አትሮኖስ
286K subscribers
118 photos
3 videos
41 files
567 links
╔╦╦╦═╦╗╔═╦═╦══╦═╗
║║║║╩╣╚╣═╣║║║║║╩╣
╚══╩═╩═╩═╩═╩╩╩
ግጥሞች አዳዲስና ቆየት ያሉ የታዋቂ ደራሲያን መፅሐፍቶችን በ PDF እንዲሁንም
ያልተነበቡ ድርሰቶችን ግጥሞችን ታሪኮችን ያገኙበታል።


Contact. @atronosebot
please dont touch the leave button.😔😳😳
Download Telegram
#ትኩሳት


#ክፍል_ሁለት


#በስብሐት_ገብረ_እግዚአብሔር

#እንደወረደ_ነውና_ለአንባቢ
#የማይመቹ_እኛ_ፀያፍ_የምንላቸው
#ቃላቶች_አሉትና_አሁንም
#በድጋሚ_እንደምናገረው
#የማይመቸው_እንዳታነቡት
#እመክራለሁ
።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።

አማንዳ
ለጥቂት ጊዜ


ያን ሰሞን አንዲት ቆንጆ አሜሪካዊት ነበረችኝ፣ አይኗ
ሰማያዊ፣ ፀጉሯ በጣም ንፁህ ቡና አይነት፡፡ እጅግ ደስ ትላለች፣
አልጋ ውስጥ ልብ ታጠፋለች ግን በማልፈልጋት ሰአት ሆቴሌ
እየመጣች አላሰራ ስላለችኝ፤ ቤተ መፃህፍት እየሄድኩ መስራት ግድ
ሆነብኝ፡፡ ሆቴሌ ስታጣኝ ወደ ቤተ መፃህፍቱ መምጣት ጀመረች።

እሷን ለመሸሽና በዚያውም ባህራምን ለማወቅ ስል ሀበሾቹን
እጠጋቸው ጀመር ምግብ ቤት አብሬያቸው እገባለሁ፣ ካፌ
ዶርቢቴል አብሬያቸው ካርታ እጫወታለሁ ከባህራም ጋር ግን ላይ ላዩን እየቀለዱ ለመሳቅ እንጂ፣ የልብ ለመጫወት አጋጣሚ ለጊዜው አላገኘሁም። ይልቅስ ከሀበሾቹ ጋር ግንኙነት በማድረጌ «ሚስቶቻቸውን» በመጠኑ እያወቅኳቸው ሄድኩ፡፡

የነበርንበት ዩኒቨርሲቲ ውስጥ ሴቶች ከወንዶቹ በጣም ይበዛሉ፡፡
ስለዚህ ለሁሉ ሴት 'ሚዳረስ ወንድ የለም....አሉ ሶስት፣ አራት፣
አምስት 'የሆኑ ወንድ 'ሚያድኑ ልጃገረዶች። ታድያ ወንዱን ቆንጆ
ቆንጆዎቹ ይዘውታል፣ ተጠምጥመውበታል። ነፃ የሆነ ወንድ አይገኝም፣ ቢገኝም ወይ የደስ ደስ የለውም፣ ወይ ጥቁር ነው። ጥቁር ደሞ ምን ቢወዱት አገሩ መመለሱ አይቀርም፡፡ ብልጥ ወይም ውብ ወይም እድለኛ ካልሆኑ፣ ፈረንሳይ ወንድ ማግኘት አይቻልም። ሳያገቡ የማርጀት ፍርሀት በወራቱ ዋሻ ሰአመታቱ ጫካ አድፍጦ
ይጠብቃል.

ጥቁሮቹ ወንዶች ገና እንደመጡ፣ በንግድነት ምክንያት ቆንጆ
ሴት ማጥመዱን ለጊዜው ስለማያውቁበት፣ የተገኘችውን እሺ ብለው ይቀበላሉ። የምትገኘው ደሞ ቆንጆ ያልሆነች ናት፣ ስለዚህ ማቆያ
ናት...

«የሀበሾቹ ሚስቶች» ጎደሎ ብጤዎች ነበሩ፡- እዚህ ቅርፅ
ይጎድሳል፣ እዚያ ድምፅ ይጎድላል፣ እዚያ ጠባይ ይጎድሳል። ብቻ፣ሉልሰገድ እንዳለኝ ሁሉም ያ ነገር ኣላቸው ለጊዜው ሀበሾቹ የፈለጉት እሱን ነው:: መልኩ፣ የደስደሱ፣ ደማምነቱ፣ ጠባዩ፣ በኋላ
ዝግ ተብሉ ይፈለጋል ከሁሉም አስቀያሚ አማንዳ ሳትሆን አትቀርም፡፡ ድብልብል
አሜሪካዊት ናት፡፡ ወፍራም አንገቷ ዙርያ ስጋው ተጣጥፏል፣ ሽንጥ
ሚሉት የላትም፣ ስትራመድ የሚንቀጠቀጠው ባቷ ረዥም ቂጥ ይመስላል። በጭራሽ ስሜት አትቀሰቅስም። ሉልሰገድ ለምን
እንደያዛት ለጊዜው ሊገባኝ አልቻለም፡፡ የቸገረው እርጉዝ ያገባል ይባላል፣ እሱ ግን አቅፏት ይዞራል። ወገቧ ዙርያ እጁ ስለማይደርስ ትከሻዋን አቅፎ እሷ ወገቡን አቅፋ ሲሄዱ አያቸዋለሁ። የአማንዳ ፈገግታ ደግና ንፁህ ነው፣ ትንንሽ አይኖቿ ንፁሀ ሰማያዊ ናቸው፣ ረዥም ፀጉሯ በጣም ንፁህ ነጭ ሆኖ፣ ጨረቃ ውስጥ ተነክሮ የወጣ ይመስላል። ግን ይህን ሁሉ ውበት ጮማዋ አፍኖ ይዞ እንደሌለ አድርጎታል። ስታያት ውፋሬዋ ነው 'ሚታይህ፣ ስታስታውሳት ጮማዋ ነው ትዝ ሚልህ

ሲልቪ ግን በጣም ቆንጆ ናት። «እጥር ምጥን» ያለች ፈረንሳዊት ሆና፣ ቡናማ ጉልህ አይኖቿ ውስጥና ውብ ሰፊ አፏ
ዙርያ እንደ ነበልባል የሚውለበለበው ፈገግታዋ ልብ ያሞቃል። ወደ ኋላ የተለቀቀው ንፁህ ጥቁር ፀጉሯ ያብለጨልጫል፣ ስትራመድ
ረዥም አንገቷን እያወዛወዘች ስለሆነ፣ ይሄ ጥቁር ሀር ፀጉሯ ዥው ዥው ይጫወታል። ከታች ደሞ አበጥ ያለው ዳሌዋ ያንኑ ያህል ይወዛወዛል። እግሯ በብዙ ጥንቃቄ የተቀረፀ ውብ ፍጥረት ነው::ፍቅርም ምኞትም የምትቀሰቅስ ወጣት ትመስላለች። ተመስገንን በጣም ትወደዋለች ሲሉ ሰምቻለሁ፡፡ ይሄ ተመስገን ፈረንሳይ አገር የተስማማው ይመስላል።

ዩኒቨርሲቲውን «ሲቴ» ይሉታል። ሲቴ ውስጥ መኝታ ቤት
ያላቸው ሀበሾች ተመስገን፣ ሉልሰገድ፣ ተካ፣ ሀይለየሱስ ናቸው፡፡
ሌሉቹ እንደኔው የሆቴል ክፍል ወይም የከተማ ቤት ተከራይተው
ይኖራሉ ቆንጆዋን አሜሪካዊት እንዳላገኝ ስፈልግ ከሉልሰገድ ወይም ከተመስገን ቁልፍ ለምኜ መኝታ ቤታቸው ቁጭ ብዬ ሰራለሁ::ሀይለየሱስ ቤት እንዳልሰራ ሰውየውን አልወደውም። ተካ ቤት
እንዳልሰራ ደሞ የተካ ቤት ይገማል። አይ ተካ! እግዜር ይይለት አንዳንዴ እንኳ እግሩን ቢታጠብና እግር ሹራቡን ቢያጥብ ምን ቸገረው ነበር? ዝም ብሎ ብቻ ጥፍሩን እየነከሰ መነጫነጭ ምን ያረግለታል?

ሉልሰገድ ወይም ተመስገን ቤት ቁጭ ብዬ ስስራ አንዳንዴ
ባህራም ይመጣል፡፡ ትንሽ እናወራና ፂሙን ተላጭቶ መልካም ስራ ብሉኝ ይወጣል። ፀጉራም ነው። እጆቹን፣ ደረቱን፣ አንገቱን፣ ፊቱን ፀጉር ወሮታል። ፂሙን ሲላጭ አይኑ፣ አፍንጫውና ጆሮው ብቻ ናቸው መላጨት የሌለባቸው:: ቢሆንም ፀጉሩ አያስቀይምም፡፡ በጣም
ንፁህ ሰው ነው።

አንዳንዴ ደሞ ቁጭ ብዬ ስሰራ ድቡልቡሏ አማንዳ ወይም
ውቢቷ ሲልቪ ይመጣሉ ወዳጃቸውን ፍለጋ፡፡ ቀስ በቀስ እነዚህን ሁለት ልጃገረዶች» እያወቅኳቸው፣ እየወደድኳቸው ሄድኩ፡፡ እነሱም ሊወዱኝ እንደጀመሩ ታወቀኝ። ስለራሳቸው ኑሮ በመጠኑ ይነግሩኝ ጀመር ..

አንዳንድ ቅዳሜ ማታ ሀበሾቹና ጓደኞቻቸው «ሱርፕሪዝ ፓርቲ»
ያደርጋሉ። «ሰርፕሪዝ ፓርቲ» ድንገተኛ ብጤ ነው። ታስቦ የታቀደ
ፓርቲ ሳይሆን፣ ጓደኛሞች ሲገናኙ «ዛሬ ምን እናርግ? ሲኒማ
እንግባ ወይስ ምን ይሻላል?» ይባባሉና ለምን ሰርፕሪዝ ፓርቲ
አናረግም?» ይላሉ፡፡ ያን እለት ማታ ፓርቲው ይደረጋል። የተገኙ
ሰዎች ይጠራሉ፣ የራሳቸውን መጠጥ ይዘው እንደሚመጡ የታወቀ ነው:: አንዱ ቤት ፓርቲው ይደረጋል። ለዚህ ጉዳይ ሀበሾቹን
ባህራም ያገለግላቸዋል
ይጀምራል፤ ወንዶቹን ይጠራል፣ ሴቶቹን ይጋብዛል፣ እዚህ ትእዛዝ
እንደ አውሎ ነፋስ በፍጥነት መዘዋወር ይጀምራል ወንዶቹን ይጠራል ሴቶቹን ይጋብዛል እዚህ ትእዛዝ እዚያ ምክር ይሰጣል፣ ከዚህ ዲስክ ከዚያ ሴት ይዋሳል፣ ፓርቲው ይጀመራል። ተሳታፊዎቹ ወንዶች ኣብዛኛዎቹ ኢትዮጵያውያንና ኢራናውያን ናቸው፣ የሁለቱ አገሮች ማህበር ይመስላል።

እንዲህ አይነት ፓርቲ ውስጥ ነበር ሉልሰገድ አማንዳን ያገኛት። ፓርቲው ውስጥ ጥቂት ሴቶች ብቻ ነበሩ፣ እነሱም ተይዘዋል፡፡ ያልተያዙ አንዲት በጣም ደቃቃ የሆነች የሩቅ ምስራቅ
ልጅና እንዲት አስቀያሚ ድቡልቡል ኣሜሪካዊት ብቻ ናቸው::ምስራቃዊቷ በጣም ደስ ትላለች፣ ግን ሉልሰገድ እሷን ይዞ አልጋ ውስጥ ሲገባ ሊታየው አልቻለም። «ዎ! ብትሞትብኝስ?» ብሎ አሰበ፡፡ ተዋት። ድቡልቡሏ አሜሪካዊት ፈፅማ ደስ አትልም፣ ግን ሙዚቃውና መጠጡ እየገፋፉ ወደሷ ወሰዱት። ተዋወቃት። ስሜ
አማንዳ ነው አለችው፣ አብረው ይደንሱ ጀመር፡፡ በእንግሊዝኛ
እያወሩ ሁለቱም በብሉይ ጠጡ፣ ሞቅ አላቸው:: ስታቅፈው
ስታናግረው በጣም ደስ እያለችው ሄደች ይስማት ጀመር

«ተው እዚህ አትሳመኝ» አለችው

«ምናለበት?» አላት ጆሮዋን እየሳመ አልችልም፡፡ ስሜቴ በጣም ይቀሰቀሳል» አለችው:: ድምፅዋ
በጣም አቆመበት።

ታድያ ምናለበት?» አለ እየተሻሻት

"ያኔ መሳም ብቻ አይበቃኝም» ብላ በሀይል ተጠጋችው::

ሉልሰገድ ቀስ ብሎ ወደ አንዱ መኝታ ክፍል ገብቶ እዚያ
ይሳሳሙ የነበሩትን ሁለት ፈረንሳዮች አስወጣቸው። (መኝታው የማን እንደሆነ እንጃ መብራቱን አጠፋ። ተመልሶ መጥቶ አማንዳን ወደዚህ ጭለማ መኝታ ቤት ወሰዳት፡፡ በሩን ቆለፈ። አልጋው ላይ አጋድሞ ይስማት ጀመር። እየሳመ፣ እያሻሽ ሙታንታዋን አስወለቃት። ጭለማ በመሆኑ አስቀያሚ መልኳ ስለማይታየውና፣አሳሳም ከማወቁም በላይ ወፍራም ገላዋ ምቹ ስለሆነ፣ እጅግ በጣም ተደሰተባት ጠግቦ ከላይዋ ሊነሳ ሲል፣ እቅፍ አደረገችውና እንዳይነሳ ከለከለችው
👍231
#ምንዱባን


#ክፍል_ሁለት


#ትርጉም_ከዬሐንስ_ገፃዲቅ

....አልፎ አልፎ መስመሩን
የሚዘረጋው ጨረቃና ደፋ ቀና የሚሉት ከዋክብተ አካባቢው ጨርሶ ጨለማ እንዳይሆን ረድተዋል :: ስለዚህ የመሬቱን የሰማዩን ያህል አልጨለመም:: ሆኖም አካባቢው በጣም ያስፈራል፡፡.

ከጉብታውና ከተንጣለለው ሜዳ ላይ ከአንድ ቅርጸ ቢስ ዛፍ ሌላ
ምንም አልነበረም፡፡ ዛፉ መንገደኛው ከደረሰበት ሩቅ አልነበረም:: ሁናቴው ስላላማረው መንገደኛው ወደመጣበት ተመለሰ፡፡

ከምሽቱ ወደ ሁለት ሰዓት ገደማ ሆኖአል፡፡ አካባቢውን ስለማያውቅ
መንገድ እንደመራው ብቻ ዝም ብሎ ተጓዘ፡፡ የከንቲባውን ቤት እንዳለፈ ከትምህርት ቤት አካባቢ ደረሰ፡፡ ትምህርት ቤቱን አልፎ እንደ ሄደ ቤተክርስቲያን አጋጠመው:: ገና ቤተክርስቲያኑን ሲያይ እጁን ጨብጦ ዓይኑን ወደላይ አንጋጠጠ፡፡

ከቤተክርስቲያን ፊት ለፊት አንድ ማተሚያ ቤት አለ፡፡ ሰውዬው
ድካም አወራጭቶት ስለነበር ከዚህ የተሻለ ሥፍራ ሳይፈልግ ከማተሚያ ቤቱ አጠገብ ከነበረው የድንጋይ አግዳሚ መቀመጫ ላይ ተጋደመ::

ወዲያው እንደተጋደመ አንዲት አሮጊት ከቤተክርስቲያኑ ወጡ፡፡
«ወዳጄ ከዚህ ምን ታደርጋለህ?» ሲሉ ጠየቁት፡፡

«አየሽ የእኔ አዛኝ፤ መተኛቴ ነዋ!» አሊ በቁጣና በድፍረት የማይሆን
መልስ መስጠቱ ሳይታወቀው:: ክብር የሚገባቸው አዛኝዋና ደግዋ ሴት ማዳም ላ ማርኩዚ ይባላሉ::

«እንዴ! ከድንጋይ ላይ!» አሉ፤ «ሌሊቱን በሙሉ ከድንጋይ ላይ
ተኝተህ ሊነጋልህ አይችልም:: ረሃብ እንዳንገላታህና ብርድ እንዳጠቃህ ሰውነትህ ይመስክራል፡፡ የሚያስጠጋ አላገኘህም?»

«ብዙ ቤት ሞከርኩ፤ የየቤቱን ደጃፍ አንኳኳሁ::»

«እና!»

‹‹ሁሉም ሰው ከበራፌ ሂድ አለኝ::
ደግዋ ሴት የሰውዬውን ጀርባ እየመቱ፡ ከአደባባዩ ባሻገር የሚታየውንና ከጳጳሱ ቤት አጠገብ የነበረውን ቤት ጠቆሙት፡፡
«ያንን ቤት ሞክረሃል?» ሲሉ ጠየቁት::

«አዎን::»

«ከዚያ ማዶ ከሚታየው ቤት አንኳኩተሃል?»

«የለም::»

«እዚያ ሞክር እስቲ፡፡»

እናያ ደገ ጳጳስ ከተማ ወስጥ ሲዘዋወሩ በመቆየታቸው ስለደከማቸው ያን እለት ማታ ከክፍላቸው ሳይወጡ ብዙ ቆዩ:: በተጨማሪም ብዙ ስራ
ስለነበራቸው «ሥራዩን ሳልጨርስ አልነሳም» በማለት አእዚያው አመሹ::

ከምሽቱ ሁለት ሰዓት ሲሆን እዚያው ሥራቸው ላይ ነበሩ:: በብጣሽ ወረቀትና በማስታወሻ ደብተር ላይ ጉልበታቸውን እያስደገፉ ሲፅፉ
እንደተለመደው አልጋቸው አጠገብ ከነበረው ቡፌ ከብር የተሠራ ሣህን ለማውጣት መዳም ማግልዋር ይገባሉ:: ሴትዬዋ ከተመለሱ በኋላ ጥቂት
ቆይቶ ገበታ እንደቀረበና እህታቸው እንደሚጠብቋቸው በመገመት ጳጳሱ ወደ ምግብ ቤት ሄዱ:: ምግብ ቤቱ፡ የአራት ማዕዘን ቅርጽ ያለው ዓይነት ሆኖ የእሳት ማንደጃ አለው:: ቢፈለግ ወደ አውራ ጎዳናው የሚያስወጣ በርም አለው:: በአትክልቱ በኩል መስኮት አለ፡፡

ማዳም ማግልዋር ገበታውን ሠርተው ከጨረሱ በኋላ ጠረጴዛውን እያስተካከሉ ከመድምዋዚል ባፕቲስታን ጋር ይጫወታሉ:: ገበታው አጠገብ
ሻማ ከትንሽ ጠረጴዛ ላይ ተቀምጦ እየተቀጣጠለ ነው:: ከማንደጃው ውስጥ
የተቀጣጠለው እሳት ፍም ብዛት ስለነበረው ክፍሉ ይሞቃል፡፡ የቤታቸው በር እንዴት መቆለፍ እንዳለበት መዳም ማግልዋር ሲያወሩ ጳጳሰ ይገባሉ፡፡

ማዳም ማግልዋር ለእራት የሚሆን ሸቀጣሸቀጥ ለመግዛት ወደ ገበያ ሄደው ሳለ አንድ መግቢያ ያጣ ማጅራት መቺ ከተማ መግባቱንና ይህ ሰው
በጊዜ ከቤታቸው በማይገቡ ሰዎች ላይ አደጋ ሊያደርስ እንደሚችል ሲወራ ይሰማሉ፡፡ ሁለቱ ሴቶች ስለዚሁ ጉዳይ ሲያወሩ ጳጳስ ስለገቡ «አባታችን
መዳም ማግልግር የሚናገሩትን ይሰማሉ?» በማለት ጠየቅዋቸው::

«የምትሉት ነገር ግልጽ ባይሆንልኝም ሰምቼአለሁ» አሉ ጳጳሱ፡፡ከዚያም ፊታቸውን ወደሚነድደው እሳት በማዞርና እጆቻቸውን ከጉልበታቸው
ላይ በማሳረፍ ሠራተኛቸውን እያዩ

«ታዲያስ ፤ ምንድነው ጉዳዩ? የሚያስፈራ ነገር አለ እንዴ?» ሲሉ ጠየቁ፡፡

ይህን ጊዜ መዳም ማግልዌር ሳያስቡት ታሪኩን በማጋነን አዋሯቸው::
«ያለመጫሚያ ባዶ እግሩን የሚጓዝ ማጅራት መቺ፧ ሌባ፤ ቀማኛ ከተማ ገብቷል» አሉ፡፡ «ክዊን ላባር ሄዶ ማረፊያ ቢጠይቅ ባለቤቱ አልፈቀደለትም::
ከመሸ በኋላ ከተማ ውስጥ ሲዘዋወር ታይታል:: ስልቻውን በገመድ አስርና ተሸክሞ ይዞራል:: መልኩ ደግሞ በጣም የሚያስፈራ ነው::

«እውነትሽን ነው?» ሲሉ ጳጳሱ ጠየቁ፡፡

ጳጳሱ በታሪኩ የተመሰጡና ፍርሃትም ያደረባቸው ስለመሰላቸው

መዳም ማግልዋር ታሪካቸውን በኩራት ይቀጥላሉ:: «አዎን አባታችን፤ እውነት ነው:: ዛሬ ማታ ከተማ ውስጥ አንድ ነገር ይሆናል፡፡ ከተማው ሁሉ ይህንኑ ነው የሚያወራው:: መድምዋዜል ባፕቲስታን ደግሞ እንደምትለው...» በማለት ሴትዬዋ ንግግርዋን ስትቀጥል «እኔ» በማለት የጳጳሱ እህት ጣልቃ ገብተው «ያልኩት ነገር የለም» ይላሉ፡፡

ተቃውሞውን እንዳልሰሙ መስለው መዳም ማግልዋር ልፍለፋቸውን ቀጠሉ፡፡

«የዚህ ቤት ደህንነት ይህን ያህል አስተማማኝ አይደለም:: አባታችን
ቢፈቅዱልኝ ሄጄ ቁልፍ ለሚሠሩት ሰወዬ የድሮዎቹን መቀርቀሪያዎች
መልሰው እንዲገጥሟቸው ልንገራቸው:: መቀርቀሪያዎቹ ስላሉ በደቂቃ ይሰርዋቸዋል፡፡ ለዛሬ ማታ ብቻ እንኳን ባይሆን ለወደፊቱም ጥሩ ነው፤
በራችን ጠንካራ መቀርቀሪያ ይግባለት:: በቀላሉ የሚከፈት በር እጅግ አደገኛና አስፈሪ ነው:: አባታችን እንደሆነ ይቅርታ ቢደረግልኝ እኩለ ሌሊት
እንኳን ቢሆን ቤት ለእንግዳ፤ ይግቡ የማለት ልምድ አለብዎት:: ግን መቼም ለዚህ ፈቃድ መጠየቅ እንኳን አስፈላጊ» ሴትዮዋ አሳባቸውን ሳያጠቃልሉ በር በኃይል ይንኳኳል፡፡ «ይግቡ» አሉ ጳጳሱ፡፡

በሩ ተከፈተ:: ኣንድ ሰው ሰዎቹ ከነበሩበት ክፍል ውስጥ ገባ፡፡
ያ የምናውቀው ማደሪያ ፍለጋ ከቤት ቤት ፤ ከሥፍራ ሥፍራ
ይንከራተት የነበረው መንገደኛ ነበር፡፡ ሰውዬው በሩን መልሶ ሳይዘጋ አንድ እርምጃ ወደፊት ተራምዶ ቆም አለ፡፡ ስልቻውን በጀርባው ተሽክሞ ዱላውን
በእጁ እንደያዘ ነው:: የእሳቱ ውጋጋን ከፊቱ ላይ ሲያርፍ ሻካራውና ድካም ያጎሳቆለው ፊቱ የጭካኔ ምልክት እንዳለበት አጉልቶታል፡፡ ሆኖም ያ ስሜት ወደ ውስጥ የተቀበረ እንጂ በግልጽ የወጣ ኣልነበረም:: የመናፍስት
በአካል መታየት ነበር የሚመስለው::

ማዳም ማግልዋር ለመጮህ እንኳን አቅም አልነበራቸውም፡፡ እንደቆሙ እየተንቀጠቀጡ አፋቸውን ከፍተው ቀሩ፡፡
መድምዋዜል ባፕቲስታን ዞር ሲሉ ሰውዬው ወደ ውስጥ ሲገባ አዩ፡፡
በፍርሃት ተውጠው ከመቀመጫቸው ብድግ አሉ፡፡ ከዚያም ዝግ ብለው ወደሚነድደው እሳት ዞረው ወንድማቸውን ተመለከቱ፡፡ ፊታቸውን ሲያዞሩ ትንሽ መንፈሳቸው ተረጋጋ፡፡

ጳጳሱ ሰውዬውን በጥሞና ተመለከቱት:: ምን እንደሚፈልግ ሊጠይቁት አፋቸውን እንደከፈቱ ለመናገር እድል ሳይሰጣቸው የያዘውን ዱላ በሁለት
እጁ በመመርኮዝ ከዚያ የነበሩትን ሰዎች አንድ በአንድ ከቃኘ በኋላ ድምፁን ከፍ አድርጎ መናገር ጀመረ::

«ተመልከቱኝ! ስሜ ዣን ቫልዣ ይባላል፡፡ የተፈረደብኝ ወንጀለኛ
👍27
#ገረገራ


#ክፍል_ሁለት


#በታደለ_አያሌው

..ማን ቢሆኑ ነዉ? ምን አገባቸዉ?
ዞር ብዬ በቁጣ ላጠናግራቸዉ አሰብሁና፣ መልሼ ተዉሁት፡፡
ካለኝ ልምድ ግን ማንነታቸዉን መገመት እችላላሁ፤ የጠላት ወገን ጆሮ ጠቢዎች ናቸው። ቢሆንም ግን ዓላማቸው አልገለጥልሽ ብሎኛል። ይኼን ጉዳይ እንዲሁ እያውጠነጠንሁ፣ እመዋ የላከችኝንም ከቤቷ አድረሼላት
ታላቁን ቤተ መንግሥት አለፍሁት። ከዚያም በታላቁ የማኅበራችን ሕንጻ ምድር ቤት በሚገኘው መኪና ማቆሚያ ደርሼ መኪናዬን አቆምሁና፣ ሰዓቴን ስመለከት መንገዱ ስድስት ደቂቃዎች ብቻ ፈጅቶብኛል። ሰባት
ኪሎ ሜትር፣ ያውም እናቴ የላከችኝን ጭምር ወደ ቤት አድርሼ፣ ያዉም በአዲስ አበባ መንገድ በስድስት ደቂቃ ብቻ? (እንኳንም እመዋ አላየችኝ
ብዬ አማትቤ፣ የቀረችኝን አንድ ደቂቃ አብቃቅቼ ወደ ዋናዉ የሲራክ፤ ማዕከል ለመግባት ተጣደፍሁ፡፡

ወደ ዐሥራ ስምንተኛው ፎቅ የሚያደርሰኝ አሳንሰር ውስጥ ጥልቅ አልሁ። አሁን ወደ ላይኛው የመጨረሻ ወለል እያቀናሁ ቢሆንም፣ የሲራክ ፯ ዋና ማዕከል የሚገኘው ግን በተቃራኒዉ ከምድር ቤቱ የመኪና
ማቆሚያም በታች ተሠውሮ ነው፡፡ በኢትዮጵያ መንግሥትም ሆነ፣ በቤተ ክርስቲያን ፊት በይፋ የሚታውቁለት የማኅበሩ ብዙ አገልግሎቶች የሚከናወኑት በዚሁ ሕንጻ ሲሆን፣ በምድር ቤት ካለው ሰፊ የመኪና ማቆሚያ እስከ ላይኛው የመጨረሻ ወለል ድረስ የሚገኙ ቢሮዎች ሁሉ፣
ለእነዚሁ አገልግሎቶች በግላጭ የተደለደሉ ናቸው። ለምሳሌ ‹ጥናትና ምርምር የሚባለው አንድ ማዕከል ብቻውን ኹለት ሙሉ ወለሎች ይዟል። ሌሎቹም እንደዚሁ። እያንዳንዷ ቢሮ ደግሞ የራሷ ስም እና ቁጥር ተሰጥቷታል፡፡

የሲራክ፮ን ህልውና ይቅርና፣ ከነጭራሹ ከሕንጻው ምድር በታች ሌሎች ወለሎች እንዳሉ የሚያውቁት እጅግ ጥቂት የራሱ የሲራክ ማዕከል አባላት እና ዋና ዋናዎቹ የማኅበሩ አመራሮች ብቻ ናቸዉ፡፡ ቀድሞ ነገር ለሕንጻዉ ንድፍ ያወጡለትም ሆነ ያሳነጹት በራሳቸዉ በአመራሮቹ
በጥብቅ ምስጢር የተመረጡ ባለሙያዎች ስለሆነ፣ ከእነሱ በቀር የሚያዉቀዉ የለም። እኔም የዚህን ጠመዝማዛ የምድር ቤት መግቢያ ዘልቀው እንዲገቡበትም ሆነ እንዲወጡበት ፈቃድ ካላቸው ጥቂቶች መካከል አንዷ በመሆኔ፣ ከምንም የሚበልጥ ዕድለኛነት መሆኑን አምናለሁ። በመሆኑም የዚህ ማዕከል ኃላፊ የሆነዉ ባልቻ፣ በአስቸኳይ እንድደርስ ወደ ጠራኝ ኮቴ አልባው የሲራክ፤ ማዕከል ለመግባት ወደ
ላይኛው ወለል ደርሼ ከአሳንሠሩ ወርጃለሁ። ከአሳንሠሩ ፊት ለፊት ትንሽ ከተራመድሁ በኋላ ወደ ግራ እጥፍ አልሁ። አሁንም ትንሽ እንደ ሄድሁ ከላይ “ ፲፰፻፴ ከታች ደግሞ “ምክረ ካህን” የሚል ቃል እንደ ነገሩ የተጻፈበት ክፍል ከፍቼ ገባሁ። ቢሮዋ መጻሕፍት በመደርደሪያዎች የታጨቁባት ክፍል ስትሆን፣ ሰዉስጥ በኩል ከበሯ አጠገብ ሁልጊዜም
ካባ የደረቡ አንድ ሽማግሌ ለይስሙላ ይቀመጡባታል። ምናልባትም ግራ የገባዉ ወይም ጥርጣሬ ያደረበት ባይተዋር ሰዉ ወደ ክፍሉ ሲያንኳኳ፣
በማያስጠረጥር ትሕትናቸዉ ከርፈድ ያደርጉና እንደሚሆን እንደሚሆን ሸንግለዉ የሚመልሱት እኒህ በሩ አጠገብ የሚቀመጡት ካህን መሳይ ባለ
ካባ ስዉዬ ናቸዉ፡፡

እጀታዉን በመያዜ ብቻ እኔ መሆኔን በአሻራዬ አውቆ የተከፈተልኝ የዚች ክፍል በር ልክ ወደ ውስጥ እንደ ዘለቅሁ በራሱ ተቆለፈ። በመቀጠል
ወደ ምዕራቡ ግድግዳ ተራመድሁና በመጻሕፍት መካከል እጄን ሰድጄ ግድግዳውን እንደ አዛኝ እናት ስደባብሰው፣ በነጭ ቀለም የደመቀዉ ልሙጥ ግድግዳ ስንጥቅ እየፈጠረ፣ እየሰረገ ሄደልኝ፡፡ ጨርሶ ጥልም ካለ በኋላ ወደ ጎን ተንሸራቶ ጠባብ በራፍ ወጣለት።

አቤት ለመጀመሪያ ጊዜ እዚህ የደረስሁ ጊዜ የተደነቅሁት፤
ወደ ዉስጠኛዉ ክፍል እንደ ዘለቅሁ፣ ይኸኛዉም በር እንደገና ወደ መጽሐፍ መደርደሪያነት ከተመለሰ በኋላ፣ ልክ እንደ መጀመሪያው ሁሉ በራሱ ተቆለፈ። ወደ ነበረበት ተመልሶ ከግድግዳዉ ጋር ለመመሳሰል
ቅጽበትም አልፈጀበት፡፡ ከዚያም ጠበብ ባለችዋ ኮሪደር ትንሽ እንደ
ተራመድሁ፣ በጨረር የታጠረ በር ላይ ደረስሁ። ዝግንትሉ የወጣ ቀይ ክር የሚመስል ኤሌክትሮናዊ ጨረር ከላይ እስከ ታች ተመሳቅሎበታል። ጨረሩ ካልጠፋ በቀር፣ በጭራሽ ማለፍ አይሞከርም። በፍጹም፡፡ ያለበዚያ
ጨረሩን ሊጥሰዉ የሞከረዉን ሁሉ አንጨርጭሮ ሕቅ የማድረግ ጭካኔ አለበት። ከፊት ለፊት ያለዉ ካሜራ ሲያየኝ ስለነበር፣ ለቅጽበት ያህል እንኳን ሳያስጠብቀኝ ጨረሩ ድርግም ብሎ ከሰመልኝ፡፡ ካሜራ መኖሩን ያወቅሁት የኋላ ኋላ ስለመኖሩ ከተነገረኝ በኋላ ነዉ እንጂ፣ በትክክል የት እንዳለ እንኳን ያኔ፣ አሁንም ድረስ አይታየኝም። ብቻ ይኼ እሱ
የሚያየኝ፣ እኔ ግን የማላየዉ ካሜራ አዉቆኝ ጨረሩን አከሰመልኝ፡፡ ከዚያም ወደ ቀኝ ታጥፌ ትንሽ እንደ ተራመድሁ፣ ባለ ኹለት ተከፋች በር አጠገብ ደረስሁ። እሱም ገና ስጠጋው ወለል ብሎ ተከፈተልኝ።
ይህንንም አልፌ አልደረስሁም ገና። ገና ወደ ታች የሚወስደኝ ሥሩ የዉስጥ ለዉስጥ አሳንሰር ይጠብቀኛል። ልክ ወደ አሳንሠሩ እንደ ገባሁ ወደ ታች ይዞኝ ተፈተለከ።

ከመኪናዬ ወርጄ፣ ከዚያ ደግሞ ያንን ሁሉ ተጠንቅቄ፣ እዚህ በምድር ቤት ከሚገኘው የሲራክ ፯ ማዕከል ለመድረስ ኹለት ደቂቃዎች ብቻ ፈጀብኝ።

ልክ እኔ እንደሆንሁት ሁሉ፣ ዕድል ብሎለት ለመጀመሪያ ጊዜ ማዕከሉን የሚጎበኝ ሰው መደንገጡ አይቀርም። ምክንያቱም መግቢያው
የመንግሥተ ሰማያት፣ ውስጡ ደግሞ ከገጠር ዳስ የማይሻል አዳራሽ ይመስልበታል። የሚከናወንበትን ተአምር እስከሚያውቅ ድረስ የታላቁ
ማኅበር መረጃ ማዕከል፣ ሲራክ፤ ይቺ ናት በቃ?› ብሎ ቢያናንቅ
አልፈርድበትም፡፡ ከፊት ለፊት ከጠፍር አልጋ በማይለዩ መጠነኛ ወንበሮች ላይ ተቀምጠዉ በየኮምፒዉተሮቻቸዉ ላይ ያፈጠጡ ጥቂት ሰዎች
ይታያሉ። ግድግዳዉ ዙሪያዉን ከወገቡ በላይ ዝርግ መከሰቻ ኖሮት ከተለያዩ ሥፍራዎች በሥዉር በተጠመዱ ካሜራዎች የሚቀርጹትን ተንቀሳቃሽ ምስል ሁሉ በመቃን በመቃን ከፋፍሎ ከስቶታል። ጠቅላይ ቤተ ክህነት ግቢዉን፣ ብሔራዊ ቤተ መንግሥት ውስጠ ገጹን፣ ብሔራዊ ቤተ መዘክር ውስጡን፣ የአክሱም ጽዮንን ቅጽረ ግቢ፣ የሌሎች ታላላቅ ገዳማትን እቃ ቤቶች፣ የማኅበሩ ጥቂት ቅርንጫፎች ዙሪያ ገባቸዉን
ያለብዥታ ያስመለክታሉ። በነዚህ ሁሉ ማን እንደሚወጣና ማን
እንደሚገባ ያለማቆራረጥ ኩልል አድርገው ያሳያሉ፡፡ ምንም እንኳን ሌላ መጠባበቂያ የመረጃ ማዕከል በሌላ ቦታ እንደሚኖረዉ ብገምትም፣አብዛኛው ከወኪሎች የተሰበሰበው መረጃ ሁሉ የሚተነተነው እና ትርጉም
የሚሰጠው ግን በዚችኛዋ ክፍል ነው፡፡ በውስጧ የተለያዩ ሚናዎች
የተሰጣቸው ሃያ ሦስት የማዕከሉ አባላት በለም አእምሯቸው ቁጭ ብድግ ይሉበታል። ወጣቶች ቢበዙበትም ጥቂት ጎልማሳዎች እና በዕድሜ ጠና ያሉ ሴቶችም አሉበት፡፡

ዕረፍት በቤቱ እምበዛም አትታወቅም፡፡

ሁልጊዜም ወደዚህ ክፍል ስገባ የሚሰማኝ ስሜት አሁንም ተሰማኝ። ወኔዬ ሞቀ። ኩራት ኩራት፣ ደስ ደስ አለኝ፡፡ ልቡናዬ እንደ መሙላት፣ ነፍሴ እንደ መርካት፣ ዓይኔ እንደ መብራት አለልኝ፡፡ በሐቅ ቤት እንዳለሁ
ተሰማኝ፡፡ ከቅኑዓን ጋር እንደ ሆንሁ ታወቀኝ፡፡ ከበጎዎች ወገን መሆኔ መጣብኝ። ሁሉም በየሥራው ተጠምዶ ልብ ያለኝ ባይኖርም፣ ጎንበስ ቀና
ብዬ ለሁሉም የፍቅር ሰላምታ እያቀረብሁ የማዕከላችን የሲራክ፤ ዋና ኃላፊ የሆነዉ ባልቻ ወደሚገኝበት ቀጣይ ክፍል ተራመድሁ።

“ልጅየዋ?” ሲል ተቀበለኝ፣
👍331
#ሳቤላ


#ክፍል_ሁለት


#ድርሰት_ሚሲስ_ሔንሪ_ውድ

« እረ እባክህ ምንም አይደለም » አለ ጌትዮው ። « ማን አለ መሰለህ ?ከልጄና
ከማርሊንግ ከመጣችው ከሚሲስ ቬን በቀር ሌላ የለብንም።ሚሲስ ቬንል ወደ ግብዣው ይዛት ለመሔድ ነበር የመጣችው። እሷም ብትሆን ከውጭ ራት አለባት ሲሉ የሰማው መስሎኛል እንደተባለው ከሌለች እኛ ብቻችንን እንበላለን እስኪ እሱን ደወል ነካ አድርገው ሚስተር ካርላይል ፡ ይህ መከረኛ እግሬ እኮ አልንቀሳቀስ አለኝ " ደውል ተደወለ። አሽከር ገባ።

« እስኪ ሚሲዝ ቬን ከኛ ጋር ራት ትበላ እንደሆነ ጠይቅ ። »
« ከውጭ ነው የሚበሉት. ...ጌታዬ ። የሚሔዱበት ሰረገላ ከደጅ እየጠበቃቸው ነው።

« መልካም ......... ሚስተር ካርላይል ፡ እንግዲህ እኛው ብቻ ነን ያለን ! አለ የቤቱ ጌታ።

ራት በአንድ ሰዓት ቀረበ ። ዊልያም ቬን በተሽከርካሪ ወንበሩ ሆኖ ወደ ምግብ
ቤት እየተገፋ ሔደ ። ከእንግዳው ጋር በአንዱ በር ሲገቡ ከፊት ለፊታቸው በነበረው በር ደግሞ ሌላ ሰው ገባ ። ለሚስተር ካርላይል የታየው ሰው ይሁን መልእክ ተጠራጠረና ልብ ብሎ ተመለከተ።

በሠዓሊዎች ሐሳብ ከሚታየው በቀር እጅግ ጥቂቶች ብቻ የታደሉት ቁንጅና
ከምንለው የላቀ መልክ ያላት ልጅ ነበረች። ከጫፉ እንደ ቀለበት ጥቅልል ጥቅል ያለው ጥቁር ጸጉሯ ከአንገቷና ከግራ ቀኝ ትከሻዋ ላይ ወርዶ ተቆልሏል ከለስላሳ የልጅ ክንዶቿ ላይ የሉል ጌጥ አስራ ውድ የሆነ ነጭ የዳንቴል ሥራ ቀሚስ ለብሳ ከፊት ለፊታቸው ብቅ ስትልበት መልአክ ትሁን ሰው ለመለየት ተጠራጠረ።

« ልጄ ናት ሚስተር ካርላይል ። እመቤት ሳቤላ ቬን» ብሎ አስተዋወቀው ። ሁሉም ከምግቡ ገበታ ዙሪያ ተቀመጡ ። ዊልያም ቬን የተለመደ የክብር ቦታውን ያዘ ። ልጅቱና ሚስተር ካርላይል ፊት ለፊት ሆነው ቁጭ አሉ ።

ሚስተር ካርላያል ለሴት ልጅ መልክ እደነግጣለሁ ብሎ አያስብም ነበር ።
የዚያች ቆንጆ ልዩ ውበት ግን ጠቅላላ መንፈሱን ማረከው ። ራሱን መቈጣጠር
እስኪሳነው ድረስ አፈዘዘው ። ከሁሉ የበለጠ ያስደሰተው ደግሞ ቅርፆ መልካም ፊቷ ወይም ትከሻዋ ላይ የተኛው ጸጉሯ ወይም የጽጌረዳ አበባ የመሰሉት ለስላሳ ጉንጮቿ ሳይሆኑ የዐይኖቿ አገላለጥ ነበር ። ከዚያ በፊት ያን የመሰለ አጋጣሚ አይቶ ስለማያውቅ ዐይኖቹን ከገጿ ላይ ሊነቅል አልቻለም ።

"ሳቤላ.... ለብሰሻል' አይደለም? » አላት አባቷ ።

« አዎን.....አባባ ። ባልቴቷን ሚሲዝ ሌቪሰን ለሻይ ብዙ እንዳይጠብቁኝ ልሔድላቸው ነው ። እሳቸው ለራሳቸው ሻያቸውን በጊዜ መጠጣት ነው የሚፈልጉ። ቢያመሹ አይወዱም ። ሚሲስ ቬንም ከዚህ ስትነሣ ዐሥራ ሁለት
ሰዓት ዐልፎ ስለነበር ለራት ሳታስጠብቃቸው አትቀርም ። »

« ብዙ እንደማታመሺ ተስፋ አለኝ ሳቤላ » አለ አባቷ ።

« እንደ ሚሲዝ ቬን ሁኔታ ነዋ አባባ እሷ ካላመሸች አላመሽም ። »

"አየ እንግዲያውስ ማምሸትሽ አይቀርም መቼም በዚ በኛ ዘመን ቆነጃጂቱ ሌሊቱን ወደ ቀን እየለወጡት ነው ። ይኸ ደግሞ ለለጋው ዕድሜያቸው ደግ አይደለም ። አንተስ ምን ይመስልሃል ሚስተር ካርላይል ? »

ሚስተር ካርላይል ቀና ብሎ ወደ እሷ ተመለከተ። ጉንጮቿ በበለጠ ደምቀው በቀላሉ የማይጠወልጉ ጽጌ ረዳዎች መስለው ታዩት ።

ራት ተበልቶ እንዳበቃ አንዲት የቤት ሠራተኛ ከሱፍ የተሠራ መደረቢያ ይዛ
ገብታ ከወጣቲቱ እመቤት ትከሻ ላይ ጣል አደረገችላት ። ልጂቱም ወደ አባቷ ቀረብ ብላ «ደኅና አምሽ ......... አባባ » አለችው

"ደና አምሺ........ የኔ ዓለም » አላት ወደሱ ሳብ አድርጎ የሚያምረው ጉንጯን ሳመና « እስኪነጋ ድረስ ውጭ መቆየትሽን እንደማልፈልግ ለሚሲዝ ቪን ንገሪያት " አንቺ ለራስሽ ገና ልጅ ነሽ እስኪ መጥሪያውን ንካው ሚስተር ካርላይል ። ልጄን ከሠረገላው ድረስ መሸኘት እንኳን አቃተኝ። »

« የእርስዎ ፈቃድ ከሆነና እመቤት ሳቤላም ወጣት ሴቶች አስተናግዶ የማያ
ውቅ እንደኔ ያለ ሰው እንዲሽኛት ከተስማማች አሳፍሪያት ብመጣ ደስ ይለኛል »አለ ትንሽ እንደ መደናገጥ ብሎ መጥሪያውን እየደወለ ።

ዊልያም ቬን አመሰገነው ። ወጣቷ እመቤትም ፈገግታ አሳየችው ። ሚስተር
ካርላይልም መብራቱ በተንጣለለበት ደረጃ እየመራ ይዟት ወረደና ከሚያምረው ምቹ ሠረገላ ውስጥ ደግፎ አስገባት ። እጅዋን ዘርግታ ሰላምታ ሰጠችውና ሠረገላው መሽከርከር ሲጀምር ካርላይልም ወደ ዊልያም ቬን ተመልሶ ገባ ።

« ታድያስ ቆንጆ ልጅ አይደለችም : ሚስተር ካርላይል ? »

« ቁንጅና የሚለው ቃል ያንሳታል ። የሷን ያህል ቆንጆ አይቼ አላውቅም ። »

« ባለፈው ሳምንት ከአንድ ግብዣ ሔዳ ነበር ። ሕዝበ አዳም አዳራሹ ውስጥ
ሲያያት ጊዜ ልዩ ስሜት ተፈጥሮ ነበር አሉ እኔማ መቼም ይህ ክፉ ቁራኛ በሽታ
ኮድኩዶ ከቤት አዋለኝና ያንን እንኳን ለማየት ሳልታደል ቀረሁ ። ልጂቱ ልቧም
እንደ መልኳ ነው ፤ እንዲህ አትምሰልህ ፤ ጥሩ ሰው ናት ። »

አባትየው የተናገረው ፡ ልጁ በመሆኗ ለማስወደድ ብሎ ሳይሆን ከልቡ ነበር ።
ሳቤላ ፡ በአስታሳሰብና በትክለ ሰውነትዋ ብቻ ሳይሆን በደግነቷም መስል አልነበራትም ።

ታርማና ተመክራ ነው ያደገችው ። ከቤት ውጭ ምንም ነገር አይታ አታውቅም ። እንደ ዘመኑ ልጆች ቅብጥብጥና ቅንጦት ወዳድ ሳትሆን ፡ ረጋ ያለች ጨዋ ልጅ ነበረች ። እናቷ በሕይወት በነበረች ጊዜ አንዳንዴ ኢስት ሊን፡ አብዛኛው ጊዜ ግን ማውንት እስቨርን ነበር የምትቀመጥ ። ከእናቷ ሞት በኋላ ከአንዲት አስተማሪ ጋር ወደ ማውንት እስቨርን ጠቅላ ገባች ። አባትየው አንድ የሟላ ትንሽ ቤት ሰጥቶ ዐልፎ ዐልፎ ያያቸው ነበር ። ሳቤላ ዐይነ አፋርና በመጠኑም ስሜት ንቁ አደብ የገዛች፡ ለሁሉ አሳቢና ተጨናቂ ነበረች ። አባቷም በጣም ስለሚወዳት መከራ ላይ ወድቃ ከሚያያት እሱ ራሱ ቢገድላት ይመርጥ ነበር ።

የወይዘሮ ሳቤላ ቬን ሠረገላ ጉዞውን ቀጥሎ ከሚስዝ ሌቪሰን መኖሪያ ቤት
አወረዳት ። ሚስዝ ሌቪሰን ጠባይዋ ልዝብ' አንደበቷ ስትር ያለ ሰማኒያ ዓመት
የሚሆናት ባልቴት ነበረች ። ሚሲዝ ቬን እንደ ተፈራው ዘግይታ ደረሰች ባልቴቷ
ለራት ብዙ ስለጠበቀች ተበሳጭታ ኖሮ ፡ ኋላ ደግሞ ሳቤላም የሻይ ሰዓት እስኪያ
ልፍ ስትቆይባት ጊዜ በመናደድ ቆቧን እንጋድዳ ደፍታ ኩፍስ ብላ ተቀምጣ አገኘቻት እውነትም እንደዚህ የመሰለ አሠራር ለአረጋውያን ጤንነትም ሆነ ጠባይ አይስማማም ።

« አስጠበቅሁዎ መሰለኝ » አለች ሳቤላ ወደ ሚስዝ ሌቪሰን እየተጠጋች ,
« ከአባባ ጋር ራት የሚበላ አንድ እንግዳ ስለ ነበረ ነው ትንሽ የቆየሁት »

« ኻያ ኣምስት ደቂቃ አሳልፈሻል » አለች ባልቴቷ ቆጣ ብላ ።

«አሁን ሻይ እንዲቀርብልኝ እፈልጋለሁ ።
ኤማ ......... ቶሎ እዘዥልኝ ። »ሚስዝ ቬን ደወለችና እንደ ታዘዘችው ተናገረች ። ይህች ወይዘሮ በመልክ በኩል እንደ ነገሩ ብትሆንም ተክለ ቁመናዋ ያማረ ፡ እና ዕቡይ ከቁመቷ መለስ ያለች የኻያ ስድስት ዓመት ቆንጆ ነበረች ። እናቷ የባልቴቷ የሚሲዝ ሌቪሰን ልጅ ነበረች ፣ ቀደም ብላ ሞታለች ። ሎርድ ( ጌታ)ዊልያም ሼን ወንድ ልጅ አልነበረውምና።ባገሩና በዘመኑ ሕግ መሠረት በወርስ ላገኘው የማወንት እስቨርንን ጉልት ማዕረግና ሀብት ሕጋዊ ወራሽ' የቅርብ ዘመዱ የሆነው ፣ ወንድ ልጅ የርሷ ባል ሬይሞንድ ቬን ብቻ ነበር ።
👍20
#የጣሪያ_ስር_አበቦች


#ክፍል_ሁለት


#ትርጉም_ሀኒም_ኤልያስ

..."ሌላም ነገር ልንገርሽ?" ሲል ጀመረ።በቅርበት እየተመለከተኝ ነው፡ “አርብ አርብ ወደ ቤት ስመጣ ላንቺም ሆነ ለወንድምሽም ምንም ስጦታዎች
ባላመጣላችሁ እንኳን… ሁለታችሁም በመምጣቴ ብቻ ተደስታችሁ እንደ እብድ እየሮጣችሁ እንደምታቅፉኝና እኔን እንጂ ስጦታዎቹን እንደማታስበልጡ አምን ነበር እናታችሁና እኔ በደርዘን የሚቆጠሩ ልጆች ቢኖሩንም እንኳን ሁልጊዜም በልቤ ውስጥ ትልቅ ቦታ እንዳለሽ የምታውቂና ጥሩ አባት በመሆኔ ትወጂኛለሽ ብዬ አስብ ነበር ለካ ተሳስቻለሁ አለ: ከዚያ መናገሩን ቆም አደረገና እንደገና በረጅሙ ተነፈሰ: ሰማያዊ አይኖቹ ደፈረሱ፡ “የእኔ
ካቲ የመጀመሪያ ሴት ልጄ በመሆኗ አሁንም ለእኔ የተለየች እንደሆነች የምታውቅ ይመስለኝ ነበር :"

በተቆጣና በተጎዳ አስተያት አየሁት ከዚያ ሳግ አነቀኝ “ግን እማዬ ሌላ ሴት ልጅ ሲኖራት ለሷም ተመሳሳይ ነገር ትላታለህ” አልኩት።

“እላታለሁ?”

“አዎና” ከመቅናቴ የተነሳ ተንሰቅስቄ ጮህኩ፡ “ትንሽና ቆንጅዬ ስለምትሆን እኔን ከምትወደኝ የበለጠ ትወዳታለህ”
“በጣም ልወዳት እችላለሁ ግን hአንቺ የበለጠ አይሆንም” አለና ክንዶቹን ዘረጋ ከዚህ የበለጠ መቋቋም አልቻልኩም: ከተጋደምኩበት ብድግ ብዬ ደረቱ
ላይ ልጥፍ አልኩና አጥብቄ አቀፍኩት። እቅፉ ውስጥ እንዳለሁ ማልቀሴን እንዳቆም አባበለኝ “አታልቅሺ ካቲ… ቅናት አይሰማሽ፡ የምወድሽ በፍጹም ከእነርሱ ባነሰ አይሆንም: ደግሞ ካቲ፣ እውነተኛ ህፃናት ከአሻንጉሊቶች
የበለጠ ደስ ይላሉ ታያለሽ ትወጃቸዋለሽ፡ እናትሽ ልትይዛቸው ከምትችላቸው በላይ ልጆች ስለሚኖሯት የአንቺን እርዳታ መፈለጓ የማይቀር ነው እኔ ቤት
በማልኖርባቸው ጊዜያት እናትሽ የሁላችንንም ህይወት ቀላል የምታደርግ ውድ ልጅ እንዳለቻት ማወቄ በራሱ ጥሩ ስሜት እንዲሰማኝ ያደርገኛል” አለኝና
ሞቃት ከንፈሮቹ በእንባ የራሰ ጉንጬ ላይ አረፉ። “ነይ አሁን ስጦታሽን ክፈቺና ውስጡ ስላለው ነገር ምን እንደምታስቢ ንገሪኝ አለ።

ስጦታውን ከመክፈቴ በፊት አይኖቹ ውስጥ ላስቀመጥኩት ሀዘን ማካካሻ ፊቱን በሙሉ በመሳም አዳረስኩትና የበለጠ ጥብቅ አድርጌ አቀፍኩት።
በሚያምረው ካርቶን ውስጥ ኢንግላንድ ውስጥ የተሰራ ብርማ ቀለም ያለው ቀ የሙዚቃ ሳጥን ነበረበት። ሙዚቃው ሲጫወት ሮዝ ቀለም ያለው ቀሚስ
የለበሰች አሻንጉሊት መስታወት ፊት እየተሸከረከረች ትደንሳለች።

“የሙዚቃ ሳጥን ብቻ ሳይሆን የጌጥ መያዣም ነው” አለና ካርቶኑ ውስጥ ከነበረች ማስቀመጫ ውስጥ ቀይ ፈርጥ ያለባት የወርቅ ቀለበት አውጥቶ
ጣቴ ላይ አጠለቀልኝ። “ገና ካርቶኑን ሳየው ልገዛልሽ እንደሚገባኝ አወቅኩ።እና በዚህ ቀለበት የኔዋን ካቲ ለዘለዓለም እንደምወዳት ቃል እገባለሁ" አለ።

አባታችን ህፃናቱ እስኪወለዱ ለመጠበቅ ለሁለት ሳምንት ያህል ቤት ነበር።ሁልጊዜ እናትና አባታችን ከባልና ሚስትነት ይልቅ ወንድምና እህት ይመስላሉ
ብላ የምትናገረው ጎረቤት የምትኖረው ወይዘሮ ቤርታ ሲምሰን ወጥ ቤት ውስጥ ሆና ምግብ እያዘጋጀችልን ነበር።

አራት ሰዓት አካባቢ አባታችን ወደምንመገብበት ክፍል እየተጣደፈ ገባና ለእኔና ለክሪስቶፈር እናታችንን ሆስፒታል ይዟት ሊሄድ እንደሆነ ነገረን
“አትጨነቁ፣ ሁሉም ነገር ጥሩ ይሆናል፡ ወይዘሮ ሲምሰንን እንዳታስቸግሯት የቤት ስራዎቻችሁን ስሩ። በጥቂት ሰዓታት ውስጥ ወንድሞች፣ እህቶች ወይም ደግሞ ወንድምና እህት ማግኘታችሁን ታውቃላችሁ።” አለን በማግስቱ ጠዋት አባታችን ከሆስፒታል ሲመለስ ፂሙን ሳይላጨው ልብሱም ተጨማድዶ በጣም የደከመው ቢመስልም በደስታ እየሳቀ “ገምቱ! ወንዶች
ወይስ ሴቶች?” አለን። “ወንዶች!” አለ ኳስ መጫወት የሚያስተምራቸው ወንድሞች የሚፈልገው ክሪስቶፈር፡ እኔም የምፈልገው ወንዶች እንዲሆኑ
ነው የአባቴን ፍቅር የሚነጥቁን ሴቶች ልጆች አልፈልግም:

“ወንድና ሴት ናቸው:: አለ አባታችን በኩራት: “እስከዛሬ አይቻቸው የማላውቃቸው አይነት የሚያማምሩ ፍጥረታት ናቸው: ራሳችሁ እንድታዩዋቸው ኑ ልብሶቻችሁን ልበሱና ልውሰዳችሁ ”

እንዳኮረፍኩ ነው አባታችን ህጻናቱ የተኙበት ክፍል ውስጥ እንዳሉ ማየት እንድችል ወደ መስኮቱ ከፍ አድርጎ ሲያቅፈኝ እንኳን ነርሷ ያቀፈቻቸውን ሁለት ሚጢጢ ህፃናት ለመመልከት እያመነታሁ ነበር በጣም ትንንሾች
ናቸው! ጭንቅላታቸው ከአፕል አይበልጥም: ትንንሽ እጆቻቸው በአየር ላይ ይወናጨፋሉ፤ አንደኛው ደግሞ ልክ በመርፌ እንደተወጋ አይነት ይጮሃል።
አባታችን ጉንጬን እየሳመና ጥብቅ አድርጎ እያቀፈኝ “እፎይ… እግዚአብሔር እንዴት መልካም ነው! ልክ እንደመጀመሪያዎቹ ልጆቼ እንከን የለሽ የሆኑ
ሌላ ወንድና ሌላ ሴት ልጅ ሰጠኝ።” አለ። ሁለቱንም እንደምጠላቸው አስቤ ነበር። በተለይ ኮሪ ተብሎ ከተሰየመ
ዝምተኛ ልጅ በአስር እጥፍ ጯሂ የሆነችውን ኬሪ ተብሎ ስም የወጣላትዐልወዳት እንደማልችል አስብ ነበር። ሁለቱ ከእኔ ክፍል ባሻገር ያለው ክፍብ ውስጥ ከሆኑ ፀጥ ያለ መኝታ የማይታሰብ ነው: ሆኖም ከፍ ብለው ፈገግ ማለት ሲጀምሩና እኔ ስመጣ ወይም ሳቅፋቸው አይኖቻቸው ላይ ያለውን ደስታ ስመለከት የቅናት ስሜቴን ሞቃትና ደስ የሚል የእናትነት ስሜት ሲተካው ታወቀኝ፡ የትምህርት ሰዓት እንዳለቀ እነሱን ለማየት፣ ከእነሱ ጋር ለመጫወት፣ የሽንት ጨርቃቸውን ለመቀየር፣ ጡጧቸውን ለመያዝና እነሱን
ለማቀፍ ወደቤት እጣደፍ ጀመር። እውነትም ለካ ከአሻንጉሊቶች የበለጠ ደስታ የሚሰጡ ናቸው።

እኔ ሁለቱንም ለመውደድ ልቤ ውስጥ ቦታ እንዳለኝ ሲገባኝ፣ ወላጆችም ልባቸው ውስጥ ቁጥራቸው ከሁለት በላይ ለሆኑ ልጆች የሚሆን በቂ ቦታ
እንዳላቸው ተረዳሁ

ትንሽ ጠየም ከሚለው ከአባታችን በስተቀር ሁላችንም ተመሳሳይ የሚያምር የቆዳ ቀለምና ወርቃማ ፀጉር ስላለን፣ የአባታችን የልብ ጓደኛ ጂም ጆንስተን
“የድሬስደን አሻንጉሊቶች” በሚል ቅጽል ስም ይጠራን ነበር እሱን የሰሙ ጎረቤቶቻችንም የሚጠሩን በዚህ ስም ነበር።

መንትዮቹ አራት አመት ሲሆናቸው ክሪስቶፈር አስራ አራት አመት ሞላው"እኔም አስራ ሁለተኛዬን ይዣለሁ። ለየት ያለው አርብ መጣ የአባታችን ሰላሳ ስድስተኛ አመት የልደት ቀን ነው: ድንገት ልናስገርመው ግብዣ አዘጋጅተናል። እናታችን ተጣጥባና ተቆነጃጅታ ተረት ተረት ላይ ያለችውን ልዕልት መስላለች የምግብ ቤቱ ጠረጴዛ በምግቦች ተሞልቶ አሸብርቋል።
ስጦታዎቹ ሁሉ ተደርድረዋል ለቅርብ ወዳጆቻችንና ለቤተሰብ ብቻ የተዘጋጀ ግብዣ ነበር፡

ሁላችንም አምሮብንና ተውበን አባታችን እስኪመጣ መጠበቅ ጀመርን፡አስራ አንድ ሰዓት አለፈ እየጠበቅነው ነው:: የአባታችን አረንጓዴ ካዲላክ መኪና ግን እስካሁን አልመጣም: እናታችን በጭንቀት ክፍሉ ውስጥ
እየተንጎራደደች ነው: የተጠሩት እንግዶች እያወሩ ነው አባታችን በተለምዶ አስር ሰዓት ላይ ይመጣ ነበር፡ አረ እንዲያውም አንዳንዴ ከዚያም ሁሉ ቀደም ይላል። ዛሬ ግን ያለወትሮው በጣም ዘግይቷል።

አንድ ሰዓት ሆነ፤ አባታችን እስካሁን ብቅ አላለም።

እናታችን ረጅም ሰዓት ወስዶባት ያዘጋጀቻቸው ምግቦች ማሞቂያው ውስጥ ብዙ በመቆየታቸው ምክንያት ደረቁ አንድ ሰዓት የመንትዮቹ የመኝታ ሰዓት በመሆኑ እንቅልፋችው መጥቶ እንኳን ሳያዩት ላለመተኛት አስር ጊዜ “አባባ የሚመጣው መቼ ነው?” እያሉ መጠየቅ ጀምረዋል።

እናታችን ወዲያ ወዲህ እየተመላለሰች ደጋግማ በሰፊው መስኮት ወደ ውጪ
ትመለከታለች።

ድንገት የሆነ መኪና ወደ እኛ ግቢ ሲታጠፍ ተመለከትኩና “አባታችን መጣ!” ብዬ ጮህኩ።
👍591
#ጠላፊዎቹ


#ክፍል_ሁለት


#በኬንፎሌት


#ትርጉም_በወንዳየሁ_ንጉሴ

ጦርነቱ የታወጀው የበጋው ወቅት ማብቂያ አካባቢ በአንድ ፀሃያማና ቀለል ያለ እሁድ ነበር፡፡

የጦርነቱ ዜና ሲታወጅ ማርጋሬት ኦክሰንፎርድ ቤት ውስጥ ነበረች፡፡ወደ ቤተክርስቲያን ለመሄድ ተዘጋጂ በመባሏ ጨሳለች፡፡ ከርቀት ያለማቋረጥ
የሚሰማት የቤተክርስቲያን ደወል አሰልቺ ሆኖባታል፡ የ19 ዓመት ልጅ በመሆኗ ስለሃይማኖት የራሷን ውሳኔ መወሰን ብትችልም አባቷ ከቤተክርስቲያን እንድትቀር አይፈቅዱላትም፡፡ ከዓመት በፊት ቤተክርስቲያን መሄድ
እንደማትፈልግ ነግራቸው ነበር፡፡ እሳቸው ግን ጆሮ ዳባ ልበስ ብለዋል።

‹‹በእግዚአብሔር የማላምን መሆኔን እያወቅሁ ቤተክርስቲያን መሄድ
ማስመሰል አይመስልም ወይ?›› አለቻቸው አንድ ቀን፡፡

‹‹ጅል አትሁኚ›› አሏት አባቷ ሎርድ ኦክሰንፎርድ፡
ትልቅ ስትሆን እንደማትሄድ ለእናቷ ነገረቻቸው፡፡
‹‹ባልሽ ይጨነቅበት የኔ ማር›› አሏት እናቷ፡፡ ከዚያ ቀን በኋላ ስለዚሁ ጉዳይ ተነጋግረው ባያውቁም እሁድ በመጣ ቁጥር ማርጋሬት ጥላቻዋ
ይጠነክራል፡

እህቷና ወንድሟ ከቤት ሲወጡ ሰማች። ኤልሳቤት 21 ዓመቷ ነው፡፡ ቁመቷ የብቅል አውራጅ ሲሆን መልክ አልፈጠረባትም፡፡ በልጅነታቸው እህትማማቾቹ ምስጢረኞች ስለነበሩ አይለያዩም፡፡ ካደጉ በኋላ ግን ተራራቁ፡፡
ትምህርት የተማሩት እንደሌሎች እኩዮቻቸው ትምህርት ቤት ሄደው
ሳይሆን አስተማሪ ተቀጥሮላቸው ቤት ውስጥ ነው፡ ኤልሳቤት በጉርምስና
ጊዜ የምታራምደው የወላጆቿን ግትር ልማዳዊ አስተሳሰብ ነበር፡፡
አመለካከቷ አክራሪ ሲሆን ከመኳንንት ዘር በመገኘቷ በእጅጉ ትመካለች፡
አዳዲስ ሃሳቦችና ለውጥ ጠላቶቿ ናቸው፡፡ በአንጻሩ ማርጋሬት የእሷ ተቃራኒ ናት፡ የሴቶች መብት ተሟጋችና የሶሻሊስት ፖለቲካ አቀንቃኝ
ስትሆን ጃዝ ሙዚቃ ትወዳለች፡ ኤልሳቤት ማርጋሬት ተራማጅ አስተሳሰብ በማፍቀሯ ለወላጆቿ ታማኝ አይደለችም ብላ ታምናለች፡፡ ማርጋሬት ደግሞ በእህቷ ጅልነት ትናደዳለች፡፡ በዚህ ምክንያት የልብ ወዳጆች ባለመሆናቸው ታዝናለች፡፡ የልብ ጓደኞች ደግሞ የሏትም፡፡

የእሷ ተከታይ ፔርሲ 14 ዓመቱ ነው፡፡ ተራማጅ ሃሳቦችን ወይ አይወድ ወይ አይቃወም፡፡ በተፈጥሮው ሸረኛ ነው፡፡ የማርጋሬት አመጸኝነት ባህሪ ግን ደስ ይለዋል፡፡ በአባታቸው አምባገነንነት ሁለቱም ተጎጂዎች በመሆናቸው ይተዛዘናሉ፣ ይደጋገፋሉ፡ ማርጋሬትም ለእሱ ልዩ ፍቅር አላት፡

ሎርድና ሌዲ ኦክሰንፎርድ ቀድመው ከቤት ወጥተዋል፡፡ ሎርድ
ዥንጉርጉር ክራቫት አስረዋል፡፡ እመቤቲቱ ጸጉራቸው ቀይ፣ ዓይኖቻቸው አረንጓዴ ሲሆን ፊታቸው የገረጣ ነው፡፡ ጌቶች ጥቁር ጸጉራቸው ላይ ሽበት ጣል ጣል አድርጎባቸዋል፡ ፊታቸው ደግሞ እንደ ቲማቲም የቀላ ነው።

ኤልሳቤት የአባቷን ጥቁር ጸጉርና ቅርጸ ቢስ መልክ የያዘች ስትሆን ማርጋሬት ደግሞ የእናቷን ግርጣት ወርሳለች፡ ፔርሲ መልኩ በየጊዜው ስለሚለዋወጥ የማንን መልክ እንደሚይዝ በውል አይታወቅም:

መላው ቤተሰቡ ከግቢው ወጣና በእግር ጉዞ ጀመረ፡፡ ከቤታቸው በአንድ
ኪሎ ሜትር ርቀት ከሚገኙት አብዛኛዎቹ ቤቶችና መሬቱ በሙሉ
የአባትየው ሀብት ሲሆን ይህንን ሀብት ያገኙት ያለምንም ድካም ነው፡
በአገሪቱ ያሉት ባለመሬት ቤተሰቦች በጋብቻ በመተሳሰራቸው የፈጠሩት
ርስት ይኸው ከዘር ወደ ዘር ተላልፎ በአባትየው እጅ ገብቷል፡

በመንደሩ ውስጥ ለውስጥ ተጉዘው ከድንጋይ ጥርብ የተሰራው ቤተክርስቲያን ቅጥር ግቢ ደረሱ።
ከዚያም አባትና እናት ከፊት፣ማርጋሬትና ኤልሳቤት በመከተል ፔርሲ ደግሞ ከእነሱ ኋላ ተከታትለው
ገቡ፡ የኦክሰንፎርድን መሬት የተከራዩ ገበሬዎች በአክብሮት እጅ ነሷቸው፡
ማርጋሬት ይሄ ኋላቀር ልማድ ሲፈጸም ስታይ በእፍረት ትሽማቀቃለች፡
‹‹ሁሉም ሰው በእግዜር ፊት እኩል ነው! በይ በይ ይላታል፡፡ አንድ ቀን
ድፍረቱ ይኖራትና እዚያ ሁሉ ሰው ፊት ትናገር ይሆናል፡፡ ነገር ግን አባቷ
የሚያደርሱትን ነገር ስታስብ አስፈራት፡፡

የሰው ሁሉ አይን እየተከተላቸው ቤተክርስቲያኑ ውስጥ የቤተሰቡ መቀመጫ ጋ እንደደረሱ ፔርሲ አባቱን ‹‹ክራቫትህ ታምራለች አ
አላቸው፡፡ ማርጋሬት ይህን ስትሰማ ሳቅ አፈናት፡፡ እሷና ፔርሲ ቶሎ ቁጭ አሉና ሳቃቸው እስኪጠፋ የሚጸልዩ ለመምሰል ራሳቸውን አጎነበሱ፡
ሰባኪ ወንጌሉ ገንዘቡን በዋዛ ፈዛዛ ስላባከነውና በመጨረሻም ወደ
ቤተሰቡ ስለተመለሰው ልጅ ታሪክ አስተማሩ፡፡ ማርጋሬት ጨርጫሳው ቄስ!
በእያንዳንዱ ሰው ጭንቅላት ውስጥ ስለሚጉላላው ጦርነት ቢሰብኩ ምናለ
ስትል አሰበች፡፡

።።።።።።።።።።።።።።።።።።።

የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር ለሂትለር ማስጠንቀቂያ ቢልኩለትም
ሂትለር ማስጠንቀቂያውን ከምንም ባለመቁጠሩ የጦርነቱ እወጃ የማይቀር
ሆነ፡

ማርጋሬት እንደ ጦርነት የምትፈራው ነገር የለም፡፡ የእስፓኒሽ እር በእርስ ጦርነት ፍቅረኛዋን ነጥቋታል ዓመት ያለፈው ቢሆንም ትዝ ሲላት
ትሳቀቃለች፡፡ ጦርነት ለሷ አስጨናቂ ነው።

በሌላ በኩል ደግሞ ጦርነትን ትሻለች፡፡ ለብዙ ዓመታት በእስፓኒሽ
ጦርነት እንግሊዝ ያሳየችው ቦቅቧቃነት ያሳፍራታል
በሂትለርና በሙሶሊኒ
የታጠቁ ወሮበሎች የተመረጠውን ሶሻሊስት መንግስት ሲገለብጡ አገሯ ዳር ቆማ ተመልክታለች፡፡ በሺህ የሚቆጠሩ ሶሻሊስት ወጣቶች ከመላው አውሮፓ
ዲሞክራሲን ለመታገል ወደ ስፔን ዘምተዋል፡፡ ነገር ግን በቂ መሳሪያ አልነበራቸውም፡፡ በመላው ዓለም ያሉ ዲሞክራቲክ መንግሥታት ፊታቸውን ቢያዞሩባቸውም ወጣቶቹ ግን ህይወታቸውን ሰዉ፡፡ እንደማርጋሬት ያሉ ሴቶችም
አንገታቸውን በሃዘን ደፉ፤ እፍረትንም ተከናነቡ፡፡ ብሪታንያ ፋሺስቶችን
ተቃውማ ብትነሳ ማርጋሬት በአገሯ እንደገና እንደምትኮራ ተማመነች፡፡

የጦርነቱ አይቀሬነት ልቧ ውስጥ ሌላም ደስታ አጫረባት፡፡ የዚህ ነፃነት
የሌለውና የተጨናነቀው የቤተሰብ ህይወቷ ማብቂያ ይሆናል ስትል አሰበች፡
ይሄ ከጊዜ ወደ ጊዜ ለውጥ የማይታይበት ልማዳዊና ትርጉም የለሽ አኗኗሯ
አንገቷ ጋ ደርሷል፡ ከዚህ አሰልቺና ተስፋ አስቆራጭ ማህበራዊ ሕይወት
አምልጣ ወጥታ የራሷን ህይወት ለመኖር ፈልጋለች። ነገር ግን የሚሆን
የሚሆን አልመስልሽ ብሏታል፡፡ ዕድሜዋ ገና ነው ቤተሰቧን ለቃ ለመውጣት አይፈቀደላትም፡፡ ገንዘብም የላትም፡፡ ለየትኛውም የስራ ዓይነት ደግሞ ብቁ አይደለችም፡፡ ነገር ግን በጦርነት ጊዜ ሁሉ ነገር የተለየ ይሆናል ስትል አሰበች፡፡

ባለፈው ጦርነት ወቅት ሴቶች ሱሪ ታጥቀው ፋብሪካ ውስጥ እንዴት
ይሰሩ እንደነበር በአድናቆት አንብባለች፡፡ ባሁኑ ጊዜ ምድር ጦር፣ ባህር ኃይልና አየር ኃይል የሴቶች ቅርንጫፍ አላቸው፡ ማርጋሬት ምድር ጦርን
መቀላቀል ፈልጋለች፡ አንድ የምታውቀው ስራ መኪና መንዳት ብቻ ነው፡
የአባቷ ሾፌር መኪና መንዳት አስተምሯታል፡ የሞተው ፍቅረኛዋ ሞተር
ሳይክል አስነድቷታል፡ የሞተር ጀልባ መንዳት አያቅታትም፡ የምድር ጦር
መምሪያ የአምቡላንስ ሾፌሮችንና ፖስታ አመላላሽ ሞተር ሳይክል ነጂዎችን
ይፈልጋሉ፡ ዩኒፎርም ለብሳ ብረት ቆብ አድርጋ በሞተር ሳይክል ከጦር ሜዳ ወደ ጦር ሜዳ እየበረረች አገልግሎት መስጠት እንደምትችል እርግጠኛ ሆናለች፡
👍24👎1🔥1
#ከቡስካ_በስተጀርባ
   #ድንግል_ውበት


#ክፍል_ሁለት


#በፍቅረማርቆስ_ደስታ


ከኢትዮጵያ ጥናትና ምርምርና ከሌሎች ተቋማት ለጥናቷ
አስፈላጊ የሆኑትን ውጤቶች ካነበበችና ከግለሰቦች ጋር ሐሳብ
ለሐሳብ ከተለዋወጠች በኋላ እግረ መንገዷን ሊረዳት የሚችል የክልሉ ተወላጅ አድራሻ፣ የጥናትና የጕዞ ፈቃድ አውጥታ ወደ
ጥናት ቦታዋ ከመጓዟ በፊት ምሽቱን በአዲስ አበባው ሒልተን እንግሊዝ ኤምባሲ ከሚሠራውና ለተወሰኑ ወራት በአዲስ አበባው
ቆይታዋ ጠረኑን ከለመደችው ጓደኛዋ ጋር እቅፉ ውስጥ ስትንቀሳቀስ
አድራ እንደገና ገላዋን ታጠበችና ልብሷን ለባብሳ ወጣች"

በአስተሳሰቧ፣ በግልጽነቷና በውበቷ የነሆለለው ስቲቭ
አለባበሷን፣ ከሰዓታት በፊት ፍቅር አመንጪ የነበረው አካሏ ተለውጦ ለሥራ መዘጋጀቷን ሲያይ እሱ ፍቅር ከፈጠረው የደስታ
ዓለም ከነበረበት ፈጽሞ ሳይንቀሳቀስ እሷ ግን ገስግሳ ወደ ገሐዱ
ዓለም በመመለሷ በፍጥነቷ ተደንቆ በተመስጦ ሲመለከታት ቆየና፣

«የኔ ቆንጆ አሁንም ታምሪያለሽ» አላት።

«ማማሬን እርሳው» አለችው።

«ለምን?»
«ከጥቂት ሰዓታት በፊት እኔም እረስቸዋለሁና።»

«የኔ ቆንጆ፣ ታዲያ ምን እንድልሽ ትፈልጊያለሽ?»

«የጉጉትን ዘዴ፣ የንስርን ማስተዋል፣ የአንበሳን ልብ፣ የኢዮብን ትዕግሥት፣ የአባትሽን ተስፋ አይቆርጤነትና አእምሮ ይስጥሽ በለኝ» ብላ፣ ጉንጩን ሳም አደረገችው"

ስቲቭ አስተያየቱን ጠለቅ አድርጎ ሲያስተውላት ቆየና፣ «አሁን አንችን የመሰለ ውብ ከእነዚያ ዘላኖች...» ሊናገር የፈለገውን ሳታስጨርሰው አፉን በአመልካች ጣቷ ከደነችው።
«ማፍቀር ያለብህ እኔን ብቻ ሳይሆን ፍላጎቴንም እንዲሆን እፈልጋለሁ" ትልቁ ውበት ደግሞ ሥራ መሆኑን አትዘንጋ» አለችውና ሌላ ቃል ሳይለዋወጡ ለቁርስ ክፍሉን ቆልፈው ወጡ"
  ።።።።።።።።።።።።።
ፈርጠም ያለ፣ የቀይ ሽንኩርት ቅርፅ መሳይ አፍንጫ ያለው! ዳጐስ ብሎ ቀላ ያለውን ከንፈሩን ሲገልጥ ነጫጭ ፍልጥ ጥርሶቹ የሚያማምሩና ከሸበላው ቁመናው ጋር የተስተካከለ አቋም ያለው
ከሎ ሆራ ለየት ያለ ባሕርይ ይታይበታል።

ቁጥብነቱን፣ ጅንንነቱን፣ ጥርጣሬውንና ብቸኝነት መውደዱን ያዩ ጓደኞቹ፣ «ነብሮ» ይሉታል የዩኒቨርሲቲ ጓደኞቹ" ቀልድ፣
ቧልት ከጀመሩለት እንደ ቆሰለ ጎሽ በንዴት ጦፎ ይፎገራል" ከሰው ጋር ደጋግሞ እንደ መጣላቱ ግን ኃይሉን ተማምኖ ተማቶ
አያውቅም" ሁለቴ ሦስቴ ቃጥቶ ቃጥቶ ማንም በማይገባው ቋንቋ
አኩተምትሞ ዘወር ይላል" ታዲያ ብዙዎቹ አዳልጧቸው ቀልድ ብጤ ጀማምረው በዚያ ፈርጣማ ጡንቻው በሰነዘረ ቁጥር ጠረመሰን
እያሉ አንዴ ከተሳቀቁ፣ «እርም» ብለው ይሸሹታል" ስለዚህ ምን እንደሚያበሽቀው ያለፈው ሕይወቱ ምን እንደሚመስል፣
ብቸኝነቱ ከመቼ ወዲህ እንደ ጀመረው ከፍቶ ማየት የሚችል ሰው አልተገኘም ግለቱ ስላላስቀረበ"

የተማሪን ቆብ አውላቂ መምህራን በለመዱት ቧልት «ጢብ ጢብ» ሊጫወቱበት ይዳዳቸውና እንደ ከለመዳሪ የሚነፋውን
ከንፈሩንና እሳት ተፊ ትናንሽ ዓይኖቹን ሲያዩ በተለይም
በአንቀሳቀሰው ቁጥር እንደ አሎሎ የሚንከባለለውን ጡንቻውን ሲመለከቱ! «በቸር አውለኝ» ብለው አቅጣጫቸውን ሲቀይሩ
ዓመታት ተቈጠሩ“

ከሎ ሆራ የአራተኛ ዓመት የሶሲዮሎጂ ትምህርቱን ሊያጠናቅቅ በተቃረበበት ወቅት በቀጭን ወገቧ ጂንስ ሱሪዋን በቀላል «ቲሸርት» አስተካክላ ለብሳ፣ የተጐነጐነ ረዥም ጸጕሯን ወገቧ ላይ እያላጋች፣ ቶሎ ቶሎ በመራመድ ጫማዋን ቀጭ ቋ ቀጭ ቋ እያደረገች የምትገሰግሰው ወጣት ከዩኒቨርሲቲው ፖስታ ቤት ወረድ ብሎ ከሚገኘው ኮሪደር ጫፍ ላይ ቁጭ ብሎ እግሩን እያወዛወዘ!
ጠጠር ወደሚወረውረው ጥቁር ወጣት ተጠግታ፣ «ይቅርታ ከሎ ሆራ ነህ አይደለም?» ብላ ጠየቀችው፣ በእንግሊዝኛ"

«አዎ ነኝ» አለ ከሎ፣ ከተቀመጠበት ሳይንቀሳቀስ"

«ካርለት አልፈርድ እባላለሁ" እንግሊዛዊት አንትሮፖሎጂስት
ነኝ" ስለ ሐመር ሴቶች ጥናት ለማድረግ ዓላማ አለኝ" አንተም የሐመር ተወላጅ መሆንህን ከዲፓርትመንትህ ኃላፊ ጠይቄ አረጋግጫለሁ» አለችና ንግግሯን በመግታት ትኵር ብላ ተመለከተችው
ከሎ ሆራ፣ የመርበትበት ስሜት አሳየና ከተቀመጠበት ፈጥኖ ተነሣ
ላብ ከወደግንባሩና ቅንድቡ አካባቢ ችፍፍ ችፍፍ ሲል ከንፈሩ አመድ የነሰነሱበት መሰለ።

«ሶ ለምን ፈለግሽኝ?» አላት በተቆራረጠ ድምፅ
«እንድትረዳኝ እፈልጋለሁ» አለችው፣ በዓይኗ እየመረመረችው
«እንድትረዳኝ እፈልጋለሁ?» ብሎ አባባሏን ደገመና ለትንሽ ጊዜ የመመሰጥ ሁኔታ አሳይቶ፣

«አዝናለሁ፣ ልረዳሽ አልችልም» አላት"

ካርለት፣ የከሎ ሰውነት ሲለዋወጥና ከብስጭቱ ጋር ሲታገል ያስተዋለች መሰላት ስለዚህ ወጣቱ ከሷ ያለበለዚያም ራሱ ከራሱ
ጋር ያልተግባቡት ወይንም ለእሷ ግልጽ ያልሆነላት ሌላ ምክንያት እንዳለው በመረዳቷ ተጨማሪ ጥያቄ ሳታነሣ፣ «አመሰግናለሁ“ ነገ
ግን ጊዜ ወስደህ ካሰብክበት በኋላ ሐሳብህን ከቀየርክ አይ.ኢ.ኤስ
ልታገኘኝ ትችላለህ ካለዚያም ስልክ ቁጥሬን ልሰጥህ እችላለሁ» ብላ፣ ፍጹም ልብ በሚነካ ፈገግታ የአድራሻዋን ካርድ ሰጥታው
«ደህና ሁን» እያለች፣ እጇን አውለብልባለት ሄደች"

ከሎ ሆራ ወደ መቀመጫው ሲመለስ፣ የሚሰበቀውን ወገቧንና ጀርባዋ ላይ ከብለል  ከብለል የሚለውን ጉንጉን ጸጕሯን ሲመለከት
ሐሳቡ ሸፈተበት" ከዓይኑ እስክትሰወር ድረስ በመደመም ሲመለከታት ቆየና ከጥቂት ደቂቃ በፊት የነበረበትን ድንገተኛ ሁኔታ ለማስታወስ ሞከረ» «ሐመር ጥናት ውብ እንግሊዛዊት የሐሳብ
ፍጥጫ፣ የተዳፈነ እሳት ጭረት.እሳት ጫሪ አንትሮፖሎጂስት...ወጣትና ውብ...ዳሚት» አለ፣ እጆቹን ከተቀመጠበት ደረጃ
ጋር እያላተመ።
  ።።።።።።።።።።።።።
ልቡ የአዶከበሬ አታሞ ይመስል እየተነረተ፣ ሰውነቱ ፀሐይ እንዳቆረናው የበረሃ ባልጩት ድንጋይ እያተኮሰ፣ እንቅልፍ ሲመኝ ግን ሲነቃ፣ ዕረፍትን ሲሻ፣ ሲንጠራወዝ፣ ሲገለባበጥ፣ በሐሳብ
ሲድህና ፎቀቅ ፎቀቅ ሲል አድሮ ዋለ"

ብዙ አወጣ አወረደI ያለፈ የልጅነት መጥፎ ትዝታውንም አስታወሰ" አሁን ሊያደርግ የማይፈልገውን እንዲያደርግ ግብዣው
ቀርቦለታል" ሌላው ቀን አልፏል። ለዛሬ ሥሩ ትናንት ነው" ትናንት ደግሞ እሱ የመከራ ጽዋውን የጨለጠበት ወቅት ነው" ዳግመኛ ሬት ሊያወርድ የሚችል ጉሮሮ የለውም” ስለዚህ በትናንት ቂም ያረገዘው አእምሮው አጓርቶና ድብልቅልቁ ወጥቶ እንዲሟሟና እንዲተን
ይፈልጋል" ችግሩ እንዳሰበው ለማድረግ አቅሙ አለ ወይ ነው።

የልጅነት ጊዜው መጥፎ ትዝታ ጥርሱን አግጥጦ፣ ጥፍሩን በማሾል፣ የታባክ ይለዋል“ ይኸኔ እንደ ልጅነቱ ልጅ ይሆንና በጭንቀት እየተንቦራቸ ይርበተበታል" ሊጮህ ይፈልግና ድምፁ
አልወጣልህ ይለዋል" ትናንት ከገደል ውስጥ ወጥቷልI ዛሬ ግን ወደ
ገደል ተገፍቶ ለመግባትና ለመሞት ዝግጁ አይደለም" መሞትም አይሻም ለምን?

እንግዲህ ችግሩ ያለው በትናንትናና በዛሬ መካከል ነው" ልጅ ከነበረው ከሎና አሁን በአካልና በአእምሮ ካደገው ከሎ መካከል
አንዱ ሽሽቱን ማቆምI አለበለዚያም፣ «በደንባራ በቅሎ ቃጭል ተጨምሮ» እንዲሉ፣ በፍርሃት ላይ የጅብን ፍርሃት እያከለ ወደ ኋላ ሳያይ የሕይወትን ሩጫ መሸምጠጥ አለበት።

ትንሹ ከሎ ማምለጥ፣ መሸሽ ይፈልጋል ከሐመር። ትልቁ ከሎ ደግሞ ልቡ ከሁለት ቦታ ተንጠልጥሎበታል" ከሎ ውሳኔው ሲከብደው ካርለት ከተወችለት ካርድ ላይ በብዕር የተጻፈውን ስልክ
ቁጥር ተመልክቶ ስልክ ደወለ" «ሔሎ ከሎ» አለችው እንደ ሕፃን
ተቁነጥንጣ።

«...ደህና ነኝ» አላት"
«ምነው ልትገልጽልኝ የምትፈልገው ጉዳይ አለ?» አለችው።

«ለመሄድ ፈቃደኛ ነኝ» አለ ከሎ።
👍29
#ኢቫንጋዲ


#ክፍል_ሁለት


#በፍቅረማርቆስ_ደስታሰ


ሰማዩ እንባውን አንዠቅዥቆ ወጣለት: ጀንበር ግን እሷ
እየነደደች ጮራዋን እንደገና በሐመር ተራሮች አሾልካ ፈነጠቀች ዳመናዎችም እንደገና ተበታትነው ለዓመፅ ምክር ይዘዋል  በድጋሚ
ሰማዩን ለማስለቀስ ምድሯን ለማጨቅየት...

ወፎች እጅብ ይሉና ቁልቁል ደሞ ሽቅብ ይጎኑና ቀስ በቀስ ሰማዩ ውስጥ ገብተው ይጠፋሉ።

“እምቡዋ...እምቡዋ… የሚያማምሩትና
ቆዳቸው የሚያብለጨልጨው
እንበሶች ቃጭላቸውን እያቅጨለጨሉ ልብ
በሚበላ ልጅነትን በሚያስታውስ ዜማ ይጣራሉ: ጎይቲ የነሱን
ድምፅ ስትሰማ ተብረከረከች።

የተወለደችው ከጥጃ ጋጥ ጎን የተንቦራቸችው ከነሱ ፍግ ላይ የመቦረቂያ ዜማዋ የነሱ ድምፅ ጣፋጩ የልጃገረድነት ድሪያ
ከነሱ ፊት ... ያ ተመልሰው የማያገኙት የልጅነት ዘመን ያለፈው ከእነሱ ጋር... ጎይቲ ከእንስሳት ሁሉ ጥጆችን ከወንዶች ሁሉ ያን ልቧን እያዳመጠ የሚያባዝታትን ፈትሉ ፍቅር የሚያለብላትን
ነፍሷን በሐሴት የሚያንበሸብሻትን ደልቲን ይናፍቃል::

ሲያቀብጣት ከሐመር ቀዬ ከጭፍራው ቦታ ከተፈጥሮ
መኝታ ቤቷ ከምትንተራሰው የደልቲ ክንድ ርቃ የጨረቃና
ከዋክብት ውበት ከማይታይበት የዱር ፍሬ ለቅመው ከማይበሉበት
የእንስሳት ቡረቃ
ከማይታይበት እየሳቁ እየተጫወቱ
ቡና ከማይጠጣበት. አገር ቆይታ እንደ ውሃ የራባትን የአባቷን ባህል
ደልቲን ለማየት ቀን ተሌት አልማ ስትመጣ ሁሉንም እንደነበረ ስታገኘው ጀግናዋን አጣችው ያኔ የሐመር ጫካ የከስኬ አሸዋ
የቡስካ የአስሌ ተራራ ባዶ ሆነባት::

"...በሉ ተዉኝ! እኔማ ተናግሬያለሁ! ጀግና እድሜ
የለውም የጀግና ልብ ቶሎ ይቀየማል  ጀግናም ምድሪቱን ታፈቅረዋለች መከታነቱን ትፈልገዋለች'  ብዬም አልነበር!
ሳልሰናበተው አያ ደልቲ' ብዬ ስንቅ የሚሆነውን ፍቅሬን ጉያው ውስጥ ሳልወሽቅለት ፍቅሬን በአስተቃቀፌ ጥንካሬ ሳላሳየው ምርቃቱንና የፍቅር ስንቄን ሳልቀበለው ነፍሴን ባስደስታት ደረቱ
ላይ ራሴን ደገፍ ሳላደርግ! ሳብ ገፍተር በሚያደርገኝ ልቡ እንደ ቂጠማ ጎንበስ ቀና ሳልል እሱ አየሩን ሲቀዝፍ እኔ ዳሌዬን
እያሽከረከርኩ ዳንኪራ  ሳልረግጥ አምሮቴ ሳይወጣልኝ የፍቅሩ
ጣዕም ዝንተ ዓለም ከጉሮሮዬ የማይጠፋውን የፍቅሬን ጌታ  ላልሰናበተው.

ጎይቲን ሳግ ተናነቃት አይኖችዋን ከድና ስትከፍታቸው እንባዋ ቁልቁል ወረደ እንደ ምንጭ ውሃ ኮለል ብሎ የጠራ
እውነተኛ ፍቅር የተጠመቀ ንፁህ እንባዋ ጠይም ቆዳዋን እየሸረሸረው ቁልቁል ፈሰሰ

ጎይቲ እንደ ውቅያኖስ ከአድማስ አድማስ የተንጣለለው የፍቅር ዘመን መተንፈሻ አሳጥቶ እንደ ውጋት አስቃተታት: አይኗን
ብትከድን ምድር ምድር ሰማይ ሰማይ ብታይ ለውጥ የለም! ሁሉም ቦታ የሚታያት ጮርቃወ ፍቅሯና የፍቅር ጀግናዋ ነው:
ስለዚህ ጎይቲ መድረሻ ጠፋት:: አንበሳዋ ሐመርን ለቆ ጠፋ ጫካ ውስጥ ሆኖ ማግሣቱን አቆመ፡

“.ኧረ ተቃጠልሁ... ኧረ የት ሆኜ ልጥራህ... አያ ደልቲ
አንተ እኔን ብለህ ለአደን ስትሄድ እኔ በምን አቅሜ መንገዱን ይዤ ጢሻውን ጥሼ ጫካ ልግባ." ጎያቲ ወደ ሐመር ተራራ ወደ ቡስካ ፊቷን አዞራ ጮከች! አያ ደልቲ የት ነህ?... ጥቀሰኝ መፋቂያህን
እንደጎረስህ ጥራኝ... የፍቅር ጦርህን ሰብቀህ የተኛ አካሌን ወጋጋው..." ብላ ወደ ሰማይ አንጋጣ ተጣራች፡ ሰማዩ ግን ድምጿን ዋጠው ደልቲን ዋጠው ፍቅሯን ዋጠው….
።።።።።።።።።።።።።።።።።።።
ከሎ ሆራ በህምታ የምትቆዝመውን ጎይቲ ሲያይ ግራ ገባውና

“ጎይቲ” አላት

"ዩ” አለችው ከንፈሯን እያሸሸች ችምችም ብለው
የሚያንፀባርቁ ጥርሶችዋን እያሳየችው።

.እውነት ይህች ፀባዬ ሸጋ ልጅ የተሸከመችው የውበት
መዓት የኔ ነው? አላት እጁን ትከሻዋ ላይ ደገፍ አድርጎ።" እሷም የእጅ ጣቶቹን በሁለት እጆችዋ እየደባበሰች ቀና ብላ የሚያንፀባርቁ
ጥርሶችዋን እያሳየችው “ይአ!  አሁንማ የሰራ አካላቴ ሁሉ የአንተ ነው የኔ ጌታ!
ከኔ በላይ የኔ ባለቤት ነህ። ከእንግዲህ ከልቤ
የማልበው የፍቅር ወተት የአንተን ጥም ቆራጭ ነው..." ብላ ሐዘን
የተቀላቀለበት ፈገግታዋን አሳየችው።

ከሎ ሆራ! “አሁንማ የስራ አካላቴ በሙሉ የአንተ ነው..." ያለችው አባባል ከነከነው፡ ጎይቲ በዚያ የነፃነት ዘመን በሐመር
ወግና ባህል የእሱ ከመሆኗ በፊት እንደ ንብ እየዘመረች በቀሰመችው የአበባ ዘመኗ በምታደርገው  ድሪያ  የፍቅር ወለላ  እየቀመመች
ጣፋጩን ስሜት በጋራ ልሣ በእርካታ የምትንበሽበሽበት ዘመን እሸቱን ፍቅሯን እያሸች ያቃመችው ስው ሌላ ነው። ከሎም ይህን
በሚገባ ያውቃል በሥልጣኔና በተፈጥሮ ህይወት መካከል
የተከፋፈለው ህሊናው ግን የትናንቱን ድርጊት እንዲሰረዝ አሊያም
እንዲደበቅ ይፈልጋል:
የፍርፋሪ ስልጣኔ ያስተማረው የሚፈልጉትን ለማግኘት ስሜትን በረጋግዶ እጅን መዘርጋት! ችግር ሲያጋጥም ደግሞ እጅን መሰብሰብ! ስሜት ሲያስቸግር መከተል፤ ስሜት እንደ እሳተ ገሞራ
ፈንድቶ ሲፈስ መፈርጠጥ መዋሸት ፊት ማዞር... ስሜትን ከህሊናው መስተጋብር ውጭ ማድረግን ነው ያስተማረው  ከሎን።

ጎይቲ ግን ከሚካል አልባውን የከስኬን ውሃ ጠጥታ ማዳበሪያ ያልነው አፈር ያበቀለውን ማሽላ በቆሎ... በልታ ያደገች
አያት ቅድመ አያቶችዋ በተጓዙበት መንገድ በልበ ሙሉነት የምትራመድ ናትና ትናንትን በትናንትነቱ ዛሬን ደግሞ በዛሬነቱ
በሐቅ መዘከር ትመርጣለች። ስለዚህ በህሊናዋ ጓዳ የተቋጠረውን ትዝታ “አካፍይን" ካሏት ካለ ይሉኝታ እየፈታች ታሳያለች:: ሆኖ ያለፈ የደስታና የሃዘን ትውስታ በውስጧ ተከማችቶ እያስደመማት
እያስቃሰታት... እንዳልሆነ እንዳልነበረ ሁሉ የትናንትን ሁሉ  የትናንትን ትውስታ በምላሷ ጫፍ ለማጥፋት መሞከር ሞቷ ነው፡፡
ቅጥፈት ነውር ነዋ! በአባቷ ባህል።

ከሎ “...አሁንማ...”ብላ የተከዘችበት ምክንያት
አልጠፋውም፡ እንደ ወይን ታሽጎ የተቀመጠና በዋለ በሰነበተ ቁጥር ጣምናው እየጨመረ የሚመጣበት የደልቲ ፍቅር እንደሆነ ያውቃል ግን እንደ አዲስ ይጠይቃታል። ያኔም

“ጎይቲ?” አላት

“ዬ!'' አለችው።

“...አሁንማ የሰራ አካላቴ በሙሉ የአንተ ነው... ያለሽኝ ድሮስ ፍቅርሽን ለማን ነበር አልበሽ የምትሰጭው?” አላት:

“ይእ! ኧረ እዩልኝ! አንተ ሰው'' ብላ ከንፈሯ እየተለጠጠ ሲሸሽ እኒያ በረዶ የመሰሉ ጥርሶችዋ ከፊት ለፊቱ ተገጠገጡና
እንደገና ተመልሰው ተሸፈኑ፡፡
አሁን ይህን እውነት አጥተኸው ነው ድሮ ፍቅርሽን የምትሰጭው?!
ያልከኝ! ድፍን ዓለም
የሚያውቀውን! የፍቅሬን እንገር በአገሬ ጫካ እንደ እንቦሳ የጋትሁት
ለአያ ደልቲ መሆኑ እውነት አሁን ጠፍቶህ ነው። እንጥፍጣፊ ሳላስቀር ፍቅሬን ሳጠባውና ጀግናዬ ግዳዩን እንደ ባልጩት ድንጋይ በለሰለሰው ጭኑ ላይ አስቀምጦኝ ሲያገሳ ነፍሴ በደስታ ትበራለች:
ከዚያ አይኑ ላይ የተሰካውን አይኔን ሳልነቅል ቁልቁል
እንሽራተታለሁ..." ብላ የጎይቲ አይኖች ቡዝዝ ሲሉ ከሉ ሆራ እሷን የራሱ ለማድረግ በሐመር ባህል መሰረት ጫካ ለጫካ ሲዞር ግራር ዛፍ ስር ደልቲና እሷ መርፌና ክር ሆነው ሲወዛወዙ ከወገቡ
በስሜት እየተናጠ ምራቁን እያንጎራጎጨ ግንድ አቅፎ የተሻሸበትን ጊዜ አስታወሰና ቅናት ውስጡን እያተራመሰው፡-

“ከተንሽራተትሽ በኋላስ?” አላት ሳያስበው፡
👍403🥰2