አስቹ!» ስትል ቀጠለች ሔዋን። «ይህን የፍቅር ጉዳያችንን አንድ ቀን እታ አበባ የሰማች እንደሆነ መግቢያ ቀዳዳ የለኝም፡፡ ስለዚህ ሚስጥራችንን ከታፈሱና ጓደኞችህ" በቀር ሌላ ማንም ስለማያውቅ ሁሉም
በሚስጥር እንዲይዙልን አደራ እንድትላቸው ነው። እለችው::
አስቻለው በሁኔታው ተገርሞ ግንባሩን ይዞ መሬት መሬት ሲያይ ቆየና ድንገት ብድግ ብሎ ሔዋን ፊት በመቆም «እስቲ ወደኔ ነይ ሒዩ!» አላት፡፡
ሔዋንም ቡድግ ብላ በመቆም የአስቻለውን ዓይኖች ማየት ጀመረች፡፡
አስቻለው በሁለት እጆቹ የሔዋን ትክሻና ትክሻ ያዝ አድርጎ ቁልቁል
እየተመለከታት፡ ቃል ልገባ ነው ሐዩ፡»
«ምን ብለህ?»
የበሕይወት እስካለሁ ድረስ ፍጹም አልለይሽም። ከሠርጋችንም በፊት
ምንም አላደርግሽም» አላት፡፡
«እሺ» አለችው ሔዋን፡፡
አንገት ለአንገት ተቃተፉ። ምናልባት በሁለተኛው የህይወት ምዕራፍ ውስጥ እንደ ገቡ ታውቋቸው ሳይሆን አይቀርም ሆዳቸው ባብቶ ሁለቱም ተላቀሱ።
ይህ ዓይነቱ የፍቅር ከመሰራረት ሂደትና በውስጡ ያለው የሔዋን አደራ ነው ዛሬ አስቻለውን የከበደውና መንፈሱን ወጥሮ ነፍሱን ያስጨነቃት። አዎ
ተጨነቀ። ሔዋን በተፈጥሮ ፈሪና ሽቁጥቁጥ መሆኗን ያውቃል፡፡ ዛሬ በሸዋዬ ፊት እንደ ጭብጦ ጭርምትምት ብላ ታየችው:: ችግሩን በምን መላ ሊፈታው
እንደሚችል ግራ ገብቶት ፍዝዝ ትክዝ እንዳለ በዋርካው ምግብ ቤት ለብዙ ጊዜ የእራት ሠዓት ደርሶ ኖሯል። ድንገት ጓደኛው በልሁ በበር በኩል ወደ እሱ ሲያመራ አየወ፡፡ በልሁ ቁመቱ፡፡ ዘለግ ሰውነቱም ፈርጠምጠም ያለ ነው፡፡ ሰፋ ባለ የቀይ ዳማ ፊቱ ላይ በትር ወስሉ የተገተረው አፍንጫው ግርማ ሞገስ
አላብሶታል:: ዓይኑ ጎላ ጎላ ያለና ፈገግ ሲል ጥርሱ የሚያምር ነው:: ከውጭ ሲመጣ አስቻለው ትክዝ ብሉ በርቀት ዓይቶት ኖሮ ቀረብ ብሎ ሲያጤነውም ስሜቱ
መመሳቀሉን በመገንዘብ፡ ምነው ይክተር? ሰላም አይደለህም እንዴ?» አለና ሰላም ብሎት ከአጠገቡ ቁጭ አለ፡፡ አስቻለው ነርስ ስለሆነ ጓደኞቹ ብዙ ጊዜ ይክተር አያሉ በመጥራት ያሾፉበታል፡፡......


💫ይቀጥላል💫
#ትኩሳት


#ክፍል_ሶስት


#በስብሐት_ገብረ_እግዚአብሔር

...በካፌ ዶርቢቴል በኩል ሳልፍ ሉልሰገድ ከዚያ ወጣ። ቀይ ፊቱ
ደም ለብሷል። ጉልህ ዓይኖቹ ጉድጓዳቸው ውስጥ ይገላበጣሉ። በጣም ተናዷል።

“ምን ሆንክ?» አልኩት
"ይህን ተካ አስታግስልኝ፣ አለዛ አንድ ቀን እገድለዋለሁ» አለኝ
“ምነው?»
"ባገኘኝ ቁጥር ያበሽቀኛል። ላብድ ነው»
«ለምን ሁለተኛ እንዳታናግረኝ አትለውም?»
የተዘረዘሩ ጥቃቅን ጥርሶቹን በተሸነፈ የንዴት ሳቅ እያሳየኝ
ቢያንስ አስር ጊዜ ብየዋለሁ» አለ ሁለተኛ ያናገርከኝ እንደሆነ፣ ወይ ለፖሊስ እነግራለሁ ወይ እገድልሀለሁ ብዬዋለሁ።
ደጋግሜ ደጋግሜ ነግሬዋለሁ፡፡ ሰድቤዋለሁ»

«ታድያስ?»
በሚቀጥለው ጊዜ ሲያገኘኝ ያነጋግረኛል። ትንሽ ካናገረኝ በኋላ
ያበሽቀኛል»
«አታኮርፈውም?»
«አይገባውማ!»
«አሁን ምን ይሻላል?»
«እኔ 'ንጃ፡፡ ይህን ከተማ ለቅቄ ልሂድ መሰለኝ
እየሳቅኩ «እስከዚያው ና ምን የመሰለ ቢራ ላጠጣህ» አልኩና
ባቡር ጣብያው አጠገብ አንዲት ስም የሌላት ካፌ አለች፣ እዚያ
ወሰድኩት። አንድ ቡና አይነት ቢራ አለ፣ ከስኮትላንድ የሚያስመጡት፡፡ ፀሀይ ላይ ቁጭ እንዳልን እሱን ቀመሰና
«ይህን እንዴት አገኘኸው ባክህን? እኔ ሁለተኛ ሌላ ቢራ
አልቀምስም» አለ። ንዴቱን መርሳት ጀምሯል፡፡ ራሱን እየነቀነቀ
«የተካ ዋና ፕሮብሌሙ ምን መሰለህ?» አለኝ «ጥሩ ልጅ ነው::
ከሰው ጋር ተስማምቶ መኖር ይፈልጋል። ግን በሄደበት ሰውን
እንዳበሸቀ ነው:: ወዶ አይደለም። ፍጥረቱ ነው»

«አውቃለሁ። ረስቼ አማንዳ ስትፈልግህ ነበር»
ዝም አለ። ገባኝ
"የፈረንጅ ሴቶች ሲሰለቹ!» አልኩት
«ያንተም ሰልችታሀለች?» አለኝ
«ፈረንጅ አይደለች?»
«አንተስ አትረባም» አለኝ
«ለምን?»
«ያችን የመሰለች ቆንጆ ምኗ ይሰለቻል? ድምፅዋ ብቻ
ይበቃል። በዛ ሰማያዊ አይኗ እያየችህ ያን ፈገግታ ስትሰጥህ
አንድ ፈገግታ እንደሱ ብታጠጣኝ ችዬ ከሷ አልለይም ነበር። በዚያ
ወፍራም ድምፅዋ ሉ ሃኒ ሉ' ብትለኝ ለዘለዓለም እታሰራለሁ»

«ፈገግታውንም ቁልምጫውንም ትሰጥሀለች ከፈለግክ»
«እንዲህም ብልህ'ኮ፣ ፈገግታውና ቁልምጫው ብቻ አይበቃም»
«አንተ ከፈለግክ ሌላውንም ትሰጥሃለች»
«እሱን ተወው! ካንተ ጋር ፍቅር እንደያዛት ያስታውቃል»
« ይመስልሀል» አልኩት
«ትወድሀለች ስልህ!»
«እሺ ይሁን፡፡ ግን አንዳንዴ ስላንተ ጣል የምታረገው ንግግር
አንተም ጠጋ ብትላት እንደማትሸሽህ ያሳያል»
«አዬ? ምን አለች?»
«አይ፣ እሱን አልነግርህም፡፡ ጠጋ ብትላት ራሷ ትነግርሀለች»
«እውነት እንድወስድልህ ትፈልጋለህ?» አለኝ
«አዎን፡፡ ግን ለሀበሾቹ እንዳትነግር»
«ግድ የለህም። እኔ ምልህ የኔን ሸክም ደሞ እንተ ትንሽ
ብትሸከምልኝ። አውቃለሁ አስቀያሚ ነች። ግን ጠጋ ስትላት የደስ ደስ አላት። ደሞ ከዛች ከቆንጆ ጋር ሰንብትህ ወደዚችኛዋ ስትመጣ
ጥሩ ለውጥ ሳይሆን አይቀርም። ሞክር እስቲ»
“አንተ ሞክር"
Shake on It! (ጨብጠኝ)» አለኝ፡፡ ተጨባበጥን
ትንሽ ቆይቶ፣ ራሱን እየነቀነቀ
«አባቶቻችን አሁን የተባባልነውን ቢሰሙ ምንኛ በናቁን!» አለ
እኔና ሉልሰገድ ሚስቶቻችንን እየያዝን አብረን ሲኒማ ገባን፣
አብረን ናይት ክለብ ሄድን። ለመለዋወጥ ሞከርን። አልቻልንም።
እነሱም ጓደኝነት ተያያዙ፡፡ እንደተሸነፍን ገባን

«ገና የፈረንጆቹን ያህል አልሰለጠንንም ባክህ» አለኝ

«እስከመቸም አንሰለጥንም» አልኩት

ሚስት መለዋወጥ ሲያቅተን ጊዜ ታሪክ ተለዋወጥን፡፡ የኔን
እንዴት እንዳገኘኋት ነገርኩት። እሱም ተራውን ነገረኝ። ታሪኩን
ሲጨርስ፣

“እንድ ቀን ምን ሆንኩ መሰለህ?» አለ «ከእራት በኋላ እቤቴ
እንድንገናኝ ተቃጠርን። የቀጠሮው ሰአት ሲደርስ ቤቴ መሄድ
በጣም አስጠላኝ፡፡ ሴት አጥተው ብቻቸውን የሚያድሩትን ጎረምሶች
በጣም ቀናሁባቸው። ቡና ጠጥተህ' ሲኒማ አምሽተህ ቤትህ
መመለስ፣ ፒጃማህን ለብሰህ ጥቅልል ብለህ ብቻህን መተኛት፤ ይሄ በጣም ትልቅ እድል መስሎ ታየኝ! ገደል ትግባ! አልኩና ሲኒማ
ገባሁ። የጀምስ ቦንድ ፊልም ነበር ያየሁት። ሰለላውን፣ ተኩሱን፣
ቦክሱን፣ ድፍረቱን ከምንም አልቆጠርኩለት። ትልቅ ጉብዝና ሆኖ የታየኝ ምን መሰለህ? ይሄ ጄምስ ቦንድ ያሰኘችውን ሴት ተኝቶ፣ ሲበቃው ዘወር ማለት ነው፤ አለቀ በቃ፡፡ እኔ ግን ከአንዲት ሴት
ዘወር ማለት አቅቶኝ እየቀጠርኳት ሲኒማ እገባለሁ፡፡ ራሴን እንዴት
ናቅኩት!

ስለጀምስ ቦንድ እያሰብኩ ወደ ሊቴ ሄድኩ። አኩርፋ
ኣንደምትቆየኝ ስላወቅኩ፣ የምነግራትን ውሸት እያሰላሰልኩ መኝታዬ ገባሁ:: መብራቱን አበራሁ። እንቅልፍ ተኝታለች። መስኮቱ ላይና ወንበሩ ላይ ሸሚዞቼ፣ ካናቴራዎቼ ሙታንታዎቼ፣ እግር ሹራቦቼ
ታጥበው ተሰጥተዋል። የተሰማኝን ልገልፅልህ አልችልም። እፍረት
ነው ይመስለኛል። ድቅቅ አልኩ፡፡ ተሸነፍኩ ልብሴን አውልቄ አልጋ ውስጥ ስገባ ነቃች። የት ቆየህ
አላለችኝም። ዝም ብላ አቀፈችኝ፡፡ አቤት እንዴት ነው ያሳዘነችኝ
ሳለቅስ ምንም ያህል አልቀረኝም

« በነጋታው ከሷ ጋር ዋልኩ፡፡
ስለሷ ማወቅ ፈለግኩ::
ጠያየቅኳት። ነገረችኝ። ያልደረሰባት ግፍ ያለ አይመስለኝም ማለቴ በወንድና በሴት መካከል የሚደረግ ግፍ፡፡ ባሜሪካን አገር የሚደረገው ነገር አንዳንዴ ከኛ አገር ይብሳል። ባስራ ሁለት ኣመቷ ሶስት ጎረምሶች በግድ ያዟትና ጭኗን ከፍተው ሻማ ጨመሩባት።ይህን ምን ትለዋለህ? እስቲ እንደ ሴት ቢበዷት ምን ቸገራቸው ነበር? ባስራ ሰባት አመቷ ደሞ የታላቅ እህቷ ባል በጉልበት ተኛት፡፡
ይህንንስ ስትነግረኝ አለቀሰች። 'ቆንጆንኳ ብሆን ደስ ብየው ነው፣
አላስችል ብሎት ነው ይባላል። ግን ቆንጆ አይደለሁም። ምኔም ደስ አይልም። እንግዲያው ለምን አዋረደኝ? ክፋትንና ጭቆናን የሚስብ አብሮኝ የተፈጠረ አንድ ነገር አለ መሰለኝ አለች

«እውነት ይህን ምን ትለዋለህ» አለ ሉልሰገድ አንድ ሰካራም
አጎት አላት፡፡ እሱ ደሞ አንድ ቀን በግድ ሊተኛት ሞከረ። ታግላ
አመለጠችው:: ግን መሞከሩ እጅግ ጎዳት፡፡ ምን ትለዋለህ ይህን
አይነት እድል? ከዚህ ሁሉ በኋላ ወንዶችን ጨርሳ መሸሽ ነበረባት።
አሷ ግን ተቃራኒ አደረገች፡፡ ለለመናት ሁሉ መስጠት ጀመረች።
እኔ ለዚህ ማስረጃ ላገኝለት አልችልም፡፡ ግን ምናልባት ለሁሉም መስጠት ያው ለማንም እንዳለመስጠት ይቆጠር እንደሆን?

ብቻ ምን ልበልህ? በጭራሽ አምላክ ያጠቃት ልጅ ናት።
ካወቀኝ ወንዶች ሁሉ አንተ ብቻ ነህ እሰካሁን እንደ ሰው የቆጠርከኝ አለችኝና እንደገና ኣለቀሰች፡፡ አልጋው ግርጌ ተንበረከከችና ጉልበቴን አቅፋ
"if you only knew what it means to me i will never be able to repay you never!” never እያለች እንባዋን አወረደችው።«ለኔ ምን ማለት እንደሆነ ባወቅክ! እስከመቸም ውለታህን ልከፍል አልችልም፣ እስከመቸም!»)
ራቁቷን ተንበርክካ ሳለ፣ ነጭ ገላዋ እንዴት ድቡልቡልና
አስቀያሚ እንደሆነ ታየኝ። በጣም አሳዘነችኝ፡፡ እንደዛ እዝኜ
አላውቅም፡፡ አብሪያት አለቀስኩ»
«ምነው አለቀስክ ? ትወደኛለህ እንዴ?' አለችኝ»
«ምንም ምርጫ አልነበረኝም
«አዎን እወድሻለሁ' አልኳት»
«'ምንም ወፍራም ብሆን?»
«'ምንም ወፍራም ብትሆኚ' »
ምንም ርካሽ ብሆን?»
«ምንም ርካሽ ብትሆኚ። ደሞ ርካሽ አይደለሽም፡፡ ተጠቃሽ
ተበደልሽ እንጂ አንቺ ያጠፋሽው ጥፋት የለም። You are a victim
(«ጥቃት የደረሰብሽ ነሽ»)
#ምንዱባን


#ክፍል_ሶስት


#ትርጉም_ከዬሐንስ_ገፃዲቅ


.....ከጥቂት ጊዜ በኋላ ከዚያ ቤት የነበረ ሰው ሁሉ እንቅልፍ ወሰደው::

እኩለ ሌሊት ላይ ዣን ቫልዣ ነቃ::

ዣን ቫልዣ ገጠሬ ሲሆን የተወለደው ብሬ በመባል ከታወቀ ደሃ ቤተሰብ ነው። በልጅነቱ ትምህርት ቤት ገብቶ የመማር እድል ባለማግኘቱ መሐይም ነው ከአደገ በኋላ ከተማ ውስጥ በአትክልተኝነት ሥራ ጀመረ

ዣን ቫልዣ በተፈጥሮው ለሰው አሳቢ እንጂ አዛኝ አልነበረም፡፡ ቤተሰቦቹ በልጅነቱ ነው የሞቱት:: እናቱ የሞቱት ታምመው ሲሆን አባቱ ከዛፍ ላይ ወድቀው ነው:: አባቱም እንደ እርሱ አትክልተኛ ስለነበሩ ዛፍ ለመከርከም
ከትልቅ ዛፍ ላይ ወጥተው ሳለ በድንገት ወድቀው ነው ሕይወታቸው ያለፈው:: ከቤተሰቡ መካከል በሕይወት የቀረች ከእርሱ ሌላ አንዲት እህት
ነበረችው:: የእህቱ ባል ሰባት ልጆች ጥሎባት ይጠፋል፡፡ ዣን ቫልዣን ያስጠጋችው እህቱ ስትሆን ባልዋ እስከጠፋ ድረስ ተንከባክባ ነበር ያሳደገችው::
ባልዬው ሲሞት የትልቁ ልጃቸው እድሜ ስምንት ዓመት ሲሆን የመጨረሻው ልጅ እድሜ አንድ ዐመት ነበር፡፡ ዣን ቫልዣ በዚያን ጊዜ 25 ዓመቱ ነበር::
እርሱ በተራው የልጆቹን አባት ተክቶ እህቱንና ልጆችዋን ይረዳ ጀመር::የወጣትነት ዘመኑን አዳጋችና አድካሚ ግን ብዙ ገቢ በማያስገኝ ሥራ ላይ ነበር ያሳለፈው:: በጊዜ ማጣትና ድኅነት ምክንያት በአፍላ ዘመኑ የከንፈር ወዳጅ እንኳን አልነበረውም:: እንዲያውም ከነአካቴው ለፍቅር ጊዜ
አልነበረውም ማለት ይቻላል፡፡

ማታ ማታ ከመሸ በኋላ ከቤቱ ተመልሶ ቃል ሳይናገር ያገኘውን
ይበላል፡፡ አንዳንድ ቀን ያቸን የምስኪን እራቱን ሲበላ እህቱ ከቀረበለት ምግብ ጥቂቱን እንደገና እየወሰደች ለልጆችዋ ትሰጥበታለች:: ይህ ሲሆን
በረጅም ፀጉሩ ፊቱን ሸፍኖ በዝምታ የተረፈችውን ይበላል:: ምንም ነገር እንዳልሆነ በመቁጠር ራሱን ለማታለል ይሞክራል:: ምርጫም አልነበረውም::

ዛፍ በሚገረዝበት ወራት በቀን እስከ 18 ሱስ ያገኛል:: ሥራ ሳይመርጥ ያገኘውን ይሠራል። እህቱም ትሠራለች:: ቢሆንም ራሳቸውን ያልቻለ ሰባት ልጆችን ማሳደግ ቀላል አልነበረም:: ገንዘቡ ስላልበቃቸው ቤተሰቡ
ችግር ቀስ በቀስ እያለ የሚያሳድደው አሳዛኝ ቤተሰብ ሆነ
የአንድ ዘመን ክረምት በጣም የከፋ ነበር፡፡ በዚህ ጊዜ ዣን ቫልዣ ሥራ አ፣ልነበረውም:: በዚህ የተነሣ ቤተሰቡ የሚላስ ወይም የሚቀመስ ነገር ያጣል:: አንድ ቀን እሑድ ማታ የአንድ ዳቦ መጋገሪያ ቤት ባለቤት ሊተኛ ሲል የዳቦ ቤቱ መስታወት ሲሰበር ይሰማል፡፡ የሰውዬው መኖሪያ ቅጥር
ግቢው ውስጥ ስለነበር በጊዜ በመድረሱ በተሰበረወ መስታወት በኩል አንድ ሰው እጁን አሾልኮ ዳቦ ሲሰርቅ ያየዋል:: ሌባው ዳቦውን ይዞ ሮጠ፡፡የዳቦ ቤቱ መስታወት የሰበረው በቡጢ ስለነበር እጁ ይደማል:: ስለዚህ
ዳቦው የተወሰደው በሌባ ለመሆነ ሌላ ማስረጃ አላስፈለገም:: ሌባ
ሰውዬ ዣን ቫልገ ነበር፡፡

ይህ የሆነው በ1795 ዓ.ም መጨረሻ ነው:: ዣን ቫልዣ የተዘጋ ቤት ጨለማን ተገን በማድረግ ሰብሮ ለመስረቅ በመሞከሩ «ወንጀለኛ ነው» ተብሎ ተፈረደበት:: ብያኔው ለአምስት ዓመታት በባርነት የመርከብ ቀዛፊ
ሆኖ እንዲሠራ ነበር፡፡

ዣን ቫልዣ አንገቱ በብረት ሰንሰለት ታስሮ ቱሉን ወደተባለ እስር
ቤት ተወሰደ:: ጉዞው ሃያ ሰባት ቀን ወሰደበት፡፡ የተጓዘው በእንስሳ በሚጎተት ጋሪ ነበር፡፡ ከተወሰነለት ሥፍራ እንደደረሰ ጥብቆ አለበሱት:: ያለፈው ታሪኩ ፤ ስሙ እንኳን ሳይቀር ተለወጠ፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ስሙ ዣን ቫልዣ ሳይሆን ቁጥር 24 ሺህ 601 ሆነ::

ከዚያ በኋላ እህቱ ምን ሆነች? ሰባት ልጆችዋስ ምን ደረሱ? ስለዚህ ጉዳይ ራሱን ያስጨነቀ አልነበረም:: ጥቂት የዛፍ ቅርንጫፎች ከትልቅ ዛፍ
ግንድ ሲቆረጥ ማነው ስለቅርንጫፎቹ የሚጨነቀው?
አራተኛ ዓመቱን ሲያገባድድ ዣን ቫልዣ ከእስር ቤት አምልጦ
ነፃነቱን የማግኘት እድል አጋጠመው:: ከእንደዚያ ባለ አስፈሪ ቦታ ያለ ሰዎች ዘወትር እንደሚተባበሩ ሁሉ የእርሱም የሥራ ጓደኞች ረድተውት
አመለጠ፡፡ ለሁለት ቀናት በየጥሻውና በእርሻ ቦታ እየተሽሎከሎከ ቆየ፡፡
በሁለተኛው ቀን ግን ወደማታ እንደገና ተያዘ፡፡ ለ36 ሰዓት ያህል እህል አልቀመሰም:: እንቅልፍም አልተኛም:: ለማምለጥ በመሞከሩ የእሥራት ዘመኑን በሦስት ዓመት ፍርድ ቤቱ አራዘመበት:: በጠቅላላው ስምንት ዓመት ሆነበት ማለት ነው:: በስድስተኛው ዓመት እንደገና ለማምለጥ
ሞክሮ ሳይሳካለት ቀረ:: ማታ ስም ሲጠራ 'አቤት' ሳይል በመቅረቱ
ጥሩምባ ተነፋ፡፡ ማታውኑ በአካባቢው የነበሩ ሰዎች ከመርከብ ስር ተሸሽጎ አገኙት፡፡ ዘበኛው ሊይዘው ሲል ተናነቀው፡፡ ወንጀሉ እጥፍ ሆነ፡፡ ለማምለጥ
በመሞከሩና ዘበኛ በመተናነቁ ለዚህ ጥፋቱ አምስት ዓመት ተፈረደበት::
አሥራ ሦስት ዓመት ሆነ፡፡ በአሥረኛው ዓመት እንደገና ለማምለጥ ሞክሮ አሁንም ሳይሳካለት ቀረ:: ለዚህም ሙከራው ሦስት ዓመት ተፈረደበት::አሥራ ስድስት ዓመት! በመጨረሻም በአሥራ ሦስተኛ ዓመቱ ይመስለኛል
እንደገና ለማምለጥ ሙከራ አድርጎ ከአራት ሰዓት በኋላ እንደገና ተያዘ፡፡
ለአራት ሰዓት ከእስር ቤት በመጥፋቱ አሁንም አራት ዐመት ተፈረደበት:: ሃያ ዓመት! ዳቦ በመሰረቁ ከእስር ቤት የገባው በ1796 ዓ.ም ሲሆን ከአሥራ
ዘጠኝ ዓመት እሥራት በኋላ ግን ለማምለጥ ቻለ፡፡

መርከብ ቀዛፊዎች ከሚታሰሩበት ሲገባ እየተንቀጠቀጠና እያለቀሰ
ነበር:: ያን ሥፍራ ሲለቅ ግን ልቡ ደንድኖ ነበር የወጣው:: ከዚያ ሲገባ ተስፋ ቆርጦ ነበር የገባው፧ ሲወጣ ግን ተስፋ ቢስ ብቻ ሳይሆን ጨካኝም ሆኖ ነው የወጣው::

ታዲያ የዚህ ነፍስ ሕይወት ምን ይሆን!

ታሪኩን ለማውሳት እንሞክር እስቲ፡፡ የሰውዬው ችግር በሕብረተሰቡ የተፈጠረ ስለሆነ ይኸው ሕብረተሰብ እነዚህን ነገሮች አጢኖ መመልከት
ይኖርበታል፡፡

ቀደም ሲል እንዳልነው ዣን ቫልዣ አላዋቂ ነው:: ግን ደደብ አይደለም:: በተፈጥሮው ጭምት ነው:: ሰንኳላው እድሉ ደግሞ በይበልጥ እንዲጨምትና
እንዲያስተውል ገፋፍቶታል፡፡ ሲገረፍ፤ በሰንሰለት ሲጠፈር፤ ጨለማ ቤት ሲታሰር ሰውነቱ በድካም ብዛት ዝሏል፡፡ የሌሊት ቁር ሲያቆራምደው፤ የቀን ፀሐይ ሲያወራጨው፤ እንዲሁም ከእንጨት ላይ ተኝቶ ዘወትር
ከአሳብ ውስጥ እየዋኘ ከኅሊናው ጋር ሲሟገት የኖረ ሰው ነው::

ራሱን እንደ ፍርድ ቤት ስለቆጠረ ምርመራውን በመጀመሪያ ከራሱ
ይጀምራል:: ያለ አግባብ የተቀጣ የዋህና ቀና ሰው አለመሆኑን ኅሊናው ያውቃል:: ሕገ ወጥ ተግባር መፈጸሙን አይክድም፡፡ ምናልባት ያንን አንድ ዳቦ ቢለምን ኖሮ አይነፈግም ነበር ይሆናል፡፡ አዛኝ ወይም አሠሪ እስኪያገኝ
ድረስ ደግሞ መታገስ ነበረበት፡፡ ለእነዚያ የትም በትኖአቸው ለቀረው ምስኪኖችም ይኸው ይበጅ ነበር፡፡ ስለዚህ የፈጸመው ተግባር የሞኝ ነው ለማለት ይቻላል፡፡ አንድ አርቆ ለማየት የማይችል ድሃ ዓለምን በጉልበት
አሸንፋለሁ ብሉ ቢጋፈጥ ወይም ችግሮችን በሌብነት እወጣለሁ ብሎ ቢታለል ስህተተኛነቱን ገሃድ ያወጣል፡፡
#ገረገራ


#ክፍል_ሶስት


#በታደለ_አያሌው


...“ሃያ ሳምንት!” አልሁኝ፣ ከአፋቸው ነጥቄ፡፡ ሳይታወቀኝ ደረቅ ቁጣ አንቆኛል፡፡ በእኔም ብሶ ደግሞ እንደ አሮጌ ቆርቆሮ ነው የጮህኩት። “ሃያ ሳምንት ከአራት ቀን!” አልኋቸው፣ የባሰ እየተንኳኳሁ። የባልቻ ያላ
ኃጢአቱ መጠርጠር ሁሉ ግድ አልሰጠኝም። ወንበሩን ወደ ኋላ
አሽቀነጠርሁና፣ እየተቆናጠርሁ ወደ በሩ ሄድሁኝ፡፡ በሩን በኃይል በርግጄ ከከፈትሁ በኋላ፣ ግው አድርጌ ዘግቼባቸው ወጣሁ። ምን እየሆንሁ እንደሆነ እንኳን እነሱ ለኔም አልታወቀኝም፡፡

መኪናዬ ዉስጥ ገብቼ እንዴት አድርጌ በየት በኩል እንደ ነዳሁት
አላስታውሰውም፡፡ እንዲሁ ብዥ እንዳለብኝ ወደ ራሴ ቤት የሚወስድ በመሰለኝ መንገድ የእውር ድንብሬን እያሽከረከርሁ ነበር፡፡ ገና ትንሽ እንደ ነዳሁ፣ ሁሉም ነገር ሰለቸኝ፡፡ ጠነባኝ፡፡
ይበልጥ ድቅድቅ ብሎ ጨለመብኝ፡፡ እንደ ምንም ዳር ይዤ አረፍ አልሁና ወደ ልቡናዬ
ለመመለስ ረዥም ጸሎት አደረስሁ፡፡ ሻል እንዳለኝ፣ የተሻለ ቦታ ተከሰተልኝ፡፡ የእናቴ ቤት!
የመኪናዬን መሪ በግራ በኩል ጠመዘዝሁት እና ወደ እመዋ ቤት
የሚወስደዉን መንገድ ተያያዝሁት። እግዚአብሔር ከክፉ አደጋ ጠብቆኝ በደህና ደረስሁ እንጂ፣ አኳኋኔ እንኳን አያድርስ ነበር። ወደ እመዋ ቤት ደርሼ ስገባ ግን ማንንም አላገኘሁም፡፡ ባዶዉ ቤት ሊዉጠኝ አፉን አ ብሎ
ከፍቶ ጠበቀኝ፡፡ ይኼ ሰፊ ቤት አሁንም አሁንም እንባዉን እስከማዉቅለት ድረስ አዛጋብኝ፡፡ እንደ ገና ደግሞ ሊያስገባኝ የቀፈፈውም መሰለኝ፡፡ እንደ
ምንም ወደ ዉስጥ ብዘልቅም፣ በዚህ ቀትር እንደ እኩለ ሌሊት ነው የጨላለመብኝ፡፡ እግሬን እየጎተትሁ ግራ ቀኝ ከተቅበዘበዝሁ በኋላ፤
ለሳሎኑ ወደሚቀርበዉ ክፍል ገብቼ አልጋዉ ላይ ወደቅሁበት።

ጥቅልል ብዬ መተኛት ነበር የሚሻለኝ፡፡ እንቅልፍ ግን ከየት አባቱ ይምጣልኝ? ነገሩ ሁሉ ተደበላልቆብኛል፡፡ እህል የሚባል ለመጨረሻ ጊዜ የቀመስሁት ትናንትና ማታ ነው:: ግን አሁንም አልራበኝም። ለነገሩ፣ እንደ ሥራዬ ቢሆንማ፣ እንኳንስ እመዋ ቤት ይቅርና እመዋ የረገጠችው
አፈር ላይ እንኳን የመተኛት ሞራሉ የለኝም፡፡ በዚያም ላይ ይኼ አልጋ
ጠዋት ከእመዋ ጋር በታዕካ ነገሥት ገዳም ቆይቼ ስወጣ መንገዴ ላይ ቆመዉ እህቱ አይደለችም ብለዉ የተወራረዱበት፣ የወንድሜ የጃሪም አልጋ ነዉ።

ሁሉንም ነገር ማፈር ጀምሬያለሁ።

የአባቴ ነፍስ እንዴት ትጠየፈኝ ይሆን? የየዋኋ እናቴ አምላክስ እንዴት ይጠላኝ ይሆን? እያልሁ ተበጠበጥሁ። ይኼ አልበቃ ብሎኝ፣ ከአንድ መቶ አርባ አራት ቀናት በፊት የተፈጠረው ነገር ሁሉ በዓይነ ኅሊናዬ እየተመላለሰ ዕረፍት የሚባል ነገር ከለከለኝ፡፡ ላለማስታወስ ከራሴ ጋር
ብዙ ብቦቃቀስም፣ አለማስታወስ ግን አልቻልሁም፡፡ ዕለቷ ከነቅጽበቷ ሳትቀር መጥታ የሚከብድ ጥላዋን ጥላብኝ ዓይነ ልቡናዬ ላይ ቁጭ አለችብኝ፡፡

ትዝ አለኝ።

ዕለቷ እሁድ ነበረች። በዚያች ዕለት፣ አመሻሽ ላይ እንደ ልማዴ ክራሬን ይዤ ወደ አንድ ምዕራባዊ የአዲስ አበባ ዳገታማ ሥፍራ ላይ ወጥቻለሁ። ልክ እንደ ሁልጊዜው፣ ከሚወዱኝ የቀረ ሰው አልነበረም። ጠይም ወይ ቀይ፣ ያገባ ወይ ያላገባ፣ ወንድ ወይ ሴት፣ የወለደ ወይ ያልወለደ፣ አማኝ
ወይ ከሃዲ ሳይቀር ግልብጥ ብሎ ከቦኛል። አንዳንዱ መልኬ ጠርቶት፣ አንዳንዱ ድምፄ ናፍቆት፣ አንዳንዱ ደግሞ ሌላ ሰው ተከትሎ መጥቷል። አለባበሴም ፀሐያማ ነበር።

አስታዉሳለሁ።

ዉቧ ጀንበር ሄድሁ ሄድሁ ብላለች፡፡

ሲጀመር ለፀሐይ ምንም አይወጣላት። ለኔ ደግሞ ምንም ሲሆን፣ ከዚህ ሰዓት ሌላ ዉበቷ ደምቆ አይታየኝም። በአድማሱ ላይ እግሮቿን ከፋፍታ፣ ደልቀቅ ብላ የምትታየኝ ሲመሻሽ ብቻ ነው፡፡ ነፃነቷስ! ራሷን ወደ ታች
በምድር ላይ፣ እግሯን ደግሞ ወደ ላይ በሰማዩ ትሰቅለዋለች። መዘቅዘቋን ተከትሎ፣ ስስ ፀሐያማ ቀሚሷ ገለብ ቢልም፣ ሐፍረተ እንትኗን ግን አናይባትም፡፡ የእኔን ጉጉት እያየች ነዉ መሰለኝ፣ ፈገግ ትልብኛለች።ፈገግታዋ ደግሞ በማንም ቆዳ ላይ አይደርስም፡፡ ይኼ ራሷ ለራሷ የሰጠችው የፍስሐ ጊዜዋ ይመስለኛል። ባትሞት ትታመም፣ ሥጋ
የሚባል ግን አይኖራት ይሆን?
በዚሁ ዕለትም ከጀንበሯ ፈገግታ ፊት ለፊት ሆኜ የግራ እጆቼን ጣቶች በክራሬ አዉታሮች ላይ ዘርግቻለሁ። ከዚያም ምዕራብ ምዕራቡን እያየሁ፣
ለስለስ አድርጌ መግረፍ ጀመርሁ።

ደገኛዉ መጽሐፍ
ባሪያዎችህም ጭምር፣
ኢትዮጵያን ይሏታል
ጌታ ያንተ ሀገር።
እንግዲያዉ ጌታዬ፤
አልሟገትህም
ሀገሬን ወደ ጫፍ ሲገፉት ብትል ዝም፣
ባገርህ ነኝና ካንተ አይብስብኝም።

ድምፄን ጨመር አድርጌ እንደ ገና አንጎራጎርሁ።

ጌታ በናትህ መልሰው፣
እረ ጌታ በማርያም መልሰው
የጀግናዬ ን ልብ እንደ ሰው።

ይኼንን ብዬ፣ ያለ ልማዴ እንደ አጋጣሚ ቀና ብል፣ ከመካከላቸው አንድ ወጣት ሹልክ ብሎ ሲሄድ አየሁት። የከበበኝን ሰዉ ሁሉ ከምንም ሳልቆጥር በረቃቅሼዉ ብድግ ብዬ ተከተልሁት። ይኼን ልጅ ነው ለመጀመሪያም ለመጨረሻም ጊዜ
ነፍስ የተያየሁት፡፡ ይኼን ልጅ
እስከማውቀው ድረስ ዕለት በዕለት የምቆጨው መነኩሴ ባለመሆኔ ነበር።በተለይም ልጅ እያለሁ ካህኑን አባቴን ተከትዬ ለመሳለም ወደ ገዳም በምሄድ ጊዜ፣ ለደስታዬ ወደር አልነበረውም፡፡ ከዛሬ ነገ ገዳም ገብቼ በአመክሮ እጀምራለሁ እያልሁ ቀን እቆጥራለሁ። አባቴ እና እናቴ እንኳን ከእኔ የሕይወት መስመር በቀር የሚያከራክራቸው ጉዳይ መኖሩን አላዉቅም። አባቴ ሁልጊዜም ቢሆን ዉብርስቴ መንኩሳ እስከ እመምኔትነት ደርሳ ሳታሳየኝ አልሙት» የሚል ነበር ጸሎቱ ሁሉ። እናቴ ደግሞ በተቃራኒዉ ልጄ ማለፊያ ትዳር ገብታ ዓይኗን በዓይኗ ሳታሳየኝ
አትግደለኝ ባይ ናት። እንዲያዉ ድከሙ ቢላቸዉ ነዉ እንጂ፣ እመዋ ሆኖላት አባቴን እንዴትም ብላ ብታሳምነዉ እንኳን፣ የእኔ ዝንባሌ ግን የአባቴ ምርጫ ነበር። እማሆይነት። ቢሆንልኝ ብዬ የምመኘዉን የምንኩስና ስም ሁሉ ለራሴ አዉጥቼ አዉቃለሁ። አብዝቼ የተለማመድሁት ሕይወትም ምንኩስናን ነዉ። እጅግ በጣም የምቀናባቸው ሰዎች፣ በአርምሞ ዉስጥ ያሉ መነኮሳት ብቻ ናቸዉ።
በሕልሜም በዉኔም የሚታየኝ ብቸኛ ቦታ በጽዶች እና በዝግባዎች የተከበበ ጸጥ ያለ ገዳም ነበር።

ይኼን ልጅ ካወቅሁት በኋላ፣ ሕልሜን በሌላ ሕልም አስለወጠኝ። እሸቴ
ይባላል።

እሸቴ!

ቆዳው ሞኛሞኝ፣ አእምሮው ግን እሳታማ የሆነለት ልጅ ነው። ወይ
ጭንቅላት! አወይ መታደል! ባልወደው ነበር የሚደንቀኝ። አነጋገሩ የጅል፣ ንግግሩ ግን የንጉሥ የሆነለት ልጅ ነዉ። እንኳን እሱ እናቱም ጭምር ለልብ የሚደርሱ የሙቀት ወንዛወንዝ ናቸው።

ጭልጥ አልሁለታ!

በዚሁ በሲራክ-፯ ጀማሪ አባል ሳለሁ፣ የመጀመሪያ ተልእኮ የተሰጠኝ የእሸቴ ጉዳይ ነበር፡፡ ከዚያ ቀደም ስሙን እና ዝናውን በሩቁ ከመስማት በቀር ትውውቁ አልነበረንም። ለመጀመሪያ ጊዜ በአካል ያየሁትም ያኔ የእሱን ጉዳይ ተልእኮዬ አድርጌ የተቀበልሁ ጊዜ ነው። በዚያን ጊዜ እሱ የአዲስ አበባ ኑሮ በአፍንጫዬ ይውጣ ብሎ፤ የት ይደርስበታል
የሚባልበትን የዩኒቨርስቲ ትምህርቱን እርግፍ አድርጎ ጥሎት አልዩ አምባ ወደምትባል ጥንታዊት ትንሽ ከተማ ከሸክላ ሠሪ እናቱ ጋር መኖር ጀምሯል፡፡ ሲራክ-፯ ደግሞ የእሸቴን የአእምሮ ያውቀዋልና፤ ይኼን የመሰለ ልጅ ባክኖ ከሚቀር ልጠቀምበት ብሎ ወሰነ።
የእኔ ተልእኮም እሱን ለሲራክ፯ አባልነት መመልመል እና ማብቃት
ነበር።
#ገረገራ


#ክፍል_ሶስት


#በታደለ_አያሌው


..እውነትም ገራሚ ልጅ አይደለም? ገና ስሙን ነግሮኝ እየተዋወቀኝ ለመስለው ለእኔ ያለ ሐፍረት እንዲህ ከመሀሉ ጀምሮ መናዘዙ አይገርምም? ቅሌቴ የሚለዉን ነገር የመናገሪያ አመጣዉ? እንዴት ሆነለት? በጣም ደነቀኝ፡፡ እኔ እሱን ብሆንስ?አይደለም ለሌላ ሰው ልነግረው ይቅርና፣ ራሴንም እንደማልክደው እርግጠኛ አይደለሁም። እሸቴ የተለየ ሰዉ መሆኑን አመንሁ። ገራገር ነው። በዚያም ላይ በግልጽነቱ ላይ ወሰን አጣሁበት። ይኼን ሰው
ከማድነቅ በቀር አማራጭ የለኝም።

“ስለ ለምንድን ነው ግን የነገርሁሽ?” አለ፣ እንደ ማፈርም እንደ መሳቅም ብሎ።

“እንጃ” አልሁት፣ ባይነግረኝ እንደማለቅስ እያወቅሁት። በእኔ ቤት ለእሱ ግድ የሌለኝ መምሰሌ ነዉ። ዉሸት! ለምን ሆነና ስንትና ስንት ኪሎ ሜትሮች አቆራርጬ፣ እዚህ አልዩ አምባ የመጣሁት? ለእሱ ብዬ እኮ ነዉ። የገዛ ታሪኩን ከራሱ አፍ ለመስማት፡፡ ደካማ ጎኑን ለማወቅና የሲራክ ፯ አባል ለማድረግ ነዉ እዚህ ድረስ መምጫ ምክንያቴ፡፡ ቢሆንም
ግን እንደማዉቀዉ ሊያዉቅብኝ አይገባም፡፡ ስለዚህ የባሰ ፊት ነሳሁት።

“ቅቅቅቅቅቅ ቅሌታም ነኝ አይደል?”

“ነህ እንዴ?”

“ይኼን ያወቁ የግቢ ልጆች ምን ብለው ቅጽል ስም እንዳወጡልኝ
ታዉቂያለሽ?”

“ግቢ...?” አልሁት፣ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የኮምፒዉተር ሳይንስ
ተማሪ እንደነበር ጠንቅቄ የማላውቅ ይመስል። እንኳንስ ይቺን፣ ስለሚያዘወትረዉ የካልሲ ቀለም ሳይቀር ተነግሮኛል። ግቢ ነበርህ እንዴ?” አልሁት አሁንም፣ ስለሱ ምንም እንደማላዉቅ መስየ።

“አዎ”

“እሺ፣ ምን አሉህ?”

“ዎዎዎዎ ዎከር”

“ዎከር?”

«ሂያጅ ማለታቸዉ እንደሆነ። ያያያያ ያው የቀላዋጭ መጠሪያው
እንደዚያ አይደል? እኔ ከዚያ በፊት ለማንም ሐሜት ደንታ የለኝም ባይ
ነበርሁ። ይኸኔ ግን ተሰማኝ። አመመኝ። በጣም አፈርሁ። ራሴን መናቅ ሁሉ ጀመርሁ። ተማሪ አስጠላኝ። አስተማሪ አስጠላኝ። ዩኒቨርስቲ አስጠላኝ። መማር ጠላሁ። በበበ በቃ ሁሉ ነገር ጉሮሮዬ ላይ መጣ።
የጀመርሁትን በጅምር ትቸው ወጣሁ። ከዚያ ሁሉም ነገር በአፍንጫዬ ይውጣ ብዬ ወደ እናቴ መጣሁ እልሻለሁ” አለና፣ ኧሁሁ ብሎ በረዥሙ ሲተነፍስ፣ ወዠቦ ያለፈ ነበር የመሰለኝ። ቅዝዝ ብዬ አየሁት፡፡ አዘንሁለት። ሰነባብቼ እንዲያዉም ሲራክ፤ ከሰጠኝ ተልእኮዬ ጎን ለጎን
ለእሱ ማዘኑንም ለራሴ እየደረብሁበት መጣሁ፡፡ ይባስ ብዬ ራሴን ሳታልለው ደግሞ «እሸቴ እኮ የእኔ እርዳታ ያስፈልገዋል ማለት ጀመርሁ። አዝኜ ሞትኋ! እኔ ማነኝና ለእሽቴ አዝናለሁ? ዉሽት።
የምንኩስና ምኞቴን የሚያስረሳ ቦታ በልቤ ዉስጥ ጠርጌ ማስረከቤን ላለማመን የፈጠርኋት መሸንገያዬ ናት። መከጀሌን ከውርደት ብቆጥረው
እንጂ አሸንፎኛል። በቃ ገዳም የሚለዉ የልጅነት ምኞቴ ቀረና ትዳር ያሰኘኝ ጀመር። መነኩሴነት ቀረ እና ሚስትነት በዓይን በዓይኔ ዞረ። በእርግጥ እሱ ብቻ ሳይሆን እኔም አሸንፌዋለሁ። ማኅበሩን ጨምሮ ጠላሁት ያለውን ነገር ሁሉ አስወድጀዋለሁ። ልክ እንደ ተላክሁት ሄጄ አምጥቼዋለሁ። ማምጣት ብቻ ሳይሆን የሲራክ-፯ አባል ማድረግ ችያለሁ። ያዉም ተራ ሳይሆን፣ እንደ ዓይን የሚቆጠር መኩሪያ አባል።

ተልእኮዬን በፍጽምና ተወጥቼዋለሁ።

ከዚያ በኋላ አፍ አዉጥተን ፍቅረኛሞች ነን ባንባባልም፣ ያዉ ሆነናል። በበኩሌ ልቤን ሰጥቼዋለሁ፡፡ ስለ እሱ ሞኝነት እና ጉብዝና መስማቱ ሱስ ሆኖብኛል፡፡ እሱም ቢሆን አይቶኝ እና እንጉርጉሮዬን ሰምቶ አይጠግብም፡፡ነገር ግን ገና ማንም ያወቀብን አይመስለኝም፡፡ ምናልባት፣ ባልቻ እና
የእሽቴ እናት ጥርጣሬው ይኖራቸው ይሆናል እንዳይታወቅብን የተለየ ጥንቃቄ አድርገን ሳይሆን እኔ ክራሬን ይዤ
ወደ አደባባይ ስወጣ ብዙ ወጣት ግልብጥ ብሎ እንደሚያጅበኝ የታወቀ በመሆኑ ይመስለኛል
በሲራክ ፯ ማዕከልም ቢሆን ከብዙዎች ጋር ጥሩ ቀረቤታ ስላለን፣ የእሽቱን የተለየ አያስመስለውም። ወይ
እኔን በእንዲህ ያለ ነገር
የሚጠረጥረኝ አይኖር ይሆናል፡፡ በተለይ ቤተሰቦቼ ሴትና ወንድ እንኳ ለይቼ ማወቅ የሚሆንልኝ አይመስላቸዉም፡፡ እንዲያውም አንደኛዋ እህቴን ልነግራት ስሞክር፤ አንቺ እንኳን እንደ እሸቴ ላለ ዘሟች ይቅርና ለጳጳስ ልጅም አትደነግጭት ብላኛለች፡፡ ጳጳስ ልጅ እንደማይወልድ ጠፍቷት ሳይሆን ምን ያህል እኔን በእንዲህ ዓይነት መንገድ
እንደማትገምተኝ ስታሳምነኝ ነው።

አላወቀችኝማ፣ ለእሽቴ ስል የማይተወዉን ሕልሜን እንደ ተዉሁት።

“እኔ ምልህ እሸቴ” አልሁት፣ በዚያች ጎደሎ ምሽት በእኔ ቤት እራት በልተን ከመጨረሳችን። ቀደም ብሎ፣ አመሻሹ ላይ ከጀንበሯ ፊት ክራር ይዤ ሳለሁ፣ እኔን ከብቦ እንጉርጉሮዬን በስስት የሚያዳምጠኝን ሰዉ
ሁሉ ከምንም ሳልቆጥር ረግጬ፤ እሱን ተከትዬዉ ቀጥታ ወደኔ ቤት
ነበር እራት እንብላ ብዬ የወሰድሁት።

“ትናንት” አልሁት፣ ለመጀመሪያ ጊዜ ወይን ለመቅመስ እጄን ወደ
ብርጭቆዉ እየሰደድሁ። አልኮል የሚባል ነገር በአፌ ዞሮ ስለማያውቅ፣ ምን ምን እንደሚል መቅመሱ ሳያጓጓኝ አልቀረም።

“ትትትትት-ትናንት ምን?”

አንድ ነገር ብጠይቅህ ሳትደብቅ ትነግረኛለህ እ?”

“ካካካ ካንቺ መደበቁ ሆኖልኝ እኔ?”

“አዉቃለሁ፣ አትደብቀኝም”

“ስስስ-ስለኔ ላንቺ ምንድነዉ ያልነገርሁሽ ዉቤዋ?”

“ትናንትና በዚህ ሰዓት የት ነበርህ?” አልሁት ዓይን ዓይኑን እያየሁ፣ ቁርጥ አድርጌ፡፡

“ትትትት ትናንትና?” አለ፣ ደም እንደሚጎነጭ ዝግንን ብሎት የወይኑን ብርጭቆ ወደ አፉ እያስጠጋ።

“የት ነበርህ?”

እንደ ትኩስ ቡና በፍራቻ ፉት ያለዉን ወይን በአፉ እንደ ያዘዉ ለረዥም ጊዜ ጣሪያ ጣሪያዉን አየ። እኔም ልቤ ለምላሹ እንደ ተንጠለጠለች፣ በዝምታ ጠበቅሁት። የጠረጠርሁት ነገር አለ። መቼም ዐመል በዋዛ
አይለቅምና፣ ምናልባት ወደ ሴተኛ አዳሪዎች መሄዱን የተወዉ
አልመስልሽ ስላለኝ ነዉ አጠያየቄ፡፡ ቢሆንም፣ ከእሱ ጋር ያለዉን እዉነት መስማት አለብኝ፡፡ እኔን እንደማይዋሸኝ ደግሞ አዉቃለሁ። እንኳንስ እንዲህ እየተቁለጨለጭሁ ጠይቄው ይቅርና፣ ድሮዉንም ግልጽነቱን
ማንም እንደ እሱ አልታደለዉ። የት ነበርሁ ይለኝ ይሆን?

“እእእ አልሆነልኝማ” ብሎኝ አረፈዉ፣ እንባ በዓይኑ ጢም እያለበት፡፡
እንደ ፈራሁት!

“ምን ማለት ነዉ አልሆነልኝም ማለት?”

“በቃ ሄጄ ነበር። እሱን አይደል የምትጠይቂኝ? ትናንትና በዚህ ሠዐት ፒያሳ ዶሮ ማነቂያ ነበርሁ”

“እኮ ምን ልትሆን!?”

“አአአ አልቻልሁም። ምን ጎትቶ እንደሚወስደኝም አላውቀው። ምኑ ሽዉ እንደሚያደርገኝ ሁሉ እንጃለቴን። ግን ትናንትም ሴተኛ አዳሪዎች ጋ ሄጄ ነበር። አቅቶኛል እኔ”

እየየ ብለን ተላቀስን። እንባዬ እየወረደም ንዴት ተናንቆኛል። እየቆየማ ጥርሴ ሁሉ ተፋጨብኝ። ይኸኔ በንክሻ ብዘለዝለዉ ሁሉ የልቤ አይደርስም። ለንዴቴ ማብረጃ አጣሁለት።

“ደግሞ አታፍርም? ጀብዱ እንደ ፈጸመ ሰዉ ጉድህን ስትናገር ሐፍረት የሚባል የለህም!?”

“ብዋሽሽ የባሰ አታዝኝብኝም ነበር?”

“ዋሽተህ መሞከር ነበራ! ሁልጊዜ አንድ ዓይነት መልስ አያሳፍርህም? ሁልጊዜ ‹አቃተኝ ስትለኝ አታፍርም!? ጨክነዉ ከተዉት እንኳን ዝሙት
ሌላዉስ ይቀር የለም እንዴ!?
ሁልጊዜ አንጀቴን የምትበላው
ይመስልሃል? ቆይ ጅል ነዉ እንዴ የምመስልህ!?”

ሌላ መልስ አጣ። ደግሞ ምናባቱንስ ይመልስልኛል?

“ልንገርህ አይደል? አንተ መቼም አያልፍልህም! መቼም አትለወጥም!”

“አሳፈርሁሽ አይደል?”

“ነገርሁህ። ተንፏቀህ ተልከስክሰህ ትቀራታለህ እንጂ፣ መቼም
አትለወጥም!”
#የጣሪያ_ስር_አበቦች


#ክፍል_ሶስት


#ትርጉም_ሀኒም_ኤልያስ


....እኔ እንደተሰማኝ ሊሰማቸው የማይገባ ስለሆነ መንትዮቹ እንዴት እንደሆኑ ለማወቅ ዞሬ ተመለከትኩ።አንድ መልካም ሰው ወደ ወጥ ቤት ወስዷቸው
ከመተኛታቸው በፊት ቀለል ያለ ምግብ እያዘጋጀላቸው ነበር። አይኔ ከክሪስቶፈር አይን ጋር ተጋጨ ልክ እንደኔ በዚህ ቅዠት ውስጥ እንደተያዘ ያስታውቃል። ፊቱ የገረጣና የደነገጠ ይመስላል። አይኖቹ ሀዘን አጥልቶባቸው ጠቁረዋል።

አንደኛው ፖሊስ ወደ መኪናው ተመልሶ የታሰሩ ነገሮች ይዞ መጣና በጥንቃቄ ጠረጴዛ ላይ ዘረገፋቸው አባቴ ኪሱ ውስጥ የሚያስቀምጣቸው ነገሮች
ነበሩ እናታችን ለገና በስጦታ የሰጠችው የኪስ ቦርሳ፣ የማስታወሻ ደብተሩ፣ የእጁን ሰዓትና የጋብቻ ቀለበቱን ስመለከት በቆምኩበት ደረቅኩ። ሁሉም ነገር ጠቁሯል። በጭስና በእሳት አርሯል።

በመጨረሻ የመጡት የመኪናው የእቃ ማስቀመጫ ሲመታ ከሻንጣው ውስጥ የተበተኑት የአባቴ ልብሶችና ለኮሪና ኬሪ የተገዙላቸው ባለቀለም አሻንጉሊቶች ነበሩ። ባለ ቀይ ፊቱ ፖሊስ ሲናገር ሁሉም የተገኙት መንገዱ ላይ ተበትነው ነበር።

እነዚያን ልብሶች አውቃቸዋለሁ: እነዚያን ሸሚዞች፣ ከረባቶችና ካልሲዎች...ሁሉንም አውቃቸዋለሁ ከልብሶቹ መሀል ላለፈው ልደቱ ሰጥቼው የነበረው ከረባት ነበረበት።

“አስከሬኑ የእሱ መሆኑን የሚለይልን አንድ ሰው እንፈልጋለን፡” አለ ፖሊሱ።

አሁን በእርግጠኝነት አወቅኩ እውነት ነው: አባታችን… በራሱ የልደት ቀን እንኳን ሳይቀር ስጦታ ይዞልን የሚመጣው አባታችን ሞቷል!!

ከዚያ ክፍል ሮጬ ወጣሁ! ልቤን ከሚያደሙትና እስከዛሬ ከተሰሙኝ ህመሞች ሁሉ በከፋ ሁኔታ ካሳመሙኝ ከተዘረገፉት ዕቃዎች ሸሽቼ ሮጥኩ። ከቤት
ወጥቼ ከጀርባ ያለው የአትክልት ቦታ ሄድኩና አሮጌውን የማፕል ዛፍ በጡጫ ቀጠቀጥኩት እስኪያመኝና እጄ ደም በደም እስኪሆን ድረስ ቀጠቀጥኩት።
ከዚያ ሳሩ ላይ ዘጭ ብዬ ወድቄ አምርሬ አነባሁ በህይወት መቆየት ይገባው ስለነበረው አባቴ አለቀስኩ። ያለ እርሱ ህይወታችንን ለምንገፋው ለእኛ አነባሁ እናም ምን ያህል መልካም አባት እንደሆነና እንደነበረ የማወቅ
እድል ላላገኙት መንታ እህትና ወንድሜ አለቀስኩ። እምባዬ አልቆ አይኖቼ አብጠው ደም መስለው እየቆጠቆጡኝ ባለሁበት ቅፅበት የእግር ኮቴ ወደኔ ሲመጣ ሰማሁ። እናቴ ነበረች:

ሳሩ ላይ አጠገቤ ተቀመጠችና እጄን በእጆቿ ያዘች ሰማዩ ላይ ግማሽ ጨረቃ በሚሊየን በሚቆጠሩ ከዋክብት ታጅባ ወጥታለች አዲስ ከተወለደው ከፀደዩ ሽታ ጋር ንፋሱ ደስ የሚል ነበር። በመካከላችን የነበረው ዝምታ ማብቂያ የሌለው በሚመስል ሁኔታ ለረጅም ደቂቃዎች ቀጠለ፡ በመጨረሻ እናቴ “ካቲ አባትሽ ከላይ ከሰማይ ሆኖ እያየሽ ነው፡ ጎበዝ እንድትሆኚ እንደሚፈልግ
ታውቂያለሽ አይደል?” አለችኝ።

“አልሞተም እማዬ!” ላለማመን ፈለግኩ።

“እዚህ ቦታ ብዙ ቆይተሻል። ምናልባት አላስተዋልሽ ይሆናል እንጂ አራት ሰዓት ሆኗል። አንድ ሰው የአባትሽን አስከሬን መለየት ነበረበት ለዚህ ደግሞ
ጂም ጆንስተን እንደሚሄድ ነገሮኝ ነበር። እኔ ግን ራሴ ማየት ስፈለግኩ ሄጄ አየሁት። አየሽ እኔም ለማመን ከብዶኝ ነበር አባትሽ ሞቷል ካቲ። ክሪስቶፈር አልጋው ላይ ሆኖ እያለቀሰ ነው፡ መንትዮቹ ተኝተዋል። መሞት
ምን እንደሆነ ገና በደንብ አልገባቸውም:”

አቅፋኝ ጭንቅላቴን ትከሻዋ ላይ አሳረፈችው።

ከዚያ ተነሳችና ከእሷ ጋር እንድነሳ ክንዷን ወገቤ ላይ አድርጋ እየጎተተችኝ “ነይ… እንደዚህ አዝነሽ ብቻሽን መሆንሽ ጥሩ አይደለም: ሀዘንሽን ውስጥሽ
ከምትቀብሪው ይልቅ ሀዘንሽን ከሚጋሩሽ ሰዎች ጋር መሆን የተሻለ ነው:"

ይህንን ስትነግረኝ አንዲት ዘለላ እምባ እንኳን አይኖቿ ላይ አልነበረም ነገር ግን በውስጧ እያለቀሰችና እየጮኸች እንደሆነ ከድምጽዋና አይኖቿ ላይ
ከሚታየው ጥልቅ ሀዘን መናገር ይቻላል።

ከአባታችን ሞት ጋር ተያይዞ ቀኖቻችንን ቅዠት ያጠላባቸው ጀመር᎓ እናቴን ያለማቋረጥ አተኩሬ እያየኋት ለእንደዚህ አይነት ነገር አስቀድማ ልታዘጋጀን
ይገባ እንደነበር አሰብኩ የሆነ ነገር በሞት ማጣት ምን እንደሚመስል
እንድናውቅ የራሳችን የሆነ ውሻ ወይም ድመት እንዲኖረን ፈቅዳልን
አታውቅም ያንን ብታደርግ ኖሮ ድንገት ሲሞቱብን ሞት ምን ማለት
እንደሆነ በጥቂቱም ቢሆን ማወቅ እንችል የነበረ ይመስለኛል የሆነ ሰው፣ትልቅ ስው፣ መልከ መልካሞችም፣ ወጣቶችም፣ በጣም አስፈላጊ ሰዎችም
ሊሞቱ እንደሚችሉ ሊያስጠነቅቀን ይገባ ነበር።

ዕጣ ፋንታ በሆነ ቀዳዳ ውስጥ እየጎተታት ቀጭንና ስስ ላደረጋት እናት እንዴት እንደዚህ አይነት ነገር ሊባል ይችላል? መናገር ወይም መብላት ወይም ፀጉሯን ማበጠር ወይም ሳጥኗን የሞሉትን የሚያማምሩ ልብሶች መልበስ ለማትፈልግ ሴት እንዴት እንዲህ አይነት ነገር በግልፅ መናገር
ይቻላል? ሌላው ቀርቶ እኛ የሚያስፈልገንን ነገር እንኳ ማየት አትችልም ነበር። ደጋግ የጎረቤቶቻችን ሴቶች መጥተው የሚወስዱን መሆናቸው
ቤታቸው ያዘጋጁትን ምግብ የሚያመጡልን መሆኑ መልካም ሆኖልን ነበር ቤታችንም በአበቦችና ጎረቤቶች ሰርተው በሚያመጡት ምግብ የተሞላ ነበር።

አባታችንን የሚወዱት፣ የሚያደንቁትና የሚያከብሩት ብዙ ሰዎች ሁለ ይመጡ ስለነበር አባታችን ይህን ያህል ታዋቂ በመሆኑ ተገረምኩ። ሆኖም
የሆነ ሰው እንዴት እንደሞተ ጠይቆ ስንት ጥቅም የሌለው መሞት ያለበት ለማህበረሰቡ ሸክም የሆነ ሰው እያለ እንደሱ አይነት ወጣት መሞቱ አሳዛኝ
ነገር እንደሆነ በተናገረ ቁጥር ሞቱ ይበልጥ ያሳምመኝ ነበር።

ከሰማኋቸው ነገሮች የተነሳ ዕጣ ፋንታ የሚባለው ነገር ክፉና ለሚወደድና ለሚፈለግ ሰው እንኳን ክብር የሌለው አሰቃቂ ነገር እንደሆነ አወቅኩ።

የፀደይ ቀናት እያለፉ ወደ በጋ ተጠጋ። ምንም ያህል ለቅሶውን ለማስተናገድ ቢሞhርም ሀዘን እየደበዘዘ የሚመጣበት የራሱ መንገድ አለው። እናም
በህይወት ውስጥ በጣም ተወዳጅ የነበረ ሰው ሳይቀር የደበዘዘና ከትኩረታችን ወጣ ያለ ጥላ እየሆነ ይመጣል።

አንድ ቀን እናታችን ፈገግ ማለት እንዴት እንደሆነ የረሳች በሚመስል ሁኔታ ፊቷ ተከፍቶ ተቀምጣ ነበር ሀዘኗን ላስረሳት በመጣር “እማዬ… አባታችን
በህይወት እንዳለ ቁጠሪውና ለሌላ የስራ ጉዞ እንደሄደና እንደሚመለስ፣ ከዚያ "
በበሩ ገብቶ ልክ ድሮ እንደሚያደርገው ተጣርቶ “የሚወደኝ መጥቶ ይሳመኝ
ሲል አይታይሽም? እማዬ ለሁላችንም እንደዚህ ብናስብ ይሻለናል ሁላችንም የሆነ እኛ የማናየው ቦታ እየኖረ እንደሆነና ድንገት እንደሚመጣ መጠበቅ እንችላለን" አልኳት።

“አይሆንም ካቲ፣ እውነቱን መቀበል አለብሽ፡ በማስመሰል ውስጥ መደበቂያ መፈለግ የለብሽም ሰምተሸኛል? አባትሽ ሞቷል። ነፍሱ ወደ መንግስተሰማይ ሄዳለች እናም በአንቺ እድሜ ማንም ሰው ከሰማይ ተመልሶ እንደማይመጣ
መረዳት አለብሽ፡ እኛ ካለእሱ የምንችለውን እናደርጋለን፡ ያ ማለት ግን እውነታን ባለመጋፈጥ ማምለጥ ማለት አይደለም” አለችኝ በቁጣ።

ከዚያ ከተቀመጠችበት ወንበር ላይ ተነስታ ቁርስ ለመስራት ከማቀዝቀዣው ውስጥ የሆኑ ነገሮች ስታወጣ አየኋት።
እንደገና እንዳትቆጣኝ እየተጠነቀቅኩ “እማዬ ካለሱ የምትችይ ይመስልሻል?
አልኳት።

“በህይወት እንድንቆይ የቻልኩትን ሁሉ አደርጋለሁ” አለች ስሜት በማይሰጥ ድምፅ።

“አሁን እንደ ወይዘሮ ጆንስተን ስራ መሄድ አለብሽ ማለት ነው?”
#ጠላፊዎቹ


#ክፍል_ሶስት


#በኬንፎሌት


#ትርጉም_በወንዳየሁ_ንጉሴ


...ማርጋሬት እንባ አነቃት፡ ኢያን ሮችዴል በህይወቷ ውስጥ ታላቁ ክስተት ነበር ሞቱ አሁንም ስቃይ ሆኖባታል፡፡ ለአመታት ዶሮ ጭንቅላት ከሆኑ የባላባት ልጆች ጋር ፓርቲ ደንሳለች እነዚህ ልጆች ከመጠጥና
ከአደን በስተቀር አእምሮአቸው ምንም አያስብም፡፡ የእሷን አስተሳሰብ የሚጋራ የእድሜ አቻዋ የሆነ ሰው በእጅጉ ትመኝ ነበር፡፡ አንድ ቀን ኢያን በድንገትና በህይወቷ ውስጥ ዘው ብሎ ገባ፡፡ ዳሩ ምን ያደርጋል፧ እሱ ከሞተ
ወዲህ እንደገና ህይወቷን ጨለማ ወርሶታል

ኢያን በኦክሰንፎርድ ዩኒቨርሲቲ የመጨረሻ አመት ተማሪ ነበር፡
ማርጋሬትም ዩኒቨርሲቲ መግባት ምኞቷ ቢሆንም መስፈርቱን አላሟላችም፡፡አንብባለች፡ ሌላ ትምህርት ቤት ሄዳም አታውቅም ሆኖም ብዙ የምታደርገው ነገር አልነበረም:: በሀሳብ መፋጨት የምትወድ መሆኗ
ይገርማታል፡ ሀሳቡን በፍጹም ትህትና የሚገልፅላትና እስካሁን ከገጠሟት ሰዎች ሁሉ ነፃ አስተሳሰብ ያለው ሆኖ ያገኘችው ኢያንን ብቻ ነበር፡፡በውይይት ወቅት ታላቅ ትዕግስት ያሳያል፤ ባለው አቅም አይኮራም፣ያልገባውን ገብቶኛል አይልም፤ ካየችው ጊዜ አንስቶ ነበር የወደደችው፡
ለረጅም ጊዜ በመሀከላቸው የነበረው ስሜት ፍቅር ነው ብላ አታስብም ነበር፡ አንድ ቀን በማፈር እየተንተባተበ ‹‹ካንቺ ፍቅር ይዞኛል፧
ጓደኝነታችንን ያበላሽብን ይሆን?›› በማለት ተናዘዘላት፡ ያኔም እሷ በፍቅሩ መነደፏን ተረዳች፡

በዚህም ህይወቷን ለወጠው፤ ልክ ሁሉም ነገር ልዩ ወደሆነበት ሌላ
አገር የሄደች መሰላት፤ ሁሉም ነገር የሚያስደስት መሆን ጀመረ፤ ከቤተሰቦቿ ጋር የምትኖረው አጣብቂኝ የበዛበት ህይወትና ብስጭቱ ሁሉ ተረሳት፡ የዓለም አቀፉን ብርጌድ ተቀላቅሎ ህዝብ የመረጠውን ሶሻሊስት መንግሥት ለመታደግ ወደ ስፔን ሄዶም እንኳን ለህይወቷ ብርሀን ይፈነጥቅበት ነበር፡ ላመነበት ዓላማ ህይወቱን ለመስጠት በመዘጋጀቱ
ኮርታበታለች: አንዳንድ ጊዜ ደብዳቤው ይደርሳት ነበር፡ አንድ ጊዜ ግጥም ልኮላታል፡ በኋላ የመጣው ደብዳቤ ግን አስደንጋጭ ነበር፡፡ ከጠላት በተተኮሰ
ላውንቸር ሰውነቱ ተበጣጥሶ መሞቱን አረዷት፡ ማርጋሬት ከእንግዲህ አበቃልኝ! ስትል ደመደመች፡፡

‹‹መጥፎ ተፅዕኖ አሳድሮብኛል›› ስትል አስተጋባች የእናቷን አባባል
በመድገም፡፡ ‹‹ቀኖናን እንዳልቀበል፣ ሐሰትን እንድፀየፍ፣ ድንቁርናን
እንዳወግዝና ማስመሰልን እንድጠላ አስተምሮኛል፡
በመሆኑም በሚባለው ህብረተሰብ ውስጥ ቦታ የለኝም፡››

አባት፣ እናትና ኤልሳቤት በአንድ ላይ መናገር ጀመሩና ሁሉም ሰሚ
አለመኖሩን አውቀው ድንገት ዝም አሉ፡ ፔርሲ ድንገተኛውን ዝምታ
በመጠቀም ‹‹ይሁዳውያንን በተመለከተ›› አለ ‹‹ከስታንፎርድ ከመጡት ሻንጣዎች ውስጥ አንድ የሚገርም ፎቶግራፍ አገኘሁ፡፡››
ስታንፎርድ በአሜሪካ ኮኔክቲከት ክፍለ ሀገር የእናትዬው አገር ነው፡፡ ከደረት ኪሱ ውስጥ አንድ የተጨማደደና ቀለሙ የፈዘዘ ፎቶግራፍ አወጣና ‹‹ሩዝግሌንኬር
የሚባሉ ቅድመ አያት ነበሩኝ አይደለም?›› አለ።

እናትም ‹‹አዎ የእናቴ እናት ነች ታዲያ ምን አገኘህ የኔ ማር
አሉ።

ፔርሲ ፎቶውን ለአባቱ ሰጣቸው: ሁሉም ለማየት ተሰበሰቡ
ፎቶግራፉ ላይ በግምት ከሰባ አመት በፊት በአሜሪካ ውስጥ ምናልባት ኒውዮርክ ውስጥ አንድ አዳፋ የስራ ልብስ የለበሰና ኮፍያ ያደረገ ዕድሜው በግምት ሰላሳ ዓመት የሚሆነው ጢማም ሰው መንገድ ላይ ቆሞ ይታያል
ሰውየው የሞረድና ቢላ መስሪያ ጋሪ ይገፋል ጋሪው ላይ በግልፅ ሩቤንራሽቤን ብረት ቀጥቃጭ›› ይላል። አጠገቡ አስር አመት የሚሆናት ቀሚስና ቦት ጫማ ያደረገች ልጅ ቆማለች፡፡

‹‹ምንድነው ይሄ ፔርሲ? እነዚህ ድሆች እነማን ናቸው?›› ሲሉ አባት ጠየቁ።

‹‹ጀርባው ላይ የተጻፈውን እየው፣ አባባ›› አለ ፔርሲ።
አባት ፎቶውን ገለበጡ፤ ፎቶው ጀርባ ላይ ‹‹ሩዝግሌንኬር ራሽቤ
ዕድሜ 10›› የሚል ተፅፏል።

ማርጋሬት አባቷን ተመለከተች በጣም ተናደዋል፡

‹‹የእናታችን ቅድም አያት በየመንገዱ እየዞረ ቢላ የሚሰራ ሰው ልጅ ማግባቱ የሚገርም ነው፤ አሜሪካ ደግሞ እንደዚህ ናት ይላሉ›› አለ ፔርሲ

‹‹ይሄ የማይሆን ነው!›› አሉ ሎርድ ኦክሰንፎርድ ድምፃቸው ሻክሮ
ማርጋሬት ግን አባቷ ሊሆን ይችላል ብለው እንደሚያስቡ ገመተች፡
ፔርሲም በግድ የለሽነት ‹‹የሆነ ሆኖ ይሁዳነት የሚተላለፈው በእናት
በኩል ነው ስለዚህ የእናቴ ቅድም አያት ይሁዳዊ ናት፤ ይህም እኔን
ይሁዳዊ ያደርገኛል›› አለ፡፡

አባት ፊታቸው በንዴት አመድ መሰለ፡፡ እናት ፊታቸው ላይ ጥርጣሬ ተነበበበት ግምባራቸውን በመጠኑ አኮማተሩ፡፡

ፔርሲም ‹‹ጀርመኖች ይህን ጦርነት ያሸንፋሉ፡፡ ማርጋሬት ሲኒማ ቤት
መሄድ አይፈቀድልሽም፤ እማማም በዳንስ ልብሶቿ ላይ በሙሉ ቢጫ ኮከብ ትሰፋለች›› አለ፡፡
ማርጋሬት ፎቶው ጀርባ ላይ የተፃፈውን ጽሁፍ በአትኩሮት ስታይ
እውነቱ ተገለፀላት፤ ‹‹ፔርሲ!›› አለች በመደሰት ‹‹ይሄ ያንተ ጽህፈት ነው!››
‹‹አይደለም›› አለ ፔርሲ፡
ጽሁፉ የእሱ መሆኑን አውቃ ማርጋሬት በሳቅ ተንከተከተች፡፡ ፔርሲ አባቱን ለማሞኘት መሬት ላይ ወድቆ ያገኘው ፎቶ ጀርባ ላይ ፃፈበት ፧አባትም አመኑት፡ ዘረኛ ሁሉ የእኔም ዘር የተደባለቀ ይሆን እያለ ሲባንን ይኖራል፤ ይገባዋልም ስትል ማርጋሬት አሰበች።

አባት ፎቶውን ጠረጴዛ ላይ ወረወሩት፡፡
የቤት አሽከራቸው ‹‹ምሳ ቀርቧል ጌቶች›› አለ፡፡ ቤተሰቡ ተያይዞ ወደ
መብል ቤት ሄደ፡ ሲጠበስ ፕሮቲኑ ይጠፋል በሚል የተጠበሰ ምግብ
አይበሉም፡፡ እሁድ እሁድ የሚበሉት የተቀቀለ ስጋ ነው።

አባት ‹‹ፀሎት እናድርስ›› አሉ፡፡

‹‹አንድ ነገር ማድረግ ይቀረናል›› አሉ እናት ሳይታሰብ ለንግግራቸው
ትኩረት እንዲሰጥ በማሰብ ‹‹ሁላችንም ይሄ የሞኛሞኞች ጦርነት እስኪያበቃ አሜሪካ እንሄዳለን››

ለአፍታ ሁሉም በድንጋጤ ዝም አሉ፡፡

ማርጋሬት በንዴት ‹‹አይሆንም!›› ስትል ጮኸች፡፡

እናትም ‹‹ለዛሬ የሚበቃንን ያህል ተጨቃጭቀናል፤ አሁን ምሳችንን
በሰላም እንብላ›› አሉ
‹‹አይሆንም›› አለች ማርጋሬት እንደገና በንዴት አፏ መናገር
አቃተው፡ ‹‹ይህን ማድረግ አትችሉም! ይሄ . .›› ልትወርድባቸው ፈለገች።
በአገር ክዳት ብትወነጅላቸው ተመኘች፡፡ ነገር ግን ከአፏ አውጥታ መናገር አቃታት፧ ማለት የቻለችው ‹‹ይህ ጥሩ አይደለም›› ብቻ ነበር፡

‹‹አፍሽን ካልያዝሽ ውጪ ከቤት!››
አሉ አባት።

ማርጋሬት በመሐረብ አፏን ጠርጋ ከወንበሯ ተነሳችና እያለቀሰች ከመብል ቤቱ ወጥታ ሄደች፡

የአሜሪካውን ጉዞ ያቀዱት ከወራት በፊት ነው፡፡

ፔርሲ ወደ ማርጋሬት ክፍል መጣና ዝርዝሩን ነገራት ‹‹ቤቱ ተዘግቶ
የሚቆይ ሲሆን የቤት ዕቃዎች በሙሉ በአቧራ መከላከያ ጨርቅ ይሸፈናሉ ሰራተኞቹ ይሰናበቱና ርስቱ ለሰው በአደራ ይተዋል፡ ገንዘቡ ባንክ ይቀመጣል፡፡ በመንግሥት በተላለፈው የውጭ ምንዛሬ ቁጥጥር ምክንያት
ገንዘብ ወደ አሜሪካ መላክ አይቻልም፡፡ ፈረሶቹ በሙሉ ይሸጣሉ፤ ጌጣጌጦቹ
ይቆለፍባቸዋል፡››

ኤልሳቤት፣ ማርጋሬትና ፔርሲ አንዳንድ ሻንጣ ውስጥ ዕቃዎቻቸውን ከተዋል፡፡ የቀረው ዕቃ በዕቃ ወሳጅ ኩባንያ ይላክላቸዋል፡ አባት ለሁሉም
በፓን አሜሪካ አውሮፕላን የሚጓዙበትን የአውሮፕላን ቲኬት ገዝተዋል የጉዟቸው ቀን ረቡዕ ዕለት ነው።
#ባል_አስይዞ_ቁማር


#ክፍል_ሶስት


#በዘሪሁን_ገመቹ_ዋቤ


እየተከታተለን ያለ ሠው ቢኖር ሁለቱም ፊት ላይ የደስታ ካፊያ እንደተርከፈከፈባቸው የፊታቸው በድንገት ማብረቅረቅ በመመልከት   በቀላሉ ይረዳ ነበር፡፡ላዳ አስቆሙና ይዟት ገባ...በስድስት ደቂቃ ውስጥ እቤቱ ደረሱ።

ግቢ ከፍቶ ወደ ውስጥ ሲያስገባት የቤቱ አካራይ በረንዳ ላይ ቆመው ነበር..

…ልትጠፋ ደርሳ ጭልጭል እያለች ባለች አይናቸው አንዴ እሷን እንዴ እሱን እያዩ…‹‹ቃል...ሰላም ነው..?ምነው በጊዜ?""አሉት

ለእሷ ከአሮጊቷ ንግግር ስሙ ማን ነው የሚለው ጥያቄዋን በከፊል ተመለሰላት‹‹ቃልአብ፤ቃል ኪዳን፤ቃል…››ከእንዚህ ውስጥ አንዱ ነው ››አለችና በአእምሮዋ ሰሌዳ በደማቁ ፃፈችው፡፡

"ሰላም ነው እማማ..፡፡እንግዳ ስላለብኝ ነው የተመለስኩት"በትህትና መለሰላቸው፡፡

ወደ እሷ  ዞረው… የተለጣጠፈ ፊቷን በጥርጣሬ እያዩ ሰላምታ ሰጧት…እሷም እየገመገሟት  እንደሆነ ስለገመተች  ምቾት አልተሰማትም፡፡አሮጊቷ ንግግራቸውን አራዘሙ "እ...እንግዳ አገኘህ...?ደህና ነሽ ልጄ ..የጊፍቲ ጓደኛ ነሽ እንዴ?"ሲሉ ጠየቋት

የምትመልስላቸው ግራ ገብቶት ዝም ብላ አፍጥጣ ታያቸው ነበር..ጊፍቲ ማን ነች…?ምኑ ነች?››በእምሮዋ የበቀለ ምቾት የማይሰጥ ጥያቄ ነበር፡፡

ቃል ጣልቃ ገባና‹‹አይ የእኔ ጓደኛ ነች››ብሎ መለሰላቸው…አሮጊቷ ሌላ ነገር ሳይዘባርቁ ፈጠን አለና ‹‹ተከተይኝ ››በማለት ወደጓሮ ይዟት ሄደ… ፡

ቤቱን ከፍቶ ቀድሟት ገባ… ተከተለችው...፡፡እዚህ ቤት እንዲህ በአጋጣሚ እና በቀላሉ እንደገባች በቀላሉ እንደማትወጣ ታወቃት….በቃ እናቶች እንዲህ አይነት የመገለጥ እና የትንቢት አይነት ጉዳይ ሲያጋጥማቸው ተከሻዬ ነገረኝ እንደሚሉ አይነት ነው እሷም ትከሻዋ የነገራት፡፡

ቅልብጭ ያለች  ሶስት ክፍል የወንደላጤ ክፍል ነች። እቃዎቹ  ልክ እንግዳ እንደሚመጣበት አውቆ ቀድሞ ያዘጋጀው ይመስላል ።ብዙ የወንደላጤ ቤት በተለያየ አጋጣሚ  ገብታ አይታ ታውቃለች..የፈለገ ቢጠነቀቁ የሆነ  የተዝረከረከ ነገር እንደማያጣቸው ታዝባለች፡፡ ይሄ ግን እንከን አልባ ነው።

‹‹ነይ እለፊ ያው መኝታ ቤት ግቢና አረፍ በይ ..እኔ ምሳ ልስራና በልተሽ ኪኒኑን ትውጪያለሽ።››አለትና ወርቃማ ቀለም ወደተቀባ የተዘጋ የእንጨት በር በአገጩ እመለከታት፡፡

"አረ አልፈልግም አራበኝም›› አለችው...፡፡

"እኔ እርቦኛል ...ለራሴ እኮ ነው የምሰራው...ለእኔ የሠራሁትን አብረን እንበላለን...ግቢ  ..ከፈለግሽ ቁልፍ ከውስጥ ተንጠልጥሎልሻል ቆልፊና ተኚ...ምሳ ሲደርስ አንኳኳለሁ።››

በንግግሩ አሳፈረት‹‹…እኔ ያላሳብኩትን አታስቢ.ለእንደዛ አይነት ጉዳይ ፈልጌ አይደለም አቤቴ ድረስ ጎትቼ ይዤሽ የመጣሁት››ያለት ነው የመሰላት፡፡

…ከዛ ፈጠን አለችና "አረ ችግር የለውም ››ብላ ተንደርድራ ወደጠቆማት ክፍል ገባች ።በራፍን ዘጋችው..  ግን አልቆለፈችውም።

እንደሳሎኑ ሁሉ መኝታ ቤቱም በስርአት የተያዘና የሚማርክ ነው ።አልጋው ጠርዝ ላይ ተቀመጠች።ፊት ለፊት ግድግዳ ላይ የድንግል ማሪያም ምስለ ፍቁር ወልዳ ስዕል 40 60 በሚሆን መጠን ተሰቅሎ ይታያል ከዛው ስዕል ስር ከታች የልጁ የምርቃት ፎቶ አነስ ባለ መጠን ተሰቅሏል፡፡

አልጋው ላይ ቁጭ ስትል ድካሟ ሁሉ ካለበት ተሰብሰቦ ሰፈረባት፡፡ለመተኛት ፈለገች፡፡ጎንበስ ብላ ጫማዋን ለማውለቅ ስትሞክር ቅድም ታክሲ ውስጥ ያ ቋቋቴ ሽማግሌ የነረታት ቦታ ኃይለኛ ውጋት ተሠማት።እንዳምንም ጫማዋን አውልቃ አልጋ ላይ ወጣችና አልጋ ልብሱን ገለጥ አደርጋ ከውስጥ ገብታ ተኛች።

ይሄ ተአምር ነው...ለቃል ከአብሮ አደጉና ከፍቅረኛው ከጊፍቲ ውጭ ሌላ ሴት ወደእዚህ ቤት ሲያስገባ አስገብቶም አልጋው ላይ እንድትተኛ ሲፈቅድ የመጀመሪያ ቀን ገጠመኙ እንደሆነ ሁሉ ለእሷም የማታውቀውም ሆነ የምታውቀው ወንድ መኝታ ክፍሉ ድረስ ገብታ አልጋው ላይ ስትተኛ ይሄ የመጀመሪያ ቀን ገጠመኟ ነው።እርግጥ ብዙ ጊዜ እጮኛዋ መድህኔ መኝታ  ክፍል ገብታ ታውቃለች… ግን አልጋው ላይ መተኛት ይቅርና ተቀምጣም አታውቅም፡፡  ይሄንን እሷና እግዚያብሄር ብቻ ናቸው የሚያውቁት። ለሌላ ሰው ግን እንደዛ ብላ ብትናገር ከጠቅላላ ሁኔታዋ ከመሽቀርቀሯና ከቅብጠቷ አንፃር በወስጣቸው ባዳበሩት ግምት  ወይ ይስቁባታል..ወይ ያሾፉባታል።ሌላ የውጭ ሰው ሳይሆን ቤተሠቦቾ እራሳቸው እንደማያምኗት ታውቃለች  ። የገዛ እናቷ ሳይቀሩ አንዳንዴ በአግቦ ‹‹አይ የጓደኞቼ ልጇችማ ከነክብራቸው ቆይተው ይሄው በደስታ ሊዳሩ ነው…እኔንስ አምላክ እንዴት ያደርገኝ ይሆን?።››በማለት  በጎን ያላቸውን ስጋት ጠቆም ሲያደረጉ ደጋግማ ሰምታለች፡፡ …ሁሉም እንደዛ በማሰባቸው አትበሳጭም። እንደውም ከእሷ ምንም እንዳይጠብቁ   ስለሚያደርግ  ነፃነቷን ያጎናፅፉታል።

የማይረቡ አርቲቡርቲ ሀሳቦችን እያሰበች ስትብሰለሰል  በራፉ በስሱ ተንኳኳ

"አቤት  ..ክፍት ነው ግባ።››

ቀስ ብሎ ከፈተና ገባ 

"እንዴ የቆለፍሽው መስሎኝ ነበር?"አላት፡፡

"በገዛ ቤትህ  እንዴት ቆልፍብሀለሁ?"

"አይ ምቾት ካልተሰማሽ ብዬ ነው ..ምሳ ደርሷል .እዚህ ላምጣ  ወይስ ወደሳሎን መምጣት ትችያለሽ  ?›› በስንት አማላጅነት እቤቱ የወሰዳትን የክብር እንግዳውን  ጠብ እርግፍ ብሎ   የሚያስተናግድ ትሁት አፍቃሪ መሰላት….እንደዛ ስላሰበችም ፈገግ አለች፡፡

"ኸረ መጣሁ"እለችና አልጋ ልብሱን ከሰውነቷ ላይ ገፍ ከአልጋው ወረደች።ቀድሟት ወደፊት ለፊተኛው ክፍል  ተመለሰ  …. ተከተለችው፡፡ ጠረጴዛው ማዕዛቸው በሚያውድና  ለአይን ማራኪ በሆኑ ምግቦች ተሞልቷል።ገና እንዳየችው ያልነበረባት ረሀብ ተቀሰቀሰባት። ማስታጠቢያ አምጥቶ በቆመችበት  አስታጠባት...ስለምግቡ እያስበች ስለነበረ ሳትግደረደር እጇን  ታጠበችና ወንበር ስባ ተቀመጠች፡፡  ..

"ይሄን ሁሉ ምግብ በግማሽ ሰዓት....ነው ወይስ?››

"ወይስ ምን..?››ቃላቱን ከአንደበቷ ነጠቀና መልሶ ጠየቃት ፡፡

"ያው የወንደላጤ ነገር ከሆቴል  አምጥተህ እንዳይሆን ብዬ ነው፡፡"

ከት ብሎ ሳቀ ..‹‹ጥርሶቹ ውብ ናቸው….፡፡ስትል ለሁለተኛ ጊዜ በውስጧ አደነቀችው፡፡

"አይ በፍፅም አይደለም..የዕድሜ ልክ ምግብ የማብሰል ችሎታ አለኝ፡፡እናቴ አኔን ስትወልድ ነው የሞተችው.አባቴ ነው ያሳደገኝ….፡፡በዚህ የተነሳ ምግብ ማብሰል የጀመርኩት በልጅነቴ ነው፡፡ለእኔም ለአባቴም ለረጅም አመት አበሰል ነበር. ለዛ ነው...እሺ እየበላሽ..."

ታሪኩ አንጀቷን በላት..እሷም አባት የላትም፡፡ከአባቷ የተለየችው ጮርቃ ህፃን ሳለች ነው…እስከአሁን ድረስም አባቷ ይኑር ይሙት አታውቅም…ግን የእሷን ከእሱ ሚለየው ‹የአባት ፍቅር› ከሚባለው የስሜት ክፍተት በስተቀር አባቷ ስለሌለ ጎደለብኝ የምትለው ነገር የለም..፡

ሀሳቧን ገታ ለእሱ መለስችለት "እየበላሁ ነው ....እኔ ግን ማብሰል የምችላቸው ምግቦች ከሶስት አይበልጡም።"አለችው፡፡

‹‹እየቀለድሽ ነው አይደል ?››አላተ…ሲያዮት ቀበጥና ሞልቃቃ አስተዳደግ ያደገች  ልጅ እንደሆነች ተረድቷል ቢሆንም ግን እንደምትለው ፍፅም ማብሰል የማትችል ገልቱ የምትባል እንደሆነች ግን ማሰብ አልፈለገም፡፡እሷ ግን ምንም ልትደብቀው አልፈለገችም፡፡
#ህያብ


#ክፍል_ሶስት


#ድርስት_ኤርሚ

እና ሁሉም ነገር እንደዚህ ሊቀጥል ነው? አይሆንም! እናቴም እኔም አንገታችንን ከምንደፋ የሆነ ሀሳብ በውስጤ መጣልኝ። እንደማደርገው እርግጠኛ ሆንኩ....
ቤት እንደደረስን ቁጭ አድርጋ የምክር ናዳ አወረደችብኝ ግን አንዱንም ከልቤ ሆኜ አልሰማኋትም..... እንዴት እንደማደርገው እቅድ እያወጣሁ ነበር።

ሁሌም ማክሰኞ ቀን እናቴ ገበያ ትሄዳለች። ያሰብኩትን ለማድረግ ከዚህ ቀን ውጪ የተመቸ እንደሌለ አውቃለሁ ስለዚህ ማክሰኞን መጠበቅ አለብኝ።
....
የምጥ ቀን እሁድ አለፈና ሰኞ መጣ.... ብርድ ልብሴን ክንብንብ ብዬ የተኛሁ መሰልኩ። እማዬ ቤት ውስጥ ውዲህ ወዲያ ስትል እንቅስቃሴዋ ይሰማኛል። አጠገቤ መጣችና
"አንቺ ሚጣ.... ሚጣዬ..... ሚጣ" ብላ ጠራችኝ። ባልሰማ ዝም ብያት የተኛሁ እንዲመስል ጣርኩ ምክንያቱም ከዚህ በኋላ ትምህርት ቤት መሄድ በጓደኞቼ እና በሌሎች ተማሪዎች መዋረድ አልፈልግም።

እኛ ላለንበት ማህበረሰብ ይሄ ከባድ ነገር ነው። መደፈሬን የሚያውቀው ሳይቀር
"የወይንሸት ልጅ ዲቃላ አረገዘች.... ድሮም ሴት ያሳደገው" ብለው እኔን ብቻ ሳይሆን ብርቱዋን እናቴንም ጭምር ነው የሚሰብሩብኝ

"አንቺ ሚጣ... ተነሽ እንቅልፍ እንዳልወሰደሽ አውቃለሁ..." አለችኝ። ምንም ማምለጫ የለኝም ፊቴን ቀስ ብዬ ገለጥኩና አጠገቤ የቆመችውን ድንቅ ሴት ከታች ወደላይ አየኋት..... እምዬን.... እናቴን። ጎንበስ ብላ በስስት እያየችኝ ነው። ከተኛሁበት ቀና ብዬ ቁጭ እንዳልኩ አጠገቤ መጣችና ጥምጥም ብላ አቀፈችኝ።

"ልጄ የኔ ስስት.... አለሜ እኮ አንቺ ብቻ ነሽ.... በዚህ እድሜሽ እንደዚ ስብር አትበይብኝ። ምን ያክል እንደሚያም ካንቺ በላይ ይገባኛል። ህመምሽ ካንቺ የበለጠ እኔን ያመኛል። ነገር ግን ቁጭ ብለን በእንባ እና ያለፈውን መራር ጊዜ በማሰብ ነጋችንን አናጨልመውም ልጄ ትማሪያለሽ ልክ እንደምትመኝው ዶክተር ትሆኛለሽ..."

"እማ እኔ ትምህርት ቤት አልሄድም" እንባዬ ከአይኔ ክልብስ አለ። እየተንሰቀሰኩ አለቅስ ጀመር።
"አይ እንግዲህ የምን ለቅሶ ነው" አለችኝ ቆጣ ብላ ይሄን ቁጣዋን አውቀዋለው ምናባሽ.... የታባሽ..... የሚባለው አይነት ቁጣ አይደለም። ቃሏ እና ፊቷ ላይ "መፍትሄ አለው" ከሚል መልዕክት ጋር ነው የምትናገረው። ለቅሶዬን አቁሜ የምትለውን ለመስማት ተመቻቸሁ።

"ልብ ብለሽ ስሚኝ የኔ ልጅ...."
በሚገባኝ ቋንቋ አስረዳችኝ።

ሙሉ ለሙሉ ነው ሀሳቤን ያስቀየረችኝ የኔ እቅድ የነበረው ገበያ ስትሄድልኝ የገዛሁትን የአይጥ መርዝ ጠጥቼ ይህችን አለም መሰናበት ነበር። ንቁዋ እናቴ ግን እቅዴን ሁሉ ቀድማ ደረሰችበት። አዲሱን እቅዷን ከነገረችኝ በኋላ እንዲህ አለችኝ።

" ያቀድሽውን ሁሉ ደርሼበታለሁ ሚጣ.... መርዝ ልትጠጭ ነበር አይደል" ክው ብዬ ነው የደነገጥኩት
........

"እንዴት ሆኖ ከኔና ባለሱቁ ውጪ እኮ መግዛቴን የሚያውቅ አልነበረም" አልኳት ምን ያክል እንደምትደነግጥና ልታዝንብኝ እንደምትችል እያሰብኩ... ፊት ለፊቴ ያለችው ሴት ግን ፍፁም መረጋጋት ነው የሚታይባት

"ባለሱቁ ባንዴ ሶስት ስትገዢው ተጠራጥሮ ነው። በመንገድ ሳልፍ ጠርቶ የነገረኝ አልዋሽሽም እንደሰማሁ ምድር ነበር የከዳችኝ... ቶሎ ብዬ ቤት ሰመጣ በረንዳ ቁጭ ብለሽ አገኘሁሽ ያኔ ወደቤት ገብቼ ከደበቅሽበት ፈልጌ አገኘሁትና ወሰድኩት....."

"ይቅርታ እማዬ ሁሉም ነገር ጨለመብኝ ከኔ ብሶ አንቺም አንገትሽን ደፋሽ..."

"ይገባኛል ሚጣዬ አሁን ስለ እቅዱ ምን ትያለሽ...." ብላ ሀሳቤን ጠየቀችኝ። እናቴ ለኔ እንዲህ ናት አስፈላጊ ያለችው ነገር ላይ ምን ታስቢያለሽ ብላ ታማክረኛለች። ምንም እንኳን ከልቤ ባልሰማት............
..........ወይም እሷ እያወራች ለጨዋታ ጓደኞቼ ሲጠሩኝ ሳላስጨርሳት ሮጬ ብሄድ..........
....... ወይም ደግሞ የልጅ ሀሳቤን ነግሪያት ሆዷን ይዛ ፍርፍር ብላ ብትስቅ... እናቴ ልጅ ናት ብላ ልትነግረኝ እንደሚገባ ያሰበችውን ለኔ ከመንገር ወደ ኋላ አትልም። በሀሳብ ጭልጥ ብዬ ስሄድባት

" ምን ትያለሽ እያልኩሽ ነው ሚጣዬ" አለችኝ ዘልዬ ጥምጥም አልኩባትና

"እጅግ በጣም ምርጥ ሀሳብ ነው ቶሎ ብለን እናድርገው አልኳት

"ኦ ኦ ልጄ እስከምትወልጂ ድረስ እንደፈለግሽ መዝለልና መንፈራገጥ የለም። በይ አሁን ተነሽ ቁርስ እንብላና ያልኩሽን እናደርጋለን።

ለብቻዬ ሌላ ጀንበር የወጣችልኝ መሰለኝ ...... ብሩህ ተስፋ.....

የተሳፈርንበትን አውቶብስ መስኮት በትንሹ ከፈትኩት፤ በመስኮቱ የሚገባው ቀዝቃዛ አየር ከነፋስ ጋር ተቀላቅሎ በጆሮዬ ላይ ቢያፏጭም ምቾት አልነሳኝም። በመስታወት ውስጥ አሻግሬ ሰማዩን ስመለከት ፀሀይ ደም የተነከረ ሸማ መስላ ከወደ ምስራቅ ብቅ ማለት ጀምራለች። በፎቶግራፍ መቅረት ያለበት ድንቅ የተፈጥሮ ውበት። አይኔን እድማሱ ላይ ሰክቼ በራሴ ከቀናት በፊት የነበረውን ነገር ማስታወስ ጀመርኩኝ።
................

ልክ እንደዛ ስብር እንክትክት ብዬ በነበረበት ሰዓት...... ራሴን ላጠፋ ጫፍ በደረስኩበት ሰዓት..... ሀሳቤን አስቀይሮ በደስታ ያስፈነጠዘኝ የእናቴ እቅድ ይህ ነበር።

" ሁሉም ሰው የሚያውቀው የአባትሽ ወንድም አጎትሽ ያለው አዲስ አበባ እንደሆነ......." አላስጨረስኳትም

"አዎ ግን የሱ እዛ መሆን ለምን ይጠቅመናል"

"እዛ የምንሄደው እሱ አንቺን ለማስተማር ጠርቶሽ እኔ ደግሞ ካንቺ አልለይም ብዬ ነው አሉ.... ይህን ለሚጠይቀን ሁሉ እንነግራለን"

"እሺ ግን መቼም አጎቴ ጋ እንሂድ አትይኝም አይደል" አይን አይኗን እያየሁ ጠየኳት

"ለጊዜው የምናርፈው እሱ ጋር ነው ትላንትና ማታ ሱቅ ሄጄ ደውዬለት ነበር ባይዋጥለትም ሁሉንም በዝርዝር ነግሬዋለሁ"

"ምን እያልሽ ነው እማ... የወንድሜ ልጅ ብሎ አንድ ቀን እንኳን ዞር ብሎ ላላየኝ.... አንቺን ሳይቀር ወንድሙን እንደገደልሽበት ለሚቆጥረው.... ለሚጠላን ሰው ነገርሽው"
አልኳት ያልጠበኩት ነገር ነው

"አዎ እኔም አንቺም ይህን ተፅዕኖ መቋቋም አንችልም። ይሁን ብንል እንኳን የኔ ችግር የለውም አንቺ ግን ይከብድሻል ለህክምና ክትትሉም ሆነ ለትምህርትሽ አዲስ አበባ ይሻልሻል...."

"ግን እዛ ሄደንስ ምን ሰርተን እንዴት ሆነን ልንኖር..." ግራ ግብት አለኝ

" እሱ እያሳስብሽ እኔ እናትሽ ላንቺ አላንስም አንቺንም ልጅሽንም ማኖር አይከብደኝም ዳገት ወጥቼም ሆነ ቁልቁለት ወርጄ ህልምሽን እንድታሳኪ አደርግሻለሁ። ታዲያ ለዚህ ያንቺ ጥንካሬ ወሳኝ ነው። በይ አሁን ለጠየቀሽ ሁሉ ካልኩት ውጪ እንዳትናገሪ ነገሮችን ላስተካክልና በጥቂት ቀን ውስጥ እንሄዳለን።

ከሀሳቤ ስመለስ እናቴን ዞር ብዬ አየኋት ጭልጥ ያለ እንቅልፍ ውስጥ ናት።
መስኮቱን ተደግፌ አይኔን አድማሱ ላይ ተከልኩ

፧፧
ከኔ አካል ቅጥነት ጋር ሲነፃፀር ሆዴ ትልቅ ሆኖ ላየው ይሰቀጥጣል። ምጤ መቶ ሆስፒታል ገብቻለሁ
"አይዞሽ በርቺ..... ግፊ.... አይዞሽ እንደሱ..... በርቺ..... ግፊ" ብዙ ጊዜ ደጋግመው ቢሉኝም ያለኝን አቅም አሟጥጬ ባምጥም ልጄ ሊወለድ አልቻለም። እኔ ግን እቅት ድክም አለኝ የሚሉት በሰመመን ይሰማኛል...

"የልብ ምቷ በጣም እየወረደ ነው ባስቸኳይ ዶክተር ፋሲልን ጥሪ" ልሞት ነው ማለት ነው። የሰዎች መሯሯጥ ድምፅ ተሰማኝ ትንሽ ቆየት ብሎ

"በአስቸኳይ ወደ ቀዶ ጥገና ክፍል አስገቧት ይህቺን የምታክል ትንሽ ልጅ እንዴት በምጥ እንድትወልድ ታደርጋላችሁ..."
#ተአምራተ_ኬድሮን


#ክፍል_ሶስት
፡፡
#በዘሪሁን_ገመቹ_ዋቤ
///

አይኑን አይታ በመጠኑ ከተረጋጋች በኃላ‹‹ቻው በቃ.. ልሂድ››አለችው፡፡

‹‹አረ ትንሽ ቆይ..እስቲ ስምሽን ንገሪኝ?››

‹‹ምን ያደርግልሀል?››

‹‹ያው የቆንጆ ልጅን ስም ማወቅ ያጓጓል ..ለዛ ነው፡፡››

በንግሩ አፈረችና አቀረቀረች፡፡በጀርባው ተንጋሎ በመዋኘት ወደ እሷ እየተጠጋ…እንደመለመንም እንደማሳዘንም በሚመስል የድምፅ ቅላፄ..፡፡‹‹ንገሪኛ ፡፡››አለት..

‹‹በሬዱ››መለሰችለት፡፡

‹‹አንቺ ቆንጆ ስምሽም ቆንጆ አሪፍ ነው፡፡››አላት፡፡

ፈራ ተባ እየለች ‹‹ያንተስ..?››ጠየቀችው፡፡

‹‹የእኔን ሌላ ቀን ከእነ ትርጉሙ አነግርሻለሁ፡፡››

‹‹እንዴ ሌላ ቀን እንጋናኛለን እንዴ?››በድንጋጤ ጠየቀችው፡፡ጥያቄዋ  ማረጋጋጫ እንዲሰጣት  የመፈለግ አይነት ነው፡፡

የልብ አውቃ ነው‹‹እንዴ !!!ትቀልጂያለሽ እንዴ ..?እኔ እና አንቺ ገና ብዙ ጊዜ ይኖረናል …ብዙ ታሪክ እንጽፋለን፡፡››ሲል ፍርጥም ብሎ መለሰላት፡፡

‹‹የምን ጊዜ…?የምን ታሪክ..?››

‹‹የፍቅር ታሪክ ፡፡››

‹‹የፍቅር ….?ምን አይነት

አይን-አውጣነት ነው…አረ እኔ እንደዚህ አይነት ነገር አላውቅም፡፡››አለችው፡፡

‹‹እንደማታውቂ አውቃለሁ…. እኔም እንዳንቺው አላውቅም ….ግን አብረን እንማረዋለን፡፡››ብሎ ይበልጥ አሳፈራት፡፡

‹‹በል ይበቃሀል አሁን ልሂድ..ብላ የግዷን ጄሪካኗን አንጠልጥላ ተሸከመችና ፊቷን አዞረች፡፡

‹‹በይ ደህና ዋይልኝ..ነገ በዚህን ሰዓት እጠብቅሻለሁ፡፡››

መራመዷን ሳታቋርጥ‹‹አታስበው…..ግን የእውነት እቤትህ እዚሁ ሳይሆን አይቀርም ?›› አለችው ፡፡

‹‹አሳይሻለው ብዬሽ የለ..? አሳይሻለው፡፡››መቶ ሜትር ያህል ከራቀች በኃላ ዞር ብላ አየችው.. ደብዛው የለም‹‹…መልሶ ሰምጦ ይሆን..?ይሄ አፍዛዝ ውበት ያለው ልጅ ሰይጣን ሳይሆን አይቀርም..?የወንዝ ሰይጣን…ግን እንዲህ አይነት ጠንበለል ሰይጣን ካለማ ይገርማል?››ስትል አብሰለሰለች፡፡
ቤተ-ክርስቲያን ግድግዳ ላይ የተለጠፈው ስዕል በቅዱስ ሚካኤል እግር ተጨፍልቆ የሚታየውን አስፈሪው ሰይጣን በምናቧ መጣባትና..ከዚህኛው ጋር አስተያይታ በራሷ አፈረች..‹‹..በስመአብ ይቅር ይበለኝ…››አለች፡፡
///

በተረጋገጠ ሁኔታ ከዛ የወንዝ ዓሳ ፍቅር ያዛት፡፡በቃ ህሊናዋን ማዘዝ፤እርሷን መቆጣጠር እስኪሳናት ድረስ አደጋ ላይ ወደቀች፡፡ የሚገርመው ደግሞ ይሄ የሆነው ከስድስት ወር ግንኙነት በኃላ አይደለም…ሶስት ወርም አይሞላውም….በአንድ ሳምንት ውስጥ ነው ስሜቷ ተርገብግቦ እዚያ ደረጃ ላይ የደረሰው፡፡
ሁኔታዋን እራሷ በራሷ ስትታዘበው የዓይኖቾ ቅንድቦች መገለጥ እሱን ለማየት ባለት ፍላጎት የሚታዘዙ፣የከንፈሯ መሸልቀቅ እና የጥርሶቾ መላቀቅ ለእሱ ንግግር መመሰጧን ለማብሰር የሚውሉ ምልክቶች እንደሆኑ፣የእግሮቾ መንቀሳቀስ እሱ ወዳለበት ለመሄዱ ባላት ፍላጎት  የሚሰሩ እየመሰላት  ከመጣ ቀናቶች አልፈዋል…፡፡አዕምሮዋንማ  በቃ  ሙሉ በሙሉ በምርኮ ተቆጣጥሮታል፤ከእሱ መልክ በስተቀር ሌላ ምንም ምስል የልተለጠፈባቸው  ኦና ሆኖባታል….፡፡

ከተገናኙ በሰባተኛ ቀናቸው  ነው፡፡ሰሞኑን ታደርግ እንደነበው የውሀ መቅጃ ጄሪካኗን ተሸክማ ከለሊቱ  11፡30 አካባቢ ሲሆን ያዶት ወንዝ ደርሳ ወንዙ ጠርዝ በመቆም ከላይ ከጥቅጥቅ ጫካ ውስጥ እያፏጨና እየተስገመገመ የሚመጣው የውሀው ማዕበል እግሯን እያቀዘቀዘላት  ደንዝዛ ቆማለች፤አይኖቾ ወንዙ ውስጥ ተተክሏል …ፈዛለች….ቡልቅ ብሎ ከወንዙ የሚወጣውን  የፍቅር ዓሳዋን ጥበቃ ፡፡ ሊታክታት ትንሽ ነው የቀራት…..‹‹ግን ጥበቃ እንዴት ይሰለቻል…? በተለይ  ከገነት ወንዝ የተቀዳ የፍቅር ጠበል ይዞ የሚመጣን የልብ ጀግናን መጠበቅ ሲሆን ይከብዳል፡፡››አለች…
ግን ደግሞ አሁንም ጥበቃዋን  ቀጥላለች…5 ደቂቃ ..10 ደቂቃ…. .በቆመችበት  እግሯን ደነዘዛት፤ባፈጠጠችበት አይኖቾን ቆጠቆጣት፤የያዘችውን  ጄሪካን እንኳን አላስቀመጠችም፤ አንከርፍፋ  እንደያዘችው ነበር….፡፡ ሌላ 10 ደቂቃ በጥበቃ ባከነ....ሰማዩ ፈገግ እያለ ለመንጋት እየተግደረደረ ነው…፡፡
‹‹ልጅ የለም...ምን ዋጠው……?.የታበቱ ሄደ?››አእምሮዋን ያጨናነቁባት ጥያቄዎች ነበሩ፡፡በዚህ አይነት ሁኔታ 15 ደቂቃ ከጨመረች  ነግቶ ሰው መምጣት ይጀምራል…ሰው መምጣት ጀመረ ማለት ደግሞ እሱም የመምጣቱ ጉዳይ አከተመ ማለት ነው?እሱ ሰው እንዲያየው  እንደማይፈልግ በውስጧ ታምናለች፡፡ እንደውም አንዳንዴ መንግስት እጅ ላለመግባት በድብቅ ተሸሽጎ የሚኖር ሽፍታ ሁሉ ይመስላታል፡፡  ማስረጃው ደግሞ….ሰለእሱ አንድ የምታወቀው ነገር ቢኖር እሱን ማግኘት ከጀመረችበት  የአንድ ሳምንት ጊዜ  ውስጥ አንድም ቀን በደንብ እስኪነጋ እና ሰው ወደወንዙ መምጣት  እስኪጀምር  አብሯት ቆይቶ አለማወቁና ከወንዝ ውጭ በየትኛውም የከተማው ክልል አይታው አለማወቋ ነው፡፡
በደመነፍስ አንድ ውሳኔ ወስነች፡፡ጄሪካኗን በቁሟ ለቀቀችው፡፡ከድንጋይ ጋር ተጋጭቶ ጓ…ጓ..ጓ የሚል ድምጽ አሰማና  ቦታ ይዞ ተቀመጠ ፡፡ጄሪካኗን ለማዘያም ለብርድ መከላከያም ብላ  ተከናንባ  የነበረውን ፎጣ ከላዮ ላይ ገፈፈችና ስሯ ያለ የዛፍ ቅርንጫፍ ላይ አንጠለጠለችው፡፡ከዛ ከፍ የሚል ድንጋይ ላይ ወጣች…ቀጥሎ ተወርውራ ወንዙ መሀከል ዳይቨ ሰመጠች……፡፡
ልክ እግሮቾ ድንጋዩን ለቀው በመስፈንጠር አየር ላይ እያለ ነበር ልብሷን ማውለቅ እንዳነበረበረባት ያስታወሰችው‹‹….ምን መሆኔ ነው …?ከነልብሴ መሆኔ አንደኛ እንደልብ ለመዋኘት አያመቸኝም …ሁለተኛ  እርጥብ ልብስ ለብሼ እየተንዘፈዘፍኩ ወደ ቤት ስመለስ ሰው በመንገድ ላይ ሲያገኘኝ ምን ይለኛል…? ቤተሰቦቼስ.…?የራሳቸው ጉዳይ …አሁን አንዴ ገብቼያለሁ…፡፡› በማለት እራሷን ለማፅናናት ሞከረች፡፡
ለአንድ ሁለት ደቂቃ ያህል  እየዋኘች ወደ ላይ ወደታች ተገለባበጠች..ከዛ ወደስር  ወደወንዙ ጥልቅ ሰመጠችና አፏን ዘግታ  ዓይኖቾን ከፍታ ማሰስ ጀመረች፤ግን አልተመቻትም ፡፡ወዲያው ወደ ላይኛው የውሀ ወለል ወጣችና ወደ ዳር ተጠጋች…..
ከወንዙ ሳትወጣ የለበሰችው  ቀሚስ ወደላይ ሞሽልቃ አወለቀችና  ዳር ላይ ከሚገኝ ድንጋይ ላይ በማስቀመጥ በፓንት ብቻ ወደ ውስጥ ተመልሳ በመስመጥ ውስጥ ለውስጥ እንደዓሳ ነበሪ  እየተሹለከለከች መዋኘቷን ቀጠለች፡፡በወንዙ የመሀከለኛ ወለል እየዋኘች ሳለ የሆነ ጠንካራና ፈርጣማ ክንድ ያለው ፍጥረት ከስሯ  በማታስበው  ፍጥነት እና ድንገተኝነት ሰቅስቆ ገብቶ በጀርባው አዝሏት ወደላይ የወንዙ ወለል ይዞት ሲወጣ እሪታዋን አቀለጠችው …

ይቀጥላል
#ትንግርት


#ክፍል_ሶስት


#በዘሪሁን_ገመቹ_ዋቤ


በማግስቱ ሁሴን ገና በጊዜ አንድ ሰዓት ላይ ነበር ወደቤቱ የገባው፡፡ ቀኑን ሙሉ በአንድ ሀሳብ አይምሮው ተጠፍንጎ ስለ ምስጢር ሲያስብ ነው የዋለው፡፡ እንደገባ ያረፈበት ለወትሮው ምቾትን የሚለግሠው የቤቱ ሶፋ ዛሬ ቆረቆረው፡፡ ሞባይሉን ከኪሱ አወጣና መጎርጎር ጀመረ፡፡ ቀን ደውላለት ነበር... ያደረጉትንም የስልክ ልውውጥ ቀድቶታል... ከፈተው፡፡ ደጋግሞ ሲያዳምጠው ይሄ ለ13ተኛ ጊዜ ነው፡፡ እያንዳንዷን ከአንደበቷ የወጡትን ቃላቶች ሸምድዳቸው ተብሎ በፍርድ ቤት ውሳኔ የተላለፈበት ፍርደኛ ይመስላል፡፡ ሞባይሉ ማውራት እሱ ማዳመጥ ጀመረ፡፡

‹‹ከየት ነው ምትደውይው?››

‹‹ከየትስ ቢሆን ምን ይፈይድልሀል?.ይልቅ ለምን ደወልሽ?የሚለው ጥያቄ አይቀልም?››

‹‹እንደዛ ብዬ እንኳን አልጠይቅሽም፤ ዋናው መደወልሽ ነው እንጂ የደወልሽበት ምክንያት ብዙም አያስጨንቀኝም፡፡››

‹‹የውክልናው ወረቀት ደረሠህ?›› ቀጭን ማራኪ ድምፅ፡፡

‹‹አዋ>>

ደርሶኛል...ታደርጊዋለሽ ብዬ ግን አላመንኩም ነበር፡፡››

«ለምን?»

‹‹እኔ እንጃ፤ይሄን ያህል እንዴት ልታምኚን ቻልሽ... ?ግራ የሚገባ ነገር ነው፡፡ በነገራችን ላይ እስከ አሁን በእኛ ጋዜጣ ላይ ከታተሙልሽ ሃያ ሰባት የሚሆኑ አጫጭር ልብወለዶች መካከል አስራ ሁለቱን መርጬ አንብበው አስተያየታቸውን እንዲሠጡኝ ለሁለት ታዋቂ ደራሲያን ሠጥቼያቸው ነበር...፡፡ >>

ጉጉት በማይታይበት የቀዘቀዘ ድምፅ‹‹ጥሩ ነው።>>

‹‹አንደኛው ምን እንዳለኝ ታውቂያለሽ? ‹ይሄ ድርሠት በአማተር ፀሀፊ ተጻፈ ብትለኝ ፍፁም አላምንህም፤ እርግጠኛ ነኝ ፀሀፊው አንተ ራስህ ነህ፤ በስምህ ላለማሳተም መቼም በቂ ምክንያት ይኖርሀል፤ ምስጢር የሚለውን የብዕር ስም ግን ለምን መጠቀም እንደፈለክ ፍፁም አልገባኝም ፡፡ ›ነበር ያለኝ፡፡

‹‹ታዲያ ለምን በራስህ ስም አታሳትመውም?››

‹‹ትቀልጂያለሽ እንዴ?››

‹‹እውነቴን ነው፡፡››

‹‹ቀልዱን አቁሚ... በዚህ ወር መጨረሻ መፅሀፍሽ ይታተማል፤ የምረቃ ፕሮግራም ለማዘጋጀት አስቢያለሁ፤ዝግጅቱ ላይ መቼም ትገኚያለሽ?››

‹‹ኪ...ኪ..ኪ.›› ከት ብላ ሳቀች፡፡ደነገጠ፡፡ ሣቋ ከሆነ ከሚያውቃት ሴት ሳቅ ጋር ተመሳሰለበት፡፡

‹‹ምን ያስቅሻል?››

‹‹አታስብ አልመጣም፡፡››

‹‹ኦ! ....ኧረ በፈጠረሽ ልታቀውሽኝ ነው? ስራዬን በትክክል መስራት እንኳን እየተሳነኝ ነው እኮ፡፡››

‹‹የማይመስል ነገር፤ በአካል እኮ አታውቀኝም::>>

‹‹ምንም ሁኚ ምንም አፈቅርሻለሁ፤ፍፁም ልረሳሽ አልችልም... ነፍስሽን ነው ያፈቀርኳት፤እስቲ በፈጠረሽ ስለ ራስሽ ጥቂት ንገሪኝ...?>>

‹‹ስለ አቋሜ ማለትህ ነው?››

«ይቻላል አዎ::>>

‹‹እንግዲህ እኔ ሦስት አይነት ሰው ነኝ፤እንደ አያቴ፣እንደ ጓደኞቼ እና እንደ አፋቃሪዎቼ...>>

<<ብታብራሪልኝ?>>

‹‹አያቴ ነፍሷን ይማርና የእኔ መላአክ ነበር የምትለኝ፤እሷ ስታደናንቀኝ ክንፍ ሁሉ ያበቀልኩ መስሎ ይሰማኝ ነበር፤ እንደሷ ምልከታ እንከን አልባ አይነት ነኝ፡፡እንደ ጓደኞቼ ደግሞ ቆንጆም ያልሆንኩ ፤ የማላስቀይምም እንደው በድርባቡ አርገው ነው የሚገልፁኝ፡፡ አፍቃሪዎቼ ደግሞ አያቴ እንደምትለው መላአክ ነበርሽ ይሉና፤ ዳሩ ምን ያደርጋልን!! ይጨምሩበታል፡፡››

‹‹ምን ማለት ፈልገው ነው?››

‹‹ቆንጆ መሆኔን አረጋግጠው ...አይነ ስውር በመሆኔ የተሰማቸውን ቅሬታ ለመግለፅ ፈልገው ..››ንግግሩ ተቋረጠ፡፡

<< ትሁን...አይነስውር ትሁን፤ከፈለገች በዊልቸር ትሂድ፤የፈለገችውን ትሁን፤እወዳታለሁ….አፈቅራታለሁ፡፡ከራሱ ጋር ሲያወራ በእጁ ያንከረፈፈው ሞባይሉ ጮኸ፡፡ ኤደን ነበረች፡፡

‹‹ደህና ዋልሽ?››

‹‹ደህና ነኝ..ምነው ጠፋህ?››

‹‹ስራ በዝቶብኝ ነው፡፡››

«የት ነህ?>>

‹‹ቤት ነኝ፡፡››

<<እየመጣሁ ነው፡፡››

<<ወዴት?>>

<<አንተ ጋር ነዋ>>::»

‹‹የተጨናነቀ ስራ ላይ ነኝ፤ብቻዬን መሆን ነር የምፈልገው፡፡››

‹‹ናፍቀኸኛል እኮ!!››

‹‹ከናፈቅኩሽ ነገ እንገናኛለን... ከደበረሽ ደግ ጓደኞችሽ ጋር መሄድ ትችያለሽ፤ እኔን ግን ተይኝ ብቻዬን መሆን እፈልጋለሁ...

ቻው፡፡››ብሎ ስልኩን ጆሮዋ ላይ ጠረቀመባት፡፡ እንዲህ አዕምሮው በተጨናነቀበት ወቅት ከኤደን ጋር መገናኘት ፍፁም አይፈልግም፡፡ በጭቅጭቋ ይበልጥ ታበግነዋለች‹‹ ቅራቅንቦ ጥያቄዎቿን መመለስ ከቀን ስራ በላይ ይከብዳል፡፡›› ይላል፡፡

‹‹ምን ሆነሀል?ምነው ጠቆርክ?...ከማን ተጣለህ?.. ካመመህ ሀኪም ቤት እንሂድ፡፡›› ወዘተ፤ሳይለያዩ ይሄን ሁሉ ዘመን እንዴት አብረው ሊቆዩ እንደቻሉም ግርም ይለዋል፡፡ ስለ አብሮነታቸው ዘውትር እቅድ እንዳወጣች ነው፡፡ አንድም ጊዜ ግን ተሳክቶላት አያውቅም፤ያም ሆኖ ግን ተስፋ አትቆርጥም፡፡ ከተቀመጠበት ተነሳና ሳሎን ውስጥ ተንጎራደደ፡፡ አዕምሮው ፍፁም ሊረጋጋለት አልቻለም፡፡ ወደ ውጭ ሊወጣ ፈለገ፡፡ ሠዓቱን ተመለከተ ፤ሁለት ሠዓት ተኩል ይላል፡፡ ሀሳቡን ቀየረና ስልኩን ደወለ፤ ዘና የሚያረገው ሰው ፈለገ፡፡

‹‹ሄሎ... ትንግርት፡፡››

‹‹እሺ የኔ ፍቅር፡፡››

‹‹አለሁልሽ .. የት ነሽ?››

‹‹ቤተ መንግስት የራት ግብዣ ላይ ነኝ፡፡››

ፈገግ አለ ‹‹ከምሬ ነው፡፡››

‹‹አንድ ደንበኛዬ ጭን ላይ ቁጭ ብዬ እያጋልኩት ነው፡፡››

‹‹መምጣት አትችይም?>>

‹‹ቢዝነስ እኮ ተነጋግሬአለሁ>>

<<ስንት?>>

‹‹የዛሬው ዋጋዬ አራት መቶ ሃምሳ ነው..... ከትላንቱ ትንሽ ረከስ ብያለሁ፡፡››

‹‹ወደ ትላንቱ ዋጋሽ ልመልስሻ ..እኔ ጋር ነይ::>>

‹‹ቀነዘረብህ እንዴ?››

‹‹ብዙም አይደል፤ ብቻ አስፈለግሽኝ... ያቺን ደራሲ ለሠዓታትም ቢሆን እንድታስረሽኝ እፈልጋለሁ፡፡››

<ኦ! ... ምን አይነት እድለኛ ነች ባክህ ... ቀናሁባት፡፡ ለማንኛውም መጣሁ፡፡ የተሻለ ዋጋ ከከፈልከኝ ጨረታውን ሙሉ በሙሉም ሆነ በከፊል የመሠረዝ መብቴ በሸርሙጦች መተዳደሪያ ደንብ የተከበረ ነው፡፡››

‹‹በሙሉ ሰርዥው›› አለ ቆጣ ብሎ፡፡ በከፊል ስትል ምን ማለት እንደፈለገች ገብቶታል፡፡ ደንበኛዋ እንዳይቀየማት አንዴ ከውጥረቱ እንዲረግብ ረድታው ለመምጣት ነው፡፡ ይሄ ደግሞ ለሁሴን አይመቸውም፡፡ ቢያንስ እሱ ጋር በምታድርበት ቀን የሌላ ወንድ ጠረን ይዛበት እንድትመጣ አይፈልግም፡፡ተሠነባበቱና ስልኩን ዘግቶ ወደ ሶፋው ተመለሰ፡፡

ሪሞቱን ከጠረጴዛው ላይ አነሳና ቴሌቪዢኑን ከፈተ፡፡ ምን አይነት ፕሮግራም እየተላለፈ እንደሆነ ለማሰብ ሳይጨነቅ ወደ ሀሳቡ
ተመልሶ ተዘፈቀ፡፡ ረዥም ቆንጆ ውብ ወጣት በአየር ላይ እየተንሳፈፈች ወደ እሱ ስትመጣ ይታየዋል፡፡ በግራ እጇ አቅጣጫ መጠቆሚያ ዘንግ ይዛለች፡፡ በቀኝ እጇ ደግሞ አዲስ የፈነዳ እምቡጥ ፅጌሬዳ አበባ ይታየዋል፡፡አይኖቿ አይታዩም፤በጥቁር መነፅር ተሸፍነዋል፡፡ ፈገግ እያለች አበባውን እንዲቀበላት ትማጸነዋለች፡፡ እሱ ደግሞ አበባውን ከመቀበሉ በፊት ከአይኖቿ ላይ የሚያስጠላውን ጭለማ መነፅር አውልቃ እንድትጥለው .. የማያዩትን አይኖቿን ቀጥታ ማየት እንደሚፈልግ እየነገራት ሳለ የሳሎኑ በር ተንኳኳ፡፡ ከጣፋጭ ሀሳቡ ነቅቶ ተነስቶ ከፈተ፡፡
#ቤርሙዳ_ዘ_ካሳንችስ


#ክፍል_ሶስት


#በዘሪሁን_ገመቹ_ዋቤ


ፋሲል ጥሏት ከሄደ ከ5 ሰዓት በኋላ ደወለላት..ከእንቅልፏ ነቅታ እዛው አልጋ ላይ እየተገላበጠች ስታስብ በነበረበት ጊዜ ነበር የደወለላት እና ለእራት የቀጠራት፡፡እየደበታትና ከዛም ተነስቶ እራስ ምታት እየጀማመራት ስለነበር የእራቱን ግብዣ በደስታ ነበር የተቀበለችው…፡፡በዛ ላይ መቼ እንደሆነ ባታውቅም በቅርብ የምታጣው ሰው ስለሆነ እንደመሰናበቻ አሪፍ አሪፍ የተባሉ ጊዜያቶችን ከእሱ ጋር ማሳለፍ ትፈልጋለች፡፡ለዚህ ነው ብዙ ሳታስለምነው በመስማማት ለባብሳና ተቆነጃጅታ ወደቀጠራት ቦታ ሄደችው፡፡

ፋሲል ከሳራ ጋር ያለው ለአንድ አመት ከሁለት ወር የዘለቀ የፍቅር ግንኙነት ህይወቱን ምስቅልቅል አድርጎበታል፡፡እርግጥ የእሱ ህይወት መቼም ከመርመስመስ ርቆ አያውቅም፡፡አሁን ግን ችግሩን የተለየ ያደረገው ማፍቀሩ ነው፡፡22 ዓመት ሆኖት በ11 ዓመት ምትበልጠውን በዕድሜ ታላቁ የሆነችዋን ሴት ከልብ አፍቅሯታል፡፡እርግጥ እሷን ብቻ ሳይሆን ብሯንም ከእሷ እኩል  ነው የሚያፈቅረው፡፡ ግን የሚገርመው ምንነቷን በጥልቀት አያውቅም:: ሀገር ቢያንሾካሹክበትም..ጓደኛቹ ቢያላግጡበትም ለእሱ ለውጥ አያመጣም.. በቃ አፍቅሯታል፡፡ እሷ ግን ታፍቅረው ወይስ  ዝም  ብላ  እንደመደበሪያ  እያየችው ይሆን? በእርግጠኝነት መናገር አይችልም፡፡ግን ማመን የሚፈልገው እንደምታፈቅረው ነው፡፡ቢሆንም ስሜቷን አንብቦ ፍላጎቷን መተንበይ ለእሱ ኪሊማንጀሮን ተራራ በሩጫ የመውጣት ያህል ከባድ ነው የሆነበት፡፡ሁለ ነገሯ ግራ ያጋባዋል…ንግግሯ ግራ ያጋባዋል…አኗኗሯ ግራ ያጋባዋል..የወሲብ ልምዷ ግራ ያጋባዋል..የወደፊት ዕቅዷ ሳይቀር ግራ ያጋባዋል፡፡

እርግጥ እሱ በእሷ ፍቅር ተንኮታኩቶ እንዲወድቅ ካደረገው ሁለት ዋና ዋና ምክንያቶች አንዱ በየቀኑ ያለስስት የምታስጨብጠው  ረብጣ  ብር  ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ይሄ ግራ አጋቢውና  ነፍሱን  ስልብ  የሚያደርገው  የወሲብ አሰራሯ ነው፡፡በቃ እንደኮኬይን ዕፅ ሱስ ሆኖበታል፡፡ሊተውት የማይቻል  ክፉ ሱስ፡፡ግን ቢሆንም ለዘላቂ ጥቅሙ ሲል ማድረግ የሚገባውን ነገር ሁሉ ለማድረግ ቁርጥ ያለ ውሳኔ ላይ ደርሷል፡፡

ከተቻለ ይህቺን ሴት ፍጹም ማጣት አይፈልግም፡፡ በአስቸኳይ አንድ ነገር ማድረግ እንዳለበት ማሰብ ከጀመረ ሰነባብቷል..ዛሬ ዝግጅቱን አጠናቆ ዕቅዱን ወደተግባር የሚቀይርበት ቀን ነው፡፡ ሊያስደንቃት ወስኗል፡፡
የቀጠራት ሆቴል ብዙውን ጊዜ የሚገናኙበት  ነው፡፡ሁለቱም  ከሆቴሉ ባለቤቶች ሆነ ከአስተናጋጆቹ ጋር ጠንከር ያለ ትውውቅ አላቸው….ስትደርስ ሆቴሉ በተስተናጋጆች ተሞልቷል፡፡ከገመተችው በላይ ሰዎች መኖራቸው ብቻ ሳይሆን በተለያየ ጊዜ ወንድሜ ነው፤ ጓደኛዬ ነው ፤የአጎቴ ልጅ ነው እያለ ያሰታዋወቃት ስድስት ሰባት የሚሆኑ በእሱ በኩል የምታውቃቸው ሰዎች ሁለትና ሶስት ሆነው እዚህና እዛ ተቀምጠው ስታይ ያልተለመደ ነገር ስለሆነባት ግራ ተጋባች…እውነታው በእሱ ሚስጥራዊ ግብዣ  ተጠርተው  የመጡ  የቅርቡ ሰዎች ናቸው፤ሌሎቹ ደግሞ ባጋጣሚ እግር ጥሏቸው የታደሙ የሆቴሉ ቋሚና ድንገተኛ ደንበኞች ናቸው፡፡ሁሉ ነገር ሙሉና ባሰበው መልኩ የተቀናጀ ቢሆንም አንድ ነገር ግን ቅር አሰኝቶታል..

የኤልሳ እዚህ መገኘት  ነው፡፡ኤልሳ  የልጅነት  ፍቅረኛው  ነበረች፡፡ነበረች  ማለት አሁን ግንኙነታቸውን ሙሉ በሙሉ አቁመዋል ማለት አይደለም፡፡በተለያየ ጊዜ እየተገናኙ ሳባ እንዳታውቅ እየተጠነቀቀ ይገባበዛሉ..አብረው ይቅማሉ.. አብረው ይጨፍራሉ አልፎ አልፎም አብረው  ያድራሉ፡፡ከዛ  በላይ  በጣም  አደገኛው  ነገር ሁሌ ኤልሳ ስለእሱ እና  ስለሳባ  ግንኙነት በምትጠይቀው ጊዜ የሚመልስላት መልስ ፈፅሞ እሷን እንደማያፈቅራት፤ የቀረባት ለገንዘቧ ሲል ብቻ እንደሆነና እንደምንም ጠቀም ያለገንዘብ ከተቀበላት በኃላ አፍንጫሽን ላሺ ብሎ እሷኑ እንደሚያገባ ከመቶ ጊዜ በላይ ነበር እየማለ ያረጋገጠላት፡፡እውነታው  ግን ዛሬ እየሆነ ያለው ነው፡፡ ፋሲል ሳባን የሚያፈቅራትን  ያህል  ኤልሳ  ደግሞ  እሱን  ታፈቅረዋለች፡፡ለዚህ  ነው ስለ ዛሬው ዝግጅት ዕቅድ ሚስጥራዊ ሆኖ ከእሷ ጆሮ እንዲጠበቅ አጥብቆ ተግቶ የነበረው..አልተሳካለትም እንጂ..አሁን ነገር እንዳታበላሽበት ልቡ ፈርቷል፡፡

በቅርቡ ሳባ የገዛችለትን የጣሊያን ሱፍ ለብሶ ዝንጥ ብሏል..ሳባ ልዩ የሆነ ረጅም ብርቱካናማ የራት ልብስ ለብሳለች፡፡ሁለቱም ውብ ሆነዋል፡፡እራት ቀረበ… ወይን ተቀዳ…ምግቡ በመጐራረስ ተበልቶ መአዱ ከፍ ካለ በኃላ ፋሲል ከመቀመጫው ተነሳና ወደመድረኩ ተንቀሳቅሰ፤ ሙዚቃውን አዘግቶ ማይኩን   ተቀበለና ጉሮሮውን አፀዳድቶ መናገር ጀመረ፡፡‹‹የእኔ ፍቅር በአሁኗ ሰዓት እዚህ በታደመው ህዝብ ፊት ላንቺ የምናገረው አንድ ነገር አለኝ››አለ፡፡የሆቴሉ   አዳራሹ ሙሉ በሙሉ ፀጥ አለ..ለወሬ የቋመጡ ጆሮዎች ከየአቅጣጫው   ተቀሰሩ፡፡እሷ ደስ የማይል ነገር ውስጧ ተፈጠረ‹‹እባክህ አታድርገው…እኔ አንተን መቼም ማግባት አልፈልገም››አለች በልቧ፡፡

‹‹ማይኩን እንደያዘ ወደእሷ ቀረበና ከፊት ለፊቷ  ተንበረከከ፡፡ልክ  በሆሊውድ ፊልም ላይ ሲደረግ እንዳየው እሷ ከምትሰጠው ገንዘብ ቆጥቦ የገዛውን የጋብቻ ቀለበት ከኪሱ ውስጥ አወጣና፡--------

‹‹የእኔ ፍቅር ሚስቴ እንድትሆኚ እፈልጋለሁ.. ታገቢኛለሽ?››

ሲል በጥርጣሬም በፍራቻም ጠየቃት፡፡በእሷ ላይ ምንም አይነት የስሜት ለውጥ አልታየም፡፡ አልበረገገችም፤ አልተፍለቀለቀችም፡፡ አልተኮሳተረችም፡፡ብቻ በፊት  በነበረችበት ሁኔታ ፀጥ ብላ ተቀመጠች፡፡ምን ማድረግ እንዳለባት ግራ ስለገባት ነው ደንዝዛ የነበረው…ገፍትራው ቤቱን ጥላ ትውጣ…ወይስ ጣቷን ቀስራ እንዲያጠልቅላት ትፍቀድለትና ስለቀጣዩ ጉዳይ ቀስ ብላ ታስብበት.ይሄንን ነገር  የመሞከር ዕቅድ እንዳለው ታውቃለች.ግን እንዲህ በፈጠነ ቀን ለማድረግ ይሞክራል ብላ ፈፅሞ ግምቱ አልነበራትም..ያ ነው በጣም እንድትደነግጥ ያደረጋት፣ይሄንን በማሰላሰል ከእራሷ ጋር ሙግት ገጥማ ባለችበት ጊዜ
ፋሲል አሻግሮ የኤልሳን ፊት መለዋወጥና የአይኗን ማጉረጥረጥ በጎሪጥ ከሩቁ አያትና ,ጀርባውን ሰጣትና አጠገቡ ወዳለችው ሳባ ዞሮ ስሯ በመንበርከክ

‹‹የእኔ ፍቅር ታገቢኛለሽ …?መልስሽን  በጉጉት  እየጠበቅኩ  ነው?››በማለት ለሁለተኛ ጊዜ ጥያቄውን አቀረበላት ፡፡እምቢ ብትለው የጓደኞቹ  እና  የኤልሳ መሳቂያ ሆኖ እንደሚከርም ሲታሰበው ውስጡ ቀዘቀዘበት፡፡
በተቃራኒው ሳባ የጠረጠረችው  ነገር  በመሆኑ  እንደመተከዝ  አለች..አሁን ጥያቄውን መቀበል አለባት.. በምንም አይነት እነዚህ ሁሉ ሰዎች መካከል እምቢ ብላው አጉል ትኩረት መሳብ አልፈለገችም፡፡በምንም አይነት ሁኔታ ግን ግንኙነታቸው ከሳምንት በላይ እድሜ እንደማይኖረው ሙሉ በሙሉ እርግጠኛ ሆነች፡፡ሀለቃዋ ስለእዚህ ፍቅረኛዋ ከሰማችበት ቀን አንስቶ ይቅርብሽ እያለች

ስታስጠነቅቃት ነበር፡፡የልጁ ፍላጎት የወሲብ ስሜቷ ላይ ብቻ ተገድቦ እዛ ላይ እንዳማይገታ ደጋግማ ነግራታለች፡፡
#ኢትዬጵያዊቷ_ሰላይ
( በአመዞን ደን ውስጥ)


#ክፍል_ሶስት


#በዘሪሁን_ገመቹ_ዋቤ

ሁለት ሰዓት ሲሆን ወደመኝታቸው ተመልሰው ገቡ፡፡
‹‹እንግዲያው መተኛት እንችላለን..››አለችና ሙሉ በሙሉ አልጋው ላይ ወጣች፡፡ የአልጋው ጠርዝ ላይ እንደተቀመጠ ‹‹አይ ግን እንቅልፌ አልመጣም››አላት፡፡
‹‹እንደዛ ከሆነ እኔም እንቅልፌ አልመጣም…››አለችና መልሳ ከአልጋው ወረደችና ‹‹ቆይ የሚጠጣ ነገር ትፈልጋህ?››ስትል ሌላ ጥያቄ ጠየቀችው፡፡
‹‹የሚጠጣ ..እኔ እንጃ ?››ነበር መልሱ
ዝም አለችና ክፍል ውስጥ ወዳለው ፍሪጅ ተንቀሳቀሰች ፤ከፈተችው…..፡፡ሁለት በቆርቆሮ የታሸጉ የአልኮል መጠጦች አወጣችና ወደ እሱ ተመልሳ ከጎኑ ተቀመጠች…አንዱን አቀበለችው፡፡ከፈተችና ተጎነጨችለት ….እንዳደረገችው አደረገ…አልተመቸውም ፤ ግሽግሽ አለ፡፡
‹‹ምነው? አልኮል ጠጥተህ አታውቅም እንዴ?››

‹‹እንግዲህ አላውቅም ማለት ነዋ…ባውቅ እንዲህ ግሽግሽ አይለኝም ነበር?››ሲል መለሰላት፡፡

‹‹ምን አድርገሀቸው ይሆን እንዲህ ትናንትህን ከአእምሮህ እጥብ ያደረጉት? ›› ስትል በውስጧ ስለእሱ አሰበች፡፡የሰላይነት ህይወቷ ሰው በሰው ላይ ብዙ ነገር እንደሚደረግና የሰው ልጅ በገዛ ስህተቱ ሆነ በማያውቀው እና በማይመለከተው ምክንያት ብዙ መከራና ስቃይ ሊደርስበትና ህይወቱን እስከማጣት የሚያደርስ መከራ እንደሚያጋጥም በተግባር ደጋግሞ አሳይቷታል፡፡ይህ ፊት ለፊቷ የተቀመጠው ሰውዬ ግን በህይወት እያለ ህይወቱን ያጣ ሆኖ ነው ያገኘችው…ይሄ ደግሞ ነፍስን እስከወዲያኛው ከማጣትም የከፋ ነው፡፡እንዲህ አይነቱ ግራ የገባው ነገር የመጀመሪያ ጊዜ ገጠመኟ ነው፡፡ለዛውም ጥሩ ነገር ብቻ አይበታለው ብላ በመጣችበት በባአድ ሀገር ፡፡ ድንገታዊ ሀሳብ በአእምሮዋ ብልጭ አለባት፡፡
‹‹ግን እንዴት ስልክ ሳይኖርህ?››ስትል ጠየቀችው፡፡

‹‹እኔ እንጃ ምን አልባት ጥዬው ሊሆን ይችላል?››

‹‹ሊሆን ይችላል ..ሞባይልህ ኖሮ ቢሆን ኖሮ የተደዋወልካቸውን ቁጥሮች እዛ ላይ ተመዝግቦ ስለምናገኘ ደውለን የሚያውቁህን ሰዎች ወይም ቤተሰቦችህን በቀላሉ ማግኘት እንችል ነበር፡፡››
‹‹እና አሁን ማንነቴን ለማወቅ ምንም ተስፋ የለኝም ማለት ነው?››

‹‹አይ እንደዛማ እንዴት ይሆናል..?አይዞህ ብራዚል እስክንደርስ ምንም ትዝ የሚልህ ነገር ከሌለ ሀኪም እንዲያይህ ማድረግ እችላለሁ… ያንቀላፋውን የማስታወስ ችሎታህን የሚቀሰቅስ የሆነ መድሀኒት አያጡም፡፡››
‹‹ለምን ግን እንዲህ ደግ ሆንሺልኝ?››ሲል ያልጠበቀችውን ጥያቄ ጠየቃት፡፡

‹‹የሰው ልጅ ስለሆንኩ ነዋ…አንተም እኮ እኔን በዚህ ሁኔታ ላይ አግኝተኸኝ ቢሆን ከዚህ በላይ የሆነ ነገር ነው የምታደርግልኝ…እንዴ ላፕቶፕህ?››ስትል ወደእሱ አፍጥጣ ጮኸች፡፡
በመብረቃዊ ንግግሯ ተገርሞ ‹‹ላፕቶፑ ምን?››ሲል ጠየቃት፡፡
‹‹ማወቅ የምትፈልጋው.. ማለት ስለማንነትህ የሚያወሩ መረጃዎች ላፕቶፕህ ውስጥ ሊገኙ ይችላሉ..አዎ እርግጠኛ ነኝ የሆነ ነገር ይገኛል፡፡››
ከተቀመጠበት ተነሳና ለፕቶፑን በማንሳት ሄዶ ከጎኗ ተቀመጠ ፡፡‹‹እንዴት ነው የሚከፈተው?›› ጠየቃት፡፡ተቀበለችውና በቀይ ቀለም የደመቀውን በተን ተጫነችው፡፡ ጥቁር የነበረው የላፕቶፕ አስክሪን ቀስ እያለ በራ….ፓስወርድ ይጠይቃል፡፡
‹‹ወይኔ ፓስወርድህን መቼስ አታስታውስም…..?ስምህን የረሳህ ሰው ፓስወርድህን እንዴት ልታስታውስ ትችላለህ?››
‹‹ቆይ እስኪ›› አለና ተቀበላት… ዝም ብሎ በደመነፍስ በሚመስል ሁኔታ የተወሰኑ ፊደሎቹንና ቁጥሮችን ሲጫን ኮምፒተሩ ተከፈተ፡፡
በደስታ እየተፍለቀለቀች‹‹ከፈትከው….ፓስወርዱን አስታውሰህ ነው ?››ጠየቀችው፡፡
‹‹አይ ..ዝም ብዬ ነበር የነካካሁት፡፡››

‹‹ግድ የለም ..ዋናው መከፈቱ ነው፡፡››

ፎልደሮችን እየከፈቱ ማየት ጀመሩ፡፡የሚገርምና ጭራሽ ግራ ሚያጋባ ፍይልነው እየተመለከቱ ያሉት፡፡ጥቅጥቅ የአማዞን ደን….ጥቅጥቅ ደን ውስጥ የታነፁ ቢላ ቢቶች…አስፈሪ መሳሪያ  የታጠቁ አውሬ መሳይ ሽፍቶች ….…. ብዛት ያላቸው ሰዎች የሚተረማምሱባቸው ነጭ ለባሽ ሰዎች የሞሉባቸው ላባራቶሪ፡፡
‹‹ቆይ ቆይ እስቲ አቁመው…››
  አቆመው..
‹‹ወደ ኃላ ትንሽ መልሰው››ሌላ ትእዛዝ፡፡
‹‹ይሄ አየኸው እራስህ ነህ፡፡ሳይንቲስት ነህ፡፡እዛ ጥቅጥቅ የአማዞን ደን ውስጥ በሚገኝ ላባራቶሪ ውስጥ ከአነዛ አደገኛ መሳሪያ የታጠቁ አስፈሪ ሰዎች ጋር አብረህ የምትሰራ ሳይንቲስት ነህ፡፡››
እንደዛ ትበል እንጂ እዚህ ስሯ ቁጭ ብሎ ማንነቱን ማወቅ እንኳን አቅቶት ልክ እንደደነበረ አውሬ መግቢያ አጥቶ የሚቁለጨለጨውን ሚስኪንና አሳዛኝ ሰው ከሽፍቶችና ገዳዬች ጋር አገናኝቶ ማሰብ ምንም ሊዋጥላት አልቻለም…ቢሆንም በህይወት አይሆንም ተብሎ ድምዳሜ ሚደረስባቸው ነገሮች በኃላ ሆነው ሲገኙ ብዙ ጊዜ ስለታዘበች የሚሆነውን ለማየት ወሰነች፡፡
‹‹ምንድነው የምሰራው….?››ጠየቃት፡፡
‹‹እኔ እንጃ…እስቲ ማጫወቱን ቀጥል፡፡››

እንዳለችው አደረገ፡፡ሀሺሽ ፕሮሰስ ሲደረግ …በየአንድ ኪሎ እተጠቀለለ ሲታሸግ ..ሌላ ቦታ ደግሞ በኪኒን መልክ ሲዘጋጅ…..ብዙ ብዙ ነገር ይታያል፡፡
‹‹አንተ ምንድነው ይሄ ጉድ….?››ሰውነቷ ሁሉ ይንቀጠቀጥባት ጀመር…በጣም ፈራችው፡፡
‹‹እንዴት ግን እዛ ልገኝ ቻልኩ…?.ምን አልባት አስገድደውኝ ይሆን?ማለት በመሳሪያ አስፈራርተውኝና አግተውኝ፡፡››
አሰበች‹‹ምን አልባት ሊሆን ይችላል..ግን እንደዛ ከሆነ ፔሩ ሊማ ምን ስትሰራ ነበር…?እዛ ፕሌን ውስጥ እንዴት ልትገባ ቻልክ…?እንዴት አንድ ጠባቂ እንኳን ሳይኖርህ? ወደብራዚሊያስ ምን ለትሰራ ነው የምትሄደው?እንዴት ሁሉን ነገር ልትረሳ ቻልክ?››ጥያቄዎችን አዣጎደጎደችበት፡፡
‹‹ለዚህ ሁሉ ጥያቄዎችሽ መልስ ኖሮኝ ብመልስልሽ በጣም ደስ ይለኝ ነበር፡፡››አለና ላፕቶፑን ከጎኑ አስቀምጦ ተነሳ ……ወደቦርሳው ሄደና ከወለል ላይ አንስቶ አልጋው ላይ አስቀመጠው፡፡ ከዛ ከፈተው…ከላይ ጀኬት አለው…አወጣና አስቀመጠው፡፡ከዛ የተወሰኑ መፅሀፎች አሉበት
..ከዛ ..ከዛ የሚያስደነግጥ ነገር ነው…ሙሉ ዶላር ነው፡፡››

በድንጋጤና በመገረም አፏን ከፍታ ‹‹አንተ ይሄ ሁሉ ብር ምንድነው?››ስትል ጠየቀችው፡፡
‹‹እኔ እንጃ?››

‹‹አንተ ከእኔ እንጃ በስተቀር ሌላ መልስ የለህም እንዴ?››በብስጭት አፈጠጠችበት፡፡
‹‹እኔ እንጃ …የለኝም መሰለኝ፡፡››

‹‹ቆይ እስኪ ሌላ ነገር የለውም.?.››አለችና የኪሱን ዚፕ ከፈተች፡፡ውስጡን ፈተሸች፡፡በትናንሽ ላስቲኮች የታሸገ ነጭ ዱቄት፡፡አወጣችና አልጋው ላይ ዘረገፈችው፡፡‹‹አየህ..ይሄን ሁሉ ኮኬይን..እንዴት ፕሌን ውስጥ ይዘህ ገባህ…?እንዴት ፍተሻውን አለፍክ..?አንተ ማን ነህ….?ይመስላኛል አንተ እዛ ላባራቶሪ ውስጥ ታግተህ ሳይሆን እራስህ በፍቃደኝነት የእነሱ አንድ አባል ወይም ቅጥረኛ ሆነህ እየሰራህ ያለህ ሰው ነህ ..የዛ የኮኬይን ማምረቻና ማቀነባበሪያ ላብ ውስጥ ወሳኙ ሰውም ልትሆን ትችላለህ …ወደሊማ ወጣ ያልከው ምን አልባት ዘና ልትልና ከከተማዋ ቆነጃጅቶች ጋር ልትዝናና ፈልገህ ሊሆን ይችላል…፡፡ምን አልባትም ደግሞ ከተረካቢዎችህ ጋር የስራ ድርድር ለማድረግም ወክለውህም ሊሆን ይችላል፡፡አሁን ስራህን ጨርሰህ ወይም ተልኮህን አጠናቀህ ወደ ምሽግህ እየተመለስክ ሊሆን ይችላል፡፡ወደብራዚል እየተጓዝክ ያለህበት ዋናው ምክንያት ምን አልባት ይሄ ላባራቶሪህና ምሽጋችሁ የሚገኘው የብራዚል ጥቅጥቅ ደን ውስጥ ሰለሆነም ሊሆን
#ጉዞ_በፀሎት
(አቃቂ እና ቦሌ)


#ክፍል_ሶስት


#በዘሪሁን_ገመቹ_ዋቤ
፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧

በፀሎት የልብ ንቅለ ተከላ ካደረገች በኋላ ልክ እንደዛሬው አይነት በህይወቷ ወሳኝ የሆኑ ትላልቅ ውሳኔዎችን አሳልፋለች….አንዳንዴ‹‹ በእውነት እንዲህ እያሰብኩና እያደረኩ ያለሁት እኔው ነኝ?››ብላ በራሷ እስክትደመም ድረስ ነበር ለውጦ፡፡

‹‹አሁን የሌላ ሰው ለዛውም የሟች ንፁህ ልብን በሰውነቴ ተሸክሜ ርካሽ የሆነ ስራ ፈፅሞ አልሰራም››የሚል አቋም ላይ ደርሳ በዛ መሰረት ነው የምትንቀሳቀሰው…ትንሽ ለስሜቷ የማይመችና የሚቆረቁር ነገር ሲያጋጥማት እንደድሮው ‹‹ቆይ እስኪ ልሞክረው›› ብላ ዘላ አትገባበትም….ጊዜ ወስዳና ተረጋግታ ታስብበታለች..ነገሩን ትመዝንና እሷንም ሆነ ሌላውን ሰው የሚያሳዝንና የሚያስከፋ መስሎ ከተሰማት ወዲያው መንገዷን ታስተካክላለች….ይሄ በብዙ ነገሮች ጠቅሟታል…ግን ደግሞ ቤተሰቦቾን በተመለከተ እንደበፊቱ ነገሮችን አይታ እንዳላየች እንድታልፍ አላደረጋትም…እያንዳንዱ በመሀከላቸው ያለው ጥላቻና ጥል በጣም ያስጨንቃትና እረፍት ይነሳት ጀመር…ለምን ብላ እንድትጠይቅ..ጥፋቱ የማንኛቸው ይሆን እያለች እንድትመረምርና ፣እንዴት ሊስማሙና ትክክለኛ ባልና ሚስት ሆነው ለእሷም መቼ እንደ ትክክለኛ ወላጅ የምትፈልገውን ፍቅር ሊለግሷት እንደሚችሉ ማለምና መተከዝ የጀመረችው ከበርካታ ወራቶች በፊት ነው፡፡

በፀሎት  ጨረቃ በነገሰችበትና ከዋክብቷች ሰማዩ ላይ ተበትነው በሚንሸራሸሩበት በዛ ውድቅት ለሊት እቤቷን ጥላ ..ከእናትና አባቷ ርቃ …ከጋደርዶቾ አምልጣ መሄዷን እንጂ ወዴት እንደምትሄድ ለምን ያህል ሰዓት መንዳት እንዳለባትና የመንገዷ ማዳረሻ የት እንደሆነ ምንም የምታውቀው ነገር የለም፡፡ዝም ብላ ብቻ በዛ ውድቅት ለሊት የአስፓልቱን መሀከል ይዛ በመድሀንያለም ቤተክርስቲያንን አጠር ታኮ በሚገኘው መንገድ ወደፊት በመውጣት ዋናውን አስፓልት ገባችና ቀጥታ ወደ ስቴዲዬም ሚወስደውን መንገድ ያዘች….መስቀል አደባባዩን እንደጨረሰች ወደግራ ታጠፈችና ወደላንቻ የሚወስደውን የአስፓልት መንገድ ያዘች..
ከትራፊክ መጨናነቅ ነፃ የሆነውን መንገድ በፍጥነት መጋለብን ተያያዘችው…ምንም ሳታውቀው ለአንድ ሰዓት ያህል ከነዳች በኃላ አቃቂ ድልድይ ጋር ስትደርስ ወደቀኝ ተጠማዘዘችና ወደአቃቂ የሚወስደውን መንገድ ገባች ፣…መንዳቷን ቀጠለች…ድንገት ተረጋጋችና ሞተሩን አቀዝቅዛ አቆመችና አካባቢውን ስታስተውል የምታውቀው ሰፈር ሆኖ በማግኘቷ ደነገጠችም.. ተገረመችም….እዚህ ሰፈርና እዚህ ቦታ ለመምጣት ባለፈው ሁለት አመት ስትመኝ ነበር….ቢያንስ በሳምንት አንድ ቀን በህልሟ እዚህ አካባቢ መጥታ ስትዳክር ነው የምታየው..ግን መጥታ የምትፈልገውን ነገር ለማድረግ አባቷ ሊፈቅድላት አልቻለም..ለጠባቂዎችም በጥብቅ ስለተነገራቸው እንኳን አሁን ያለችበት ሰፈር ይቅርና ክፍለከተማው ውስጥም ዝር እንድትል እንዳይፈቅዱላትም ፤ከዚህ ቀደም ምንአልባትም ከአመት በፊት ሰፈሩንና እቤቱን ለአንድ ጊዜ በስንት ጭቅጭቅ ያሳያት እራሱ አባቷ ነበር፡፡

በጊዜው መኪናዋን አሁን ሞተሯን ያቆመችበትን ቦታ አቁሞ…የቤቱን በራፍ በጥቁሩ የመኪና መስታወት ወደውጭ እየጠቆመ…‹‹አየሽ የልጅቷ ቤተሰቦች የሚኖሩት እዚህ ነው..እኛ አሁን የሚገቡት አባቷ ናቸው…አብሯቸው ያለው ደግሞ ልጃቸው ነው….እናትና እህቷም አሉ››እያለ ነበር ያብራራላት፡፡

‹‹አባዬ እንዲት እንዲህ ጭንቁርቁስ ያለ ቤት እንዲኖሩ ትፈቅዳለህ..?እየው እስኪ አጥሩን..እቤታቸውን ተመልከተው››በምሬት አባቷን መጠየቋን ታስታውሳለች፡፡

‹‹ልጄ ምን ላድርግ ?በግድ በወታደር አስገድጄ ሌላ ቤት ውስጥ እንዲገቡ ማድረግ አልችል››

‹‹ማለት…?››

‹‹ነግሬሻለሁ እኮ …ቤተሰቡ ከእኛ አምስት ሳንቲምእንደማይቀበሉ ምለው ነው የነገሩን››

‹‹አባዬ ይሄ ምንም ሊገባኝ አልቻለም…የተሸከምኩት እኮ የልጃቸውን ልብ ነው….በልጃቸው ሞት እኮ ነው አሁን እኔ በህይወት መኖር የቻልኩት…አልገባህም አባዬ …ለምን እሷ ሞታ እኔ ኖርኩ..?እግዚያብሄር ይሄን እንዴት ፈቀደ…?.አባዬ በየቀኑ የጥፋተኝነት ስሜት እየተሰማኝ ነው…እየተሰቃየሁልህ ነው…››

‹‹አውቃለው  ልጄ…እነሱ  ፍቃደኛ  ቢሆኑ  እኔ  የሀብቴን  ግማሽ  እንኳን  ብሰጣቸውና
..ላደረጉልኝ ነገር ምስጋና ባቀርብ ደስ ይለኝ ነበር…ግን ተቀባይ ከሌላ መስጠት ስለፈለግሽ ብቻ አይሳካልሽም፡፡››

‹‹ቢሆንም አባ ..እኔ ልቧን ሰጥታኝ ህይወቴን እንዲራዘም ያደረገቺኝን ልጅ ቤተሰቦች እንዲህ በጉስቁልና እንዲኖሩ አልፈልግም…..ልጃቸው በህይወት ኖራ ቢሆን ትጦራቸው ነበር…የሆነ የሆነ ነገር ታደርግላቸው ነበር….ብቻ አላውቅም የሆነ ዘዴ ፍጠርና እርዳቸው፡፡››

‹‹አይ ልጄ አልገባሽም እንዴ…ልጃቸው ላንቺ ልብ ከመስጠቷ ከአመታት በፊት በእኛ ፋብሪካ የሚሰራውን ወንድ ልጃቸውን እራሱ ስራ እንዲለቅ አድርገውታል…..ለማንኛውም የተቻለኝን እሞክራለው..አሁን ይሄን ያህል ካየሻቸው ይበቃሻል… አንሂዱ ››ብሎ ነበር ከአካባቢው ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ የለቀቁት፡፡

ከዛ ወዲህ ግን ፍፅም ወደአካባቢው እንድትጠጋና ከቤተሰቡ ጋርም በምንም አይነት መንገድ ተገኛኝታ እንዳትተዋወቅ ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ተሳክቶላቸዋል…አሁን ግን ይሄው በደመ ነፍሷ ከቤቱ ፊት ለፊት አስፓልቱ ጠርዝ ላይ ሞተሯን አቁማ ቁልቁል አዘቅዝቃ እያየችው ነው፡፡

‹‹ወደእዚህ መምጣት በአእምሮዬ ስሌት ውስጥ አልነበረም….ሳስበው ግን የልጃችሁ ልብ ነው እየመራ እዚህ ድረስ ያመጣኝ››ስትል አጉረመረመች፡፡ድንገት ስሜታዊ ሆነችና ነዳጁን ረገጠችና ጨምቃ የያዘዘችውን ፍሬን ለቀቀች…አስፓልቱ ን ለቃ ቀጥታ ወደቤቱ አቅጣጫ መንዳት ጀመረች

…የሞተሩ ፍሬን ድንገት እምቢ አላት… ያ ደግሞ ጠቅላላ ሰውነቷ በፍራቻ እንዲቀዘቅዝ ነው ያደረጋት…ሞተሩ ከቁጥጥሯ ውጭ እየወጣ ነው.. መንገድን ሰታ ወደቀኝ እየተጓዘች ነው…›የተውሸለሸለ የእንጨት አጥር ቤት ጥሳ ገባች…. የቆርቆሮ በር ካለው ሰርቢስ ቤት በራፍ ጋር ተላትማ በአየር ላይ ተንሳፈፈችና መሬት ላይ ጧ…ጧጧ ብላ ወደቀች....ሞተሩ አጥሩን ጥሶ ሲገባና ከቆርቆሮ በራፉ ሲጋጭ የፈጠረው ድምፅ የፍንዳታ አይነት ነው….እሷ ወዲያው ነው ጭልም እያለባት የሄደው…እንዲህ ባለ ሁኔታ እራሷን አደጋ ላይ የመጣል እቅድ አልነበራትም…….ከቤት ውስጥ ግን ቡዙ ጫጫታና ትርምስ ተሰማ…

‹‹አማዬ ምንድነው……?››

‹‹.ልጆቼን ..››

‹‹ልጆቼን ››

‹‹አባዬ ሰላም ነህ?››

የሶስት ወይም የአምስት ሰዎች ድምጽ እየተሰማት ነው….እያንዳንዱ ድምፃ ልቧ ላይ እየተንጠባጠ እያቀለጣት ያለ ነው የመሰላት፡፡‹‹ምን ሆኜ ነው …?ምን ተፈጠረ…?ይሄን እያሰበች ሳለ ጭልም እያለባት ሄደ ፣እንደምንም ላለመጥፋት ብትሞክርም አልቻለችም
…እራሷን ሙሉ በሙሉ ሳተች….፡፡እቤቱ ውስጥ ያለ አንድ ጎረምሳ እና አንድ ወጣት ሴት… እናት አባት በዛ ውድቅት ለሊት ፈጣሪ ምን አይነት መብረቅ እንደላከባቸው ለማወቅ በሀይለኛ ድንጋጤ እንደተመቱ የተተራማመሱ የቤታቸውን በራፍ እንደምንም ተራ በተራ እየተጋፉ ወደውጭ ወጡ….የውጭ መብራት አብርተው ሲመለከቱ ..ከበራፉ በሶስት ሜትር ርቀት መሬት ላይ የተዘረጋ ጥቁር እና ነጭ ቀለም የተቀባ ዘመናዊ ሞተር ሳይክል
ይታያል...ከሳይክሉ ሁለት ሜትር ርቀት አንድ ሄሌሜት ያደረገ ባለመካከለኛ ቁመት ሰው እጥፍጥፍ ብሎ ወድቆ ይታያል....ሁሉም በቃል ሰይነጋገሩ እየሮጡ ሰውዬውን ከበቡት…
#ወይ_አጋጣሚ(አጭር ልብወለድ)


#ክፍል_ሶስት


#ድርሰት_በዘሪሁን

====================
‹‹ካሰብሽበት አሁንም ቀን ነው፡፡››
‹‹አንተ ቤተሰብ ያለኝ ሰው እኮ ነኝ፡፡››
‹‹አንቺ እሺ ይኑርሽ.. ያደነዘዘኝን ቂጥሽን ግን ላኪልኝ፡፡››መቼስ የምላሴ ፍሬኔ ብጥስጥስ ብሎብኛል፡፡
‹‹ናና ውሰደዋ፡፡››
‹‹በቃ መጣሁ፡፡››
‹‹እውነትህን ነው?››
‹‹አዎ እውነቴን ነው..ትናንት የተለያየንበት ቦታ ስደርስ ደውልልሻለሁ››
‹‹ያ እኮ ሰፈሬ አይደለም ብላ …የእሷን ትክክለኛ ሰፈር በምልክት ነገረችኝ.. ሂሳብ እንዴት እንደከፈልኩ.. እንዴት ተንደርድሬ ሰፈሯ እንደደረስኩ አላውቅም..ግን ስደውልላት ባሏ ተከትሏት ቢወጣስ..?የራሱ ጉዳይ ‹‹የቆመበት የቆመ ነገር አያይም››ይባል የለ፡፡ ደወልኩላት… ከአምስት ደቂቃ በኃላ መጣች፡፡ጨለማ ውስጥ ሆኜ ያለሁበትን ቦታ በእጅ ምልክት ጠቆምኳት..መጣች፡፡
‹‹አንተ ጉደኛ!!!››
በቃላት መልስ ከመመለሴ በፊት ጐተትኩና ከሰውነቴ አጣብቄያት ከንፈሯን ገመጥኳት ፡፡የሀይሚን እልክ በእሷ እየተወጣሁ ያለው መሰለኝ፤ በግድ ነው ያስለቀቀቺኝ‹‹አንተ ሰፈሬ እኮ ነው ያለሁት…ሰው ቢያየኝስ?››አለችኝ፡፡ ንግግሯ ደስ አሰኘኝ…ሰፈሯ ባይሆን ኖሮ በመሳሟ ደስተኛ ነች ማለት ነው፡፡
‹‹ባክሽ ጭለማ ውስጥ ነው ያለነው..ማንም አያይሽም፡፡››
‹‹ወይኔ ጉዴ!!!››አለች ድንገት ራሷን ይዛ እየተርበተበተች፡፡
‹‹ምነው….?ምን ሆንሽ…?›.
‹‹ባሌ መጣ …ባሌ፡፡››
በድንጋጤ ተሸቀንጥሬ ጨለማ ውስጥ ተሸገጥኩ፤እሷ በቆመችበት ሆና በሳቅ ፍርስ አለች‹‹ሲያዩህ ጀግና ትመስላለህ››
ከተወሸቅኩበት ወጣሁና ወደ እሷ በእርጋታ እየቀረብኩ ‹‹ጀግናማ ጀግና ነኝ ላንቺ ደህንነት አስቤ አስጂ..፡፡››
‹‹እሱን እንኳን ተወው..ጀግና አናውቅም እንዴ?››
‹‹ግን ባልሽ እቤት ነው?››
‹‹ባሌ እቤት ቢኖር..እንዲህ አጥር ስር አስደግፌህ አዋራሀለው፡፡››
‹‹ጥሩ አጋጣሚ ነው ፊልድ ሄዶል ማለት ነው››..አንገቷን ወደ መሬት ደፍታ ዝም አለች፡፡ግራ ገባኝ‹‹ምነው ያልኩሽን ሰምተሸል?››
‹‹አዎ ባሌ የሞተብኝ በቅርብ ነው፡፡ ሰሞኑን ነው ጥቁሩን የሀዘን ልብሴን ያወለቅኩት ››ደነገጥኩ፡፡የተደፈነ ልብ ሸሽቼ ስመጣ የተሸነቆረ ልብ ገጠመኝ እንዴ..?
‹‹ይቅርታ›› ብዬ ዳግመኛ ወደ ሰውነቴ አጣበቅኳትና ከንፈሯ ላይ ተጣበቅኩ፡፡እጄ ትናንትና ያደነዘዘኝ ቂጦ ላይ አርፎል… ቃተተች፡፡ እንደምንም ተላቀቀቺኝና ‹‹እዚሁ ብትንትኔን አወጣኸው እኮ..በዛ ላይ ረሀብተኛ ነኝ፡፡››
‹‹እኔም ጠኔ ሊጥለኝ ትንሽ ነው የቀረኝ፡፡በቃ ይዘሺኝ ወደ ቤት ግቢያ..››
‹‹ወዴት?››
‹‹ወዳንቺ ቤት ነዋ፡፡››
‹‹እንዴ ልጄ እኮ አለች..በዛ ላይ ሰራተኛዋም….››
‹‹እሺ የሆነ ሰበብ ፍጠሪና ወደ እኔ ቤት ወይም ወደፈለግሽበት ሌላ  ቦታ ይዤሽ ልሂድ፡፡››
‹‹እሱማ አይቻልም..ውጭ ለማደር ምንም የምሰጠው ምክንያት የለኝም..ይልቅ ደፋር ከሆንክ አንድ ሀሳብ አለኝ፡፡››
‹‹ኸረ አፄ ቴዎድሮስ አጐቴ ነው… ጀግንነቱ ከደማችን ነው ሚንጠባጠበው፡፡››
‹‹ከ3-4 ሰዓት ባለው ጊዜ ይተኛሉ ..መኝታ ቤቴ ለብቻዬ ስለሆነ ስደውልልህ ትመጣና ትገባለህ..ታዲያ ለሊት 11 ሰዓት ወጥተህ ለመሄድ ከተስማማህ ነው ?››
ጥብቅ ብዬባት ሳምኳት እና ‹‹ቂጥሽ ብቻ ሳይሆን ልብሽም ቀይ ነው..ተስማምቼያለሁ፡፡››
‹‹ታዲያ እስከዛ የት ትቆያለህ?››
‹‹ችግር የለውም..ወደኃላ ተመልሼ በቅርብ የሚገኝ አንዱ ቡና ቤት አመሻለሁ… ስለ እሱ አታስቢ አንቺ ብቻ እንዳልሺው አድርጊ፡፡››
‹‹ችግር የለውም …አሁን ግን ሱቅ ዕቃ ልግዛ ብዬ ስለወጣሁ  መመለስ አለብኝ፡፡››
‹‹ታዲያ የገዛሽው ዕቃ የታል?››
‹‹አጣኋ…ባለሱቆቹ የለንም ጨርሰናል አሉኝ፡፡›› ብላ ጉንጬን በስሱ ስማኝ እየፈገገች ወደ ግቢዋ ተመልሳ ገባች፡፡››
አቤት የሰው ልጅ ልዩነት ድሮም ከህፃን ጋር መከራዬን ሳይ መኖሬ እንዲህ ትናንት ተዋውቆ ለዛሬ ብን ማለት እያለ ስድስት ወር ሙሉ  ስዳክር መኖሬ..አምኜ ወደ ኃላ ልመለስ አልቻልኩም፡፡እንዴ የሆነ ነገር ቢያጋጥመኝስ..? ድንገት ሳልሰማ ጉልበተኛው መንግስታችን ሰዓት እላፊ አውጆ ቢሆንስ…?ድንገት ዘራፊዎች ሞባይሌን ቢመነትፉኝስ በምን ደውዬ አገኛታለሁ…?ኸረ የሰይጣን ጆሮ ይደፈን እንጂ በእንደዚህ አይነቱ ቀን ድንገት የሚፈጠር ስንት አደናቃፊ ነገር አለ መሰላችሁ፡፡ለሀይሚ ተብዬዋ እንኳን ያን ሁሉ ሰዓት በባዷ አባክኜ የለ…ያደረግኩት አንድ ነገር ቢኖር እዛው ፊት ለፊቴ ካለች አንድ ትንሽ ኪወክስ ሄጄ ጭንብል መሸመት ነው፡፡ሶስት እሽግ ህይወት ትርስት..ሶስት እሽግ ሰንሴሽን ሸመትኩና በእያንዳንዱ ኪሴ ሁለት ሁለት በታትኜ ከተትኩ፡፡
አንድ ወንዳ ወንድ የሆነች የሱቁ ሻጭ‹‹ምነው የወር ቀለብ ነው እንዴ?›› አለቺኝ፡፡
‹‹ምነው ችግር አለው?››
‹‹ለምን ችግር የለውም ፡፡ ሆነ ብለህ ምርትን ከተገቢው በላይ በማከማቸት የዋጋ ንረት ለመፍጠር አስበህ ቢሆንስ?››
‹‹አይዞሽ አትስጊ ከተረፈኝ ጥዋት መልስልሻለው ›› አልኳት እና መልሼ ጨለማዬ ውስጥ ተወሸቅኩ፡፡3፤15 ሲሆን ተደወለ.. ባለቂጧ መስላኝ ተንደርድሬ አፈፍ አድርጌ አነሳሁና‹‹እሺ ተኙልሽ››
‹‹አዎ ልተኛ ነው››አለችኝ፡፡አቤት የደነገጥኩት ድንጋጤ.. ከራማዬ ነው ቡን ያለው፡፡ ሀይሚ ነበረች ደዋዮ፡፡አሁን በዚህ አሳሳች ሰዓት  ማን ደውይ አላት?
‹‹ሄሎ ምነው ዝም አልከኝ፤አኩርፈኸል እንዴ?››
‹‹አይ ለምን አኮርፍሻለሁ?››
‹‹ደግሞ ውጭ ነው እንዴ ያለኸው...፡፡ንፋስ ነገር ይሰማኛል›› ብላኝ ቁጭ፡፡ሁሉም ሴቶች ከጥንቆላ መንፈስ የተገነባ ስድስተኛ የስሜት ህዋሳት አላቸው…፡፡ይሄ ጉዳይ ሁሌ ይገርመኛል፡፡ከሆነች ሴት ጋር አፍ ለአፍ ገጥመህ ስታወራ…ወይንም የሆነች ሴት ልትስም አፍህን አሞጥሙጠህ ወደ ፊት መጓዝ ስትጀምር..ወይ ለአንዴ ልስረቅ ብለህ ሱሪህን በማውለቅ ላይ ሳለህ…ስልካቸው ጭርርርርርር ይልብህና ያሳቅቅሀል፡፡
‹‹ባክሽ ደብሮኝ እቤቴ በረንዳ ላይ ቁጭ ብዬ ከዋክብት እየቆጠርኩ ነው››
‹‹አውቄያለሁ ደብሮሀል ማለት ነው..?ግን ለቀኑ ነገር ተረድተኸኛል አይደል…?››ለዚህ ጥያቄዋ መልስ ከመመለሴ በፊት ሌላ ስልክ ዌይቲንግ ገባብኝ..ቂጣሟ ነች፡፡
‹‹በጣም ነው የተረዳሁሽ የእኔ ፍቅር፡፡አሁን ግን ሀለቃዬ እየደወለልኝ ነው..ላናግረውና መልሼ ደውልልሻለሁ፡፡››
‹‹አይ አያስፈልግም ፍቅር ..ልተኛ ስለሆነ ደህና እደር… ነገ ትደውልልኛለህ..ደግሞ አፈቅርሀለው እሺ፡፡››አለችኘ፡፡
‹‹እኔም አፈቅርሻለሁ፡፡›› አልኩና ዘጋሁት ..አያችሁልኝ አይደል፡፡‹‹አፈቅርሀለሁ፡፡››ብላኝ እኮ አታውቅም፡፡ሁልጊዜ ከስልክ ልውጥ  በኃላ ‹‹አፈቅርሻለሁ›› ስላት ‹‹እኔም›› ብላ ነው ምታሳርገው፡፡ ዛሬ ግን እኔን ለማሳቀቅ እና በአእምሮዬ ፀፀት ለመርጨት ሆነ ብላ አቅዳ እና አልማ ‹‹አፈቅርሀለሁ›› አለችኝ፡፡..ሞኟን ትፈልግ …በዚህ ሰዓት ለእሷ ንግግርም ሆነ ለአዕምሮዬ ፊት አልሰጣቸውም፡፡….
የቂጣሟን ስልክ አነሳውት…..‹‹ሄሎ››
‹‹ና በቃ … በራፍ ላይ ስትደርስ ደውልልኝ››
‹‹በመጀመሪያውስ ከበራፍሽ መች ተንቀሳቀስኩ››
‹‹እስከአሁን እዛው ነኝ እንዳትለኝ?››
‹‹አልኩሽ..ከስልክ እንጨቱ ጋር ተጣብቄልሻለሁ፡፡››
‹‹እውነትም ቀንዝሮብሀል..እሺ መጣሁ ››ብላ ስልኩን ዘጋች፡፡የውጩ በራፍ ተከፈተ፤ ጐትታ ወደ ውስጥ አስገባችና መልሳ ዘጋችው፡፡በግቢው ሆነ በቤታቸው ምንም አይነት መብራት አይታይም፡፡‹‹ምነው መብራ ተቆርጦባችሁ ነው?››በሹክሹክታ ጠየቅኳት፡፡
#የጣት_ቁስል


#ክፍል_ሶስት


#ድርሰት_በአብርሃም_ቃሉ

እድላዊት

ከወሰዳት የንቅልፍ ሸለብታ ነቃች፡፡ መኝታዋን ሳታነጥፍ ለምን እንደተኛች ግራ ተጋባች፡፡ የሆነውን እና የተፈጠረውን ነገር ሁሉ ለማስታወስ አንድ በአንድ ወደ ኋላ ተመልሳ በሃሳብ ነጎደች፡፡

የተነሳችበት ሰዓት ሳይነጋ እኩለ ለሊት ላይ ነው፡፡ ወዴት እንደምትሔድ ጨነቃት፡፡ ልቧ ሸፍቶ ጥፊ እያለ አስቸግሯታል፡፡ ለመጥፋት ወሰነች፡፡

መተኛቷን ትታ ቁጭ አለች፡፡ ወዴት እንደምትጠፋ እና ወዴት እንደምትሔድ አሰበች፡፡ ምን ይገጥመኝ ይሆን ? እንደገና ደግሞ ሃሳቧ እየተቀያየረባት ከምጠፋ ታንቄ ብሞት አይሻልም ? ሰርጌን ለመብላት ሲያደገድጉ በአቋራጭ ተስካሬን ይበሉ ነበር፡፡

ሃሳቧን እየቀያየረች ስታወጣና ስታወረድ ቆየች፡፡ አልሸነፍም ፤ አልረታም ፤ ለሞት እጄን አልሰጥም ብሎ የመጥፋት መንገድን የመረጠው ልቧ ሳይመለስ ቀረ፡፡ ሲገፋፋት ቆየ፡፡ ልቧ የመጥፋት መንገድን ማሸነፍ አልቻለም፡፡
ከሔደችበት የሃሳብ ሰመመን ተመለሰች፡፡ ሌሊቱ እየነጋጋ ነው፡፡ የታጠበውንም ፣ ያልታጠበውንም ልብሷን በፌስታል ሸከፈች፡፡ ቤተሰቦቿ ሳይሰሟት መውጣት እንዳለባት ወሰነች፡፡

መጥፋትን የወሰነችው እድላዊት መነሻዋን እንጅ መድረሻዋን አታውቅም፡፡ ጓዟን ጠቅልላ የእናት አባቷን ቤት እና የተወለደችበትን ቀዬ ለቃ ለመሄድ ተነሳች፡፡በሮቹን ድምፅ ሳታሰማ እና የተከፈቱ ሳታስመስል ግቢውን ለቃ ጨለማ በተቀላቀለበት ሌሊት ጉዞዋን አሃዱ አለች፡፡
ትንሽ እንደተጓዘች ጨለማው እየለቀቀና እየነጋጋ ሄደ፡፡ እለቱ እሁድ በመሆኑ በሩቅ ርቀት ላይ ሰዎች ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲሔዱ ተመለከተች፡፡ የምትጓዝበትን መንገድ ትታ ሰው ሳያያት ለመሔድ ፈለገች፡፡ አማራጭ መንገድ በጫካ ውስጥ መረጠች፡፡ የአካባቢው ሰው እንዳያያት የጫካውን መንገድ ይዛ መጓዝ የግድ ሆነባት፡፡

እድላዊት ከቤት ስትወጣ ከልብሷ በስተቀር የሚበላ ስንቅ አልያዘችም፡፡ በጉዞው አድካሚነትና አሰልችነት የተነሳ እራባት፡፡ ውሃም እየጠማት መጣ፡፡ ምግብ የበላችበትን ሰዓት አስታወሰች፡፡ ከትምህርት ቤት  ከወንድሟ ጋር ስትመጣ የቀመሰች ነው፡፡ እራትም ሳትበላ ነበር ያደረችው፡፡

ድካሟ እየባሰባት መጣ፡፡ አረፍ ለማለት በምትጓዝበት ጫካ ውስጥ ወደ ሚገኝ አንድ ትልቅ ዛፍ ስር ተቀመጠች፡፡ ውሃ ጥሙ ግን እየባሰባት ሄደ፡፡ ካረፈችበት ዛፍ ስር ተነሳች፡፡እየተጓዘች በአይኖቿ መንደር እና ውሃ በአካባቢው እያፈላለገች ፣ እየቃኘች ስትሔድ ጫካ ከመሆኑ አንፃር ውሃና መንደር የሚባል በቅርብ ልታገኝ አልቻለችም፡፡ ታዲያ ማፈላለጓን አላቋረጠችም፡፡ ከምትሄድበት መንገድ ባሻገር ከብቶች ሲሔዱ ተመለከተች፡፡

ከብቶቹ ወደ ውሃ እንደሚሄዱ ገመተች፡፡ የያዘችውን መንገድ ለቃ ከብቶቹ የሚጓዙበትን መንገድ በመያዝ ተከተለች፡፡

እውነትም የገመተችው ትክክል በመሆኑ ከብቶቹ ውሃ ሲጠጡ አገኘቻቸው፡፡

እድላዊት የጠማትን ውሃ ለመጠጣት ከብቶቹ ከሚጠጡበት ከፍ ብላ ልትጠጣ ተቀመጠች፡፡ የሚያንጎራጉር እና የፉጨት ድምፅ ሰማች፡፡ውሃውን ሳትጠጣ የሚያንጎራጉረውን የሰው ድምፅ ከየት አቅጣጫ እንደሆነ ለመለየት በአይኖቿ አማተረች፡፡
የእንጉርጉሮው ድምፅ እየቀረባት መጣ፡፡ ፍራት ፍራት ተሰማት፡፡ የዛሬን አውጣኝ ከዚህ ጫካ እያለች ፈጣሪዋን እየተማፀነች ፤ እየተርበተበተች አብዝታ ለመነች፡፡
የሚያንጎራጉረው የእንጉርጉሮው ድምፅ ከብቶች የሚያጠጡ እረኞች ነበሩ፡፡

እድላዊት እረኞቹን ፈራች፡፡ የመውጫዋን እና የማምለጫ መንገዷን ፈለገች፡፡

ከብቶቹን ከሚያጠጡት ሁለት እረኞች መካከል አንዱ ከበደ የሚባለው እረኛ እያንጎራጎረ ወደ ወንዙ ቀና አለ፡፡ አንድ የተቀመጠ ሰው ተመለከተ፡፡
ለጓደኛው ደበበ ያየውን ሰው ያ ማነው ? እዛ ላይ የተቀመጠው? አለ፡፡ ደበበ ጓደኛው እንዳለው ወደ ላይ ቀና ብሎ አየ፡፡ ቁጭ ያለ ሰው ተመለከተ፡፡

"ውሃ የሚጠጣ ሰው ይሆናል" አለው ለጓደኛው፡፡

እድላዊት እረኞች በእጃቸው እየተጠቋቆሙ ሲመለከቷት የባሰ ፈራች፡፡ በድንጋጤ እንደጠማት ልትጠጣ በእጇ የጨለፈችውን ውሃ እንኳን ሳትጠጣ ተነሳች፡፡ ቁጭ ብላ ከእረኞቹ ማምለጫ ስታማትር ወደ አገኘችው መውጫ መንገድ ተነስታ ለማምለጥ ሞከረች፡፡
እረኞቹ እድላዊትን ወንዝ ላይ ተቀምጣ ሰው ከመሆኗ ውጪ ወንድ ይሁን ሴት ትሁን አላወቋትም ነበር፡፡

እድላዊት ውሃ ለመጠጣት ከተቀመጠችበት ተነስታ ስትሮጥ ተመልክተው ሴት መሆኗን ለይዋት ፤ ከብቶቻቸውን ማጠጣታቸውን ትተው በእድላዊት መልክና ውበት እየተገረሙ በአይናቸው ተከትለው ሸኟት፡፡

አይን ለአይን እየተያዩ፡፡ የማነች ቀሽት ባክህ! ስታምር ፤ ከየት ይሆን የምትመጣው?

እውነትም ቀሽት ናት፡፡ ደግሞ እየፈራች ነው ፣ የምትሔደው፡፡ ምን ያገላምጣታል;

እረኞቹ እድላዊት ስትርበተበት አይተዋት ፤ ብቻዋንና የተከተላት ሰው አለመኖሩን ነቅተውባታል፡፡ይች ቀሽት ሳታመልጠን እንከተላት ተባባሉ፡፡ መጀመሪያ በአይናቸው ሸኝተዋት ቢመለሱም ልባቸው ግን ተከትሏት ነበር፡፡ እየተጣደፉ
እንዳታመልጣቸው በሔደችበት መንገድ ተከተሏት፡፡ እድላዊት የልቧ ትርታ ጨመረ፡፡ ሰውነቷ ሁሉ እየተንቀጠቀጠ፡፡ ትንፋሿ ቁርጥ ቁርጥ አለ፡፡ ይከተሉኝ ይሆን ብላ ተጠራጠረች፡፡ እንዴው አምላኬ
የዛሬን አውጣኝ፡፡ ከዚህ ከጨለማ፡፡ እያለች እንዳይደርሱባት በደከመ አቅሟ ለመሮጥ ሞከረች፡፡ ለእሷ የሮጠች መሰላት፡፡ ዳገቱ ግን ሊገፋላት አልቻለም፡፡ መልሶ ወደ መጣችበች ይገፈትራት ነበር፡፡ በአይኖቿ ወደ ኋላ፤ እየተመለሰች ብትገላመጥም የጠረጠረችው እና የፈራችው አልቀረም ፡፡ ባልጠበቀችው አቅጣጫ ሁለቱም እረኞች ከላይ እንደመጣ የመብረቅ ነበልባል ሆነው ደረሱባት፡፡

እድላዊት መሬት ተከፍታ ብትውጣት እንዴት በተደሰተች ነገር፡፡ ግን መሬት ተከፍታ ልትውጣት አልቻለችም፡፡ በድንጋጤ ሰውነቷ ተርበተበተ፡፡ ላብ በላብ ሆነች፡፡ እረኞቹ ግን የሚተዋትና የሚያዝኑላት አይመስሉም፡፡

ገና ሳይዟት ከነ ነብሷ የሚውጧት ነበር የሚመስሉት፡፡ አንበሳ አፍ ውስጥ እንደገባ ስጋ እንደሆነች ታወቃት፡፡

እረኞቹ ከመንገድ ላይ እጆቿን ይዘው ወደ ጫካ ጎተቷት፡፡ ማምለጥ አልቻለችም፡፡ ነብስ ዝም ብላ ከስጋ እስከ ምትለይ መፈራገጧን አተውም እና እድላዊትም እየጮኸች ባላት አቅም እየተፈራገጠች ጩኸቷን አባረቀችው፡፡

ዘመድና ወገን እንደሌላት መሬት ለመሬት ነብሱ እንደወጣ የአህያ እሬሳ ጎተቷት፡፡ ያ የሚያምረው ለግላጋና ማራኪ ውበቷ በደምና በአቧራ ተለወሰ፡፡
ከሴት ልጅ እንዳልተፈጠሩ እናትና ሴት እህት እንደሌለው ሰው ጭካኔ በተሞላበት አረመኔያዊ ድርጊት ለወሷት፡፡ መንገዱን አስለቅቀው ጫካው ውስጥም አስገቧት፡፡

እግዚአብሔር የእድላዊትን ስቃይና መከራዋን አይቶ ፤ የመማፀኒያ ልመናዋን ሰምቶ ፤ መላክተኛውን የሚካኤል አምሳያ ላከላት፡፡

አደን እንኳን ወጥቶ አያውቅም፡፡ አቶ አርምዴ የሚባል ሚንሻ፡፡ እድላዊት በአረመኔዎቹ እረኞች ተይዛ በምጮህበት በረሃ አካባቢ ነበር፡፡ አንድ አሳቻ ቦታ ተቀምጦ የሚያድነውን አውሬ እየፈለገ፡፡ በጫካው ውስጥ የሴት ልጅ ጩኸት ሰማ፡፡ ተነስቶ ወደ ጩኸቱ እሮጠ፡፡ ሁለት ልጆች እድላዊትን መሬት ለመሬት እየጎተቷት ደረሰ፡፡
#የድንግሊቷየ_አፍቃሪዎች


#ክፍል_ሶስት


#ድርሰት_ዘሪሁን_ገመቹ
===============

ላዳዋ ይዛቸው ትንሽ እንደተጓዘች

‹‹እሺ ምን ገጠመህ?››ሲል አለማየሁ  የመጀመሪያውን ጥያቄ ጠየቀ፡

አላዛርም‹‹ሰውዬው እየሞተ ነው መሰለኝ….፡፡››ሲል በደፈናው መለሰ፡፡

ሁሉም የአላዛር መልስ አልገባቸውም‹‹የትኛዬው ሰውዬ?››ሲል ሁሴን ጠየቀ፡፡

‹‹አባት ተብዬው፡፡››

‹‹በስመአብ..?ማን ነገረህ?››ሰሎሜ በድንጋጤ ጠየቀች፡፡

‹‹አንድ ሴትዬ ነች..ሚስቱ ነኝ አለችኝ..አላውቃትም፡፡››

‹‹ጋሽ ተሰማ አግብተዋል እንዴ?››ሁሉም በመገረም ጠየቁት..፡፡

‹‹እኔም ዛሬ ነው የሰማሁት፡፡››

‹‹አይዞህ አትደንግጥ ምንም አይሆኑም››ሰሎሜ ልታፅናናው ሞከረች፡፡

በንዴት በሚርገበገብ ድምፅ ‹‹ለምንድነው የምደነግጠው…? ቢሞት እንደውም ግልግል ነው፡፡››ሲል መለሰላቸው፡፡

‹‹ባክህ አታስመስል..ባትደነግጥ በዚህ ምሽት እኛንም ቀስቅሰህ ልታያቸው  ትሄድ ነበር?፡፡››
ሰሎሜ  ነች ተናጋሪው፡፡

‹‹አንቺን  አልቀሰቀስኩም..ብቻዬን  ከምሆን አሌክስን ብቻ ነው አካሂደኝ ያልኩት..አንቺና ሁሴንን አልጠየቅኳችሁም፡፡››

‹‹እና እናንተ ጓደኞቼ አይደላችሁም እያልከን ነው?››አለው ሁሴን በንዴት፡፡

‹‹አንተ ደግሞ ሁሌ ነገር ማጣመም ትወዳለህ፡፡››አላዛር ተበሳጨ፡፡

ሰሎሜ በድጋሜ‹‹ዝም ብለህ ስታስመስል ነው..ምንም ቢሆን አባትህ ናቸው፡፡››አለችው  ፡፡

‹‹ዝም በሉኝ በቃ… ሌላ ወሬ አውሩ››ተቆጣ ፀጥ አሉ…

አላዛር ሰፈሩን እንጂ ቤቱን እርግጠኛ አይደለም..ከአመት በፊት ነው አንድ ጓደኛው ጋር በዛ ሰፍር ሲያልፉ ‹‹የአባትህ ቤት ይሄ ነው›› ብሎ ያሳየው….በወቅቱ እቤቱን በጨረፋታ ተመልክቶ ከመገርም ውጭ  ለነገረው ልጅ  እንኳን መልስ አልመለሰለትም ነበር፡፡ግን እቤቱ እንደፈራው አልጠፋውም፡፡ሲደርሱ ከላዳዋ ወርደው ወደአጥሩ በራፍ እየሄዱ በተደወለለት ስልክ መልሶ ደወለ፡፡

‹‹ሄሎ አላዛር››ቀጭንና ልስልስ ድምፅ፡፡

‹‹መጥተናል በራፉን ክፈቺልን፡፡ ››

‹‹ክፍትነው ግፋውና ግባ፡፡››
እንዳለችው ገፋ ሲያደርገው ተከፈተ፡፡ሶስት ጓደኞቹን አስከትሎ አልፎ ወደውስጥ ሲገባ የሳሎኑ በራፍ ሲከፈት ተመለከተ.. በፍጥነት ተጠጉ..አንድ በእሱ እድሜ ያለች ገጠር ቀመስ ግን ደግሞ ውብ  ሴት እየተንቀጠቀጠች ትታያለች፡፡የአራቱም ዓይኖች በመላ አካሎ ላይ ተንከባለሉባት፡፡

‹‹የደወልሽልኝ አንቺ ነሽ?››

‹‹የአባቴ ሚስት አንቺ ነሽ ?››ብሎ መጠየቅ ነበር የፈለገው…..ምክንያቱም ይሄቺን የመሰለ ትንቡክቡክ ያለች ውብ ገራገር ወጣት ያንን ያበቃለትን የሰው አውሬ ብሎ የሚያስበውን  አባቱን እንዴት ታገባለች ብሎ ይገምት?››

‹‹አዎ ግቡ ግቡ ››በማለት ይዛቸው ወደውስጥ ገባች….እቤቱ ሳሎንና አንድ መኝታ ክፍል ያለው ባለሁለት ክፍል ነው፡፡አባትዬው ሳሎን ባለ አንድ አሮጌ ሶፋ ላይ ዝርግትግት ብሎ ትኝቷል፡፡ተጠጋውና በመጠየፍ አንገቱን ይዞ አወዛወዛው.. ለበድንነት የቀረበ ሁኔታ ላይ ነው ያለው፡፡
አለማየሁ‹‹ቶሎ ብለን ሀኪም ቤት እንውሰዳቸው››ብሎ ቀድሞ ሄደና ሰቅስቆ አቀፋቸው…ሁሴን የተንንዘላዘለ እግራቸውን በመደገፍ ሊያግዘው ሞከረ፡፡ሰሎሜ ተከተለችው…፡፡አላዛር ወደኃላ ቀረና

‹‹..አንቺ እዚሁ ጠብቂን…አይዞሽ ሰውዬው በቀላሉ የሚሞት አይነት ሰው አይደለም…አትጨናነቂ››አላት፡፡

የንግግሩ ይዘት አልገባትም፡፡ግራ በመጋባት አይኖቾን አቁለጨለጨችበት፡፡ ትከሻዋን በእጆቹ ቸብ..ቸብ እያደረገ‹‹አይዞሽ አትጨነቂ አልኩሽ እኮ…ያለውን ነገር እየደወልኩ አሳውቅሻለሁ፡፡ የሚያስተኙት ከሆነ  ጥዋት መጥቼ ወደተኛበት ሆስፒታል ወስድሻለው››ሲል ቃል ገባለት፡፡

ምርጫ ስላልነበራት
‹‹እሺ..አመሰግናለሁ..እግዜር ይስጥልኝ› ›ስትል መለሰችለት፡፡

አላዛር ፊቱን አዞረና ወጥቶ ሄደ..ጓደኞቹ አባትዬውን ላዳ ውስጥ አስገብተውት ነበር የጠበቁት….፡፡
አለማሁ ቀልቡ እዛ ቤት የቀረችው ወይዞሮ ላይ ተጣብቆ ስለቀረ ዝም ብሎ ላዳዋ ውስጥ ሊገባ አልቻለም፡፡

‹‹ እሷ አትመጣም እንዴ?››ሲል አላዛርን ጠየቀው…፡፡

‹‹ምን ትሰራላች ላዳዋ ለእኛም እኮ አትበቃንም፡፡››

‹‹አይ ድንጋጤ ላይ ስላለች ብቻዋን ትፈራለች ብዬ ነው፡፡››ለእሷ ይሄን ያህል ምን እንዳሳሰበው አያውቅም፡፡ግን ድንገት በጨረፍታ እንዳያት በዛው እስከወዲያኛው ሊረሳት አልፈለገም፡፡

አላዛርም ስጋቱ ተጋባበትና‹‹ለምን ከሶስታችሁ አንዳችሁ አብራችኋት አትሆኑም?››የሚል ሀሳብ አስከተለ፡፡ ሰሎሜን፤ ሁሴንንና አሌክስ እርስ በርስ ተያዩ…‹‹አንተ አብረሀት ሁን..ሁለት ሴት አብረን ከመፍራት ውጭ ምን እረዳታለው?ሁሴንም ቢሆን ወረቀት የሌለበት ቤት ያቃዠዋል››ስትል  ሰሎሜ  የራሷን ሀሳብ አቀረበች ፡፡

አለማየሁ በቀረበው ሀሳብ በመደሰት‹‹በቃ እሺ… እኔ አብሬት ሆናለው…ግን ያለውን ነገር በስልክ አሳውቁኝ፡፡››በማለት መስማማቱን አሳወቀ፡፡

አላዛርም‹‹አመሰግናለው አሌክሶ›› አለና ገቢና ገባ ፡፡ሰሎሜ ና ሁሴን ከኃላ  አባትዬውን ከግራና ቀኝ ደግፈው  ተቀመጡ… አሌክስ መልሶ ወደ ጊቢው ሲገባ ላዳዋ ተነቀሳቀሰች፡፡

አለማየሁ ወደጊቢ ገብቶ የሳሎኑን በር ሲቆረቁር…ወዲያው ብርግድ ተደርጎ ተከፈተ..ከበራፉ ጋር.. ያልጠና የወጣትነት ልቡም ነበር አብሮ የተበረገደው፡፡እሷ በራፉን ስትከፍት አላዛርን ነበር የጠበቀችው…ጓደኛው ሆኖ ስታገኘው ግን ግራተጋብታ

‹‹ምነው…ምን እረሳችሁ?››ስትል ጠየቀችው፡፡

‹‹አይ ምንም አረሳንም…ብቻሽን እንዳትሆኚ አብረሀት ሁን ብለውኝ ነው››

ነበር?››አለችው ከግራ መጋባቶ ሳትላቀቅ‹‹ውይ እኔ ምን ሆናለው ?እነሱን ብትረዳቸው አይሻልም፡፡

‹‹ሶስት እኮ ናቸው..እንደውም ከባለላዳው ጋር አራት ናቸው..እሱም  የሰፈር ልጅ ስሆነ ያግዛቸዋል፡፡››

‹‹ጥሩ እሺ ግባ››ብላ በራፉን ለቀቀችለት፡፡በዝግታ እርምጃ ገባና ፊት ለፊት ያለ አሮጌ ሶፋ ላይ ተቀመጠ፡፡እሷም በራፉን ዛጋችና ከእሱ በአምስት ሜትር ርቀት ላይ በሚገኝ ኩርሲ ላይ ጭብጥብጥ ብላ ተቀመጠች፡፡ለተወሰነ ደቂቃዎች ዝም ተባባሉ፡፡
ከገባችበት ሀሳብ እንደመባነን ብላ‹‹ወይኔ በእግዚያብሄር ዝም አልኩህ አይደል…?ሻይ ላፍላ ብና?››ስትል ጠየቀችው፡፡

‹‹አረ ችግር የለውም….ከቻልሽ ውሀ ስጪኝ››አላት

‹‹ እሺ››ብላ ወደውስጥ ገባችና ውሀ በብርጭቆ አምጥታ ሰጠችው….ተመልሳ ወደ ጓዲያ ገባችና የተጣጠፈ ጋቢ እየዘራጋች መጥታ ‹‹ብርድ ነው ትከሻህ ላይ ጣል አድርገው›› አለችውና አቀበለችው… ተቀበላትና ለበሰው፡፡

‹‹የአላዛር ጓደኛው ነህ?››

‹‹አዎ ጎረቤት ነን..አብረን ነው ያደግነው..ወንድም በይኝ››

‹‹እሳቸውንም ታቃቸዋለህ ማለት ነዋ?››

‹‹ጋሽ ተሰማን…አዎ ለእኔም አባቴ በያቸው፤ግን መቼ ነው የተጋባችሁት…?›ሲል የገረመውን ጥያቄ ጠየቃት፡

‹‹ብዙም አልቆየን… አንድ ሰባት ወር ቢሆነን ነው…፡፡››

‹‹ትዳር ታዲያ እንዴት ነው?፡፡››

እንደማፈር አለችና ተሸኮረመመች‹‹ችግር የማያደርግህ ነገር የለም፡፡የምደገፍበት ቤተሰብ የማኮርፍበት ዘመድ ስላልነበረኝ እሷቸው ላግባሽ ሲሉኝ እምቢ ማለት አልቻልኩም፡፡..ምንም እንኳን በእድሜ ከአባቴ ሚበልጡ ሰውዬ እንደሆኑ ባውቅም….አምላክ ከፈቀደው ምንም አይደል እንደአባት ይንከባከቡኛል እንደባል ያስደስቱኛል ብዬ እሺኝ አልኩና ገባሁበት፡፡የተደበቀ አመላቸው አፈትልኮ ለመውጣት ግን አንድ ወር እንኳን አልፈጀበትም…፡፡በቃ ትንሽ መጠጥ ከቀመሱ ሙሉ በሙሉ ሌላ ሰው ሳይሆን ሌላ አውሬ ነው የሚሆኑት፡፡ከዛሬ ነገ ይሻሻላሉ በማለት
#አላገባህም


#ክፍል_ሶስት


#ድርሰት_በዘሪሁን_ገመቹ


////
‹‹ቆይ ዘሚካኤል የት ነበር የጠፋው?፡፡››

‹‹እናቱና እህቱ የሞቱ ቀን ነው የተሰወረው፡፡ሁለቱ በመልክም ሆነ በአመካከት ፍጹም ተቃራኒ የሆኑት  ወንድማማቾች ከከተማ ተያይዘው ወደቤት ሲገቡ ..ሳሎኑ ፍፁም ትርምስምስ ብሎ ያያሉ ..ግራ በመጋባት  ወደውስጥ ዘልቀው ሲገቡ እናታቸው ልቧ ላይ ነጭ አብረቅራቂ ቢላዋ ተሰክቷባት ወለሉ ላይ ዝርግትግት ብላ ተኝታለች..አባትዬው ስሯ በደም በተጨማለቀው እጇቻቸው ጭንቅላታቸውን ይዘው ደንዝዘዋል….፡፡

‹‹እንዴ አባዬ ምንድነው..?እናቴን ምን አደረካት?›› ብለው ሲጮሁ ከፊት ለፊት  ኮርኒሱን ከደገፈው ብረት ላይ በታሰረ  ሲባጎ  አንገቷ የታነቀው እህታቸው በድኗ 360 ዲግሪ ሲሽከረከረከር ይመለከታሉ፡፡ሁለቱም ወንድማማቸች ወደእህትዬው እየሮጡና ሁለት እግሮቾን አንድ ላይ ይዘው ወደላይ ከፍ ያደርጎታል….‹‹ቶሎ በል ቢላዋ አምጣና ..ገመድን ቁረጥ…››
.ዘሚካኤል ይንደረደርና እናትዬው ደረት ላይ የተሰካውን ቢላዋ ይነቅልና ወንበር ላይ ቆሞ ገመዱን ይበጥሳል…እህትዬው ተዝለፍልፍ ሚካኤል ተከሻ ላይ ታርፋለች… ቀስ ብለው ወለል ላይ አሳርፈው በፍጥነት አንገቷ ላይ ያለውን ገመድ አላቀው ትንፋሿን ቢያዳምጡም በውስጧ የቀረ  ምንም  እንጥፍጣፊ እስትንፋስ አልነበረም….ከዛ ዘሚካኤል ቀጥታ እህቱ የተንጠለጠለችበትን ገመድ የቆረጠበትን እና እናቱ የተገደለችበትን ቢላዋ ይዞ ወደአባትዬው ሲንደረደር…ሚካኤል  በደመነፈስ ሮጠ ይጠመጥበታል…

‹‹ልቀቀኝ..እናቴንና እህቴን ገድሎ እሱ በህይወት አይኖርም››

‹‹አይሆንም….ስለሆነውን ምንም ምናውቀው ነገር የለም››ሲል ይመልስለታል፡፡

‹‹እንዴት አናውቅም..?አታይም እንዴ …?እጁ በደም ተጨማልቆ……ልቀቀኝ ልግደለው›› ሲል ይጋበዛል፡፡

‹‹አባቴንም ማጣት አልፈልግም››

‹‹እንግዲያው ሁለታችሁንም እገድላችኃለው…››ይለውና ድብድብ ይጀምራሉ…ይሄ ሁሉ ሲሆን አባትዬው ደንዝዘው ከተቀመጡበት  ቦታ ንቅንቅ አላሉም ነበር….ወንድማማቾቹ አባቴን ልግደል አትገድልም በሚል ጠብ እርስ በርሳቸው ተቦቅሰውና ተደባድበው ሳይለይላቸው ቤቱ በፖሊስ ይሞላል፡፡

አባትዬ እነሱ ከመድረሳቸው በፊት ስልክ ደውለው ሚስታቸውን  እንደገደሉ ነግሮቸው ነበር፡፡ፖሊሶቹ ወንድማማቾቹን አገላግለው ሶስቱንም ወደእስር ቤት ከወሰዷቸው በኃላ ሬሳዎቹን አንሰተው ለምርመራ ወደሆስፒታል ይልካሉ..በማግስቱ አባትዬው ሚስታቸውንም ሆነ ልጃቸውን የገደሉት እራሳቸው እንደሆነ ቃል ስለሰጡ በዛ መሰረት ሁለቱ ልጇች ይፈታሉ፡፡

ከአራት ቀን በኋላ የእናትና እህታቸውን  ሬሳ ተረክበው ከቀበሩ በሆላ ዘሚካኤል በከተማው አልታየም፡፡‹‹አንተ ያንን አውሬ ሰውዬ ገድዬ የእናቴንና የእህቴን ደም እንዳልበቀል ያደረከኝ ጠላቴ ነህ..ከእሱ በላይ እጠላሀለው ..እና ደግሞ መቼም ቢሆን ይቅር አልልህም፡፡››የሚል ማስታወሻ ለወንድሙ ጥሎ ነበር የጠፋው፡፡ቆይቶ እንደሰማነው ከጓደኞቹ ጋር በቦረና በኩል ወደኬኒያ ከዛም ወደጣልያን ከተሻገረ በኋላ…በፊትም ልጅ እያለ ጀምሮ ይሞካክረው  በነበረው ሙዚቃ ገፋበትና በትምህርትም አሳድጎ ጥሩ ሙዚቀኛ ሆነ ፡፡ለመጀመሪያ ጊዜ በህይወት መኖሩን ያወቅነው የዛሬ 3 አመት የሙዚቃ ክሊፑን ሲለቅ ነው፡፡

….የዛን ጊዜ ሚካኤል የተደሰተው መደሰት ያው አንቺም አብረሺን ስለነበርሽ ታውቂዋለሽ፡፡ከዛ በሀገር ውስጥ በጣም ተቀባይነት ስላገኘ ..ጓዙን ጠቅልሎ ገባ፡፡በሙዚቃ ብቻ ሳይሆን በፊልም ትወና ላይ መስራት ቀጠለ…እንግዲህ ባለፉት አምስት አመታት የገነባውን ስምና ዝና  እኩል ነው የምናውቀው፡፡››

‹‹ይገርማል….ግን ከመጣ በኃላ ወንድሙን ለማግኘት አልሞከረም…?››

‹‹ወይ ማግኘት..እኔ አንኳን ላገኘው ሄጄ ስለወንድሙ ሳነሳበት እንዴት እንደተንገሸገሽ እስከዛሬ ሳስበው ይዘገንነኛል..አሁንም ጥላቻው እንዳለ ነው፡፡አልፎ አልፎ በድብቅ እየመጣ የእናቱንና የእህቱን መቃብር እየጎበኘ እንደሚሄድ አውቃለው….በዛው ልክ ስለአባቱም ሆነ ስለወንድሙ ምንም መስማት እንደማይፈልግ እና ቢሞቱም ግድ እንደሌለው አውቃለው፡፡››

‹‹ተይ እንደዛ አትበይ…..››

‹‹ወይ አንቺ ልጅ ስንት ነገር ውስጥ አስገባሺኝ..ስለእሱ ለማወቅ ለምንድነው የፈለግሽው?፡››ስትል ዳግመኛ ጠየቀቻት፡፡

‹‹እንደምንም ብዬ በሰርጋችሁ ላይ እንዲገኝ ለማድረግ አስቤለው››

‹‹ምን?››አዲስአለም ክፉኛ ነው የደነገጠችው፡፡

‹‹ምነው መጥፎ ሀሳብ ነው እንዴ?››

‹‹አረ በፍጹም…ግን የሚሳካ እቅድ አይደለም….››

‹‹ከተሳካልኝስ?››

‹‹ከተሳካልሽማ….ለሚካኤል በሰርግ ላይ ሌላ ሰርግ ደገሽለት ማለት ይሆናል….በፊቱንም ይወድሻል በቃ የዘላለም ባለውለታው ነው የምትሆኚው››

ፀአዳ ‹‹ለማንኛውም ጉዳዩ በእኔና አንቺ መሀከል በሚስጥር ይያዝ …..ሚካኤል ሰምቶ ካልተሳካ ቅር እንዲሰኝ
አልፈልግም፡፡››ስትል አስጠነቀቀቻት፡፡

‹‹አታስቢ እኔም ባሌ በሰርጉ ሰሞን እንዲያዝንብኝ ስለማልፈልግ ..አልነግረውም…ለአንቺ ግን እንዲቀናሽ በቻልኩት መንገድ ሁሉ አግዝሻለው፡፡››

በዚህ ሁኔታ ነበር ከአዲስ አለም  ስለዘሚካኤል የተወሰነ ነገር ማወቅ የቻለችው..ከዛ ወደ ሶሻል ሚዲያ ሄደችና እና ስለእሱ የተፃፉ የጋዜጣ አምዶችና በተለያየ ጊዜ የሰጣቸውን ቃለ መጠይቆችን ሰብስባ ማንበብና ማዳመጥ ነው የቀጠለችው…ይሄ ሂደት አንድ ሳምንት ነው የፈጀባት፡፡በዚህ ጊዜ በአምስት አመት ውስጥ ያወጣችውን ሶስት አልበሞችና ፤ከስምንት በላይ ነጠላ ዜማዎችን እየደጋገመች ያደመጠች ሲሆን እሱ የተሳተፈባቸውን ስምንት የሚሆኑ ፊልሞችንም በጽሞና መመልከት ችላለች፡፡

እና በዚህ አንድ ሳምንት ውስጥ ለአመታት የምታውቀው የቅርቧ ሰው እንደሆነ እንዲሰማት አድርጎታል..ያንን ስሜት ግራ አጋቢ ነው፡፡‹አይ በጣም የምወደው ወንድሜ የሚካኤል ወንድም ስለሆነ በእሱ እይን  እሱንም ማየት ጀምሬለው ማለት ነው..›ስትል ለራሷ ማብራሪያ መስጠት ብትሞክርም ሊያሳምናት ግን አልቻለም፡፡

ደግሞ ስለሴሰኝነቱ..በየጊዜው ስለሚቀያይራቸው ሞዴል መሳይ ሴቶች፤ ከዝነኛ እንስቶች ጋር ስለሚጀምረው የፍቅር ግንኙነትና ስለመለያየቱ …ከስራው እኩል አንዳንዴም ከስራው በላይ ነው ሚያወራው፡፡እና ለእንደዚህ አይነት ሴት አውል የማይጨበጥ ሙልጭልጭ ወንድ ምን አይነት ስሜት ነው እየተሰማት ያለው….?መልስ የላትም፡፡ግን አሁን ልታገኘውና ልትጋፈጠው ወስናለች..ዝግጅቷንም ጨርሳለች፡፡
///          
ፀደይ ባደረገችው ጥናት እና በሰበሰበችው መረጃ መሰረት  የሚካኤል መንታ ወንድም የሆነው ዘሚካኤልን ለማናገር አንድ ብቸኛ መንገድ ብቻ እንዳላት ተረድታለች፡፡በሳምንት ሶስት ቀን በሚሰራበት በከተማዋ ታዋቂ  ናይት ክለብ  ተገኝታ እድሏን መሞከር ፡፡ከእሷ ባህሪ አንጻር እንደዛ አይነት ቦታ ተገኝታ የማታውቀውን ሰው ማናገር በጣም ከባድ የቤት ሰራ ነው፡፡ቢሆንም የግድ ልትወጣው የሚገባ ተግባር እንደሆነ እራሷን አሳምናለች፡፡

ባለፉት ሁለት ቀን ውስጥ የተባለው ናይት ክለብ ውስጥ በውድቅት ለሊት በመገኘት እሱ ሲዘፍን እና በቀበጥ አድናቂዎቹ ሲሞገስና ሲሸለም መመልከት ብትችልም  እሱን ተጠግቶ ለማናገር ያደረገችው ሙከራ ግን ሙሉ በሙሉ  አልተሳካላትም ነበር፡፡ዛሬ ግን የግድ ሊሳካላት ይገባል..ምከንያቱም ሰርጉ ከአምስት ቀን  በኃላ  ነው፡፡ዛሬ አግኝታ ካላናገረችው…ወደእዚህ መጥታ ሌላ ሙከራ የምትሞክርበት ሌላ እድል የላትም፡፡