አትሮኖስ
286K subscribers
118 photos
3 videos
41 files
569 links
╔╦╦╦═╦╗╔═╦═╦══╦═╗
║║║║╩╣╚╣═╣║║║║║╩╣
╚══╩═╩═╩═╩═╩╩╩
ግጥሞች አዳዲስና ቆየት ያሉ የታዋቂ ደራሲያን መፅሐፍቶችን በ PDF እንዲሁንም
ያልተነበቡ ድርሰቶችን ግጥሞችን ታሪኮችን ያገኙበታል።


Contact. @atronosebot
please dont touch the leave button.😔😳😳
Download Telegram
#ምንትዋብ


#ክፍል_አምስት


#ድርሰት_በሕይወት_ተፈራ


....“ጉድ! ጉድ!” አለ፣ ወይዘሮ ጌጤነሽ ሳይቀደሙ ለመቅደም። ቆመው እጅና እግራቸውን በእርጥብ እጃቸው ያባብሳሉ።

ባላምባራስ ዝም አሉ።
ወይዘሮ ጌጤነሽ ባላቸው፣ “ምንድርነው?” ሳይሏቸው በመቅረታቸው ቅር ተሰኙ። ወሬውን ለማውራት የነበራቸውን ጉጉት ስለአመከኑባቸው
ወሽመጣቸው ተቆረጠ። የባላቸውን ዝምታ አሰቡና ነገሩ ከነከናቸው።.

“ምንድርነውም አይሉ?” አሏቸው፣ የጎሪጥ እያይዋቸው።
“የትም አምሽተሽ መተሽ ደሞ ጉድ ትያለሽ?” አሉ፣ ባላምባራስ።

“ነገረኛ፣ ታሞ አይተኛ አሉ” አሉ፣ ወይዘሮ ጌጤነሽ፣ ድምፃቸውን
ዝቅ አድርገው።

“ምን አልሽ?”

“ምን እላለሁ ሳናግርዎ መልስ አይሰጡም ወይ ነው ያልሁት። ሌላ ምን እላለሁ?” አሉ፣ ራት ለመሥራት ምድጃ ላይ ድስት የጣደችውን የቤት አገልጋይ እያዩ።

“ሚሰማሽ ካገኘሽ ምላስሽ ረዥም ነው።”

“ኸርሶ አይበልጥ” አሉ፣ አሁንም ቀስ ብለው።

ባላምባራስ ቆጣ ብለው፣ “ምን አልሽ?” ካሉ በኋላ፣ ጉድ ከሰሙ
ስለ ሰነበቱ ጉዱን የመስማት ፍላጎት አደረባቸው። ቁጣቸውን ገታ አድርገው፣ “እና ምንድርነው ጉዱ?” አሉ፣ ለጠጥ ብለው እምብዛም ለወሬ የጓጉ እንዳይመስሉ።

ወይዘሮ ጌጤነሽ እንዳልሰማ ዝም አሉ፤ እንደ ማኩረፍ አድርጓቸዋል።

“ምንድርነው ጉዱ አልሁሽ እኮ” አሉ ባላምባራስ፣ ቆጣ ብለው።

ወይዘሮ ጌጤነሽ አሁንም ያልሰሙ መሰሉ።

“ሳናግርሽ መልስ 'ማሰጪ?” የባላምባራስ ቁጣ እየተጋጋለ ነው።

“ምን አሉኝ?” አሉ ወይዘሮ ጌጤነሽ። ፊታቸው ላይ ስስ ፈገግታ ይነበባል። ዛሬ አነስተኛ ቢሆንም ባላቸው ላይ ድል ተቀዳጅተዋል።

እነዚህን መሳይ ጥቃቅን ድሎች ናቸው አንዳንዴ ባላቸውን ያሸነፉ
እንዲመስላቸው የሚያደርጓቸው።

“ጉድ እያልሽ ገባሽ። ምንድርነው ብልሽ አለመጥሽ።” አሁንም
ድምፃቸው ገኗል፣ ባላምባራስ ሁነኝ።

“አልሰማሁ ሁኜ ነው” አሉ፣ ወይዘሮ ጌጤነሽ። የባላቸው ቁጣ
የሚገነፍልበትን አፍታ ስለሚያውቁ ያገኙትን ድል እያጣጣሙ፣
“የግራማች ልዥ ...” ሲሉ ጀመሩ።

“ግራማች?” ሲሉ አቋረጧቸው፣ ባላምባራስ። ወሬውን ለመስማት
ቸኩለዋል።

“ግራማች መንበር ናቸዋ።”

“ኸሷው ጋር ስታወሪ እንደቆየሽ አውቄያለሁ። ወልደልዑል ምንን
ሆነ?”

“ሴቷ ወለቴ።”

ጥላዬ፣ የሆነ ነገር እንዳለ ደመነፍሱ ነገረው። ነፍሱ ከዳችው። ጉዱን ለመስማት ቤት ውስጥ መግባት ፈልጎ፣ ወገቡ አልታዘዝ፣ ጉልበቱ አልንቀሳቀስ አለው። እንደምንም ብሎ ተነስቶ ውስጥ ገብቶ መደብ
ላይ ተቀመጠ።

ባላምባራስ በመገረም ተመለከቱት። እሳቸው ሳይተኙ ቤት ውስጥ ስለማይገባ፣ ዐይኑን ካዩት ከርመዋል። ሆዳቸው ተገላበጠ።

“እና ምንን ሆነች?” አሉ፣ መባባታቸው እንዳይታወቅባቸው
እየታገሉ።

ወይዘሮ ጌጤነሽ ከመናገር ተቆጠቡ። ጥላዬን ሰረቅ አድረገው አዩት።እሱ የሚሉትን ለመስማት ቢጓጓም ጎንበስ ብሎ መሬቱን በስንጥር መጫጫር ጀመረ።

“ዛሬ ምንን ነክቶሻል? ምንን ሆነች ስልሽ መልስ ማሰጪ?”

“በያ ሰሞን ንዳድ ይዟቸው ኸነሱ ዘንድ ተኝተው የነበሩት ለካስ
ንጉሡ ኑረዋል...”
“ንጉሠ?”
“አዎ።”
“አጤ በካፋ?”
“እሳቸው። ሌላ ንጉሥ አለ?”
“ምንድርነው ምታወሪው?” አሉ ባላምባራስ፣ የሚስታቸውን ትንኮሳ
ችላ ብለው።
መንን
“አጤ በካፋ ራሳቸው። ወለቴ አስታማቸው ስታበቃ ዛሬ ሰዎች
ኸጥሎሽ ጋር ሰደዱ።”
“ሊያገቧት?”
“ኋላ?”
ጥላዬ ዱብ ዕዳ ሆነበት፣ ድንጋጤ ሰውነቱን አብረከረከው። ተነስቶ
ሊወጣ ፈልጎ ወሬ ለመስማት ተቀመጠ።

“ሰው ለማንጓጠጥ ማን ብሎሽ። ወረኛ! ደሞ ማታመጪው የለ” አሉ
ባላምባራስ፣ ተደናግጠዋል፣ ንዴትም ተናንቋቸዋል።
“እንዴት በሉ? ምን ያልሆነ አምጥቸ አውቃለሁ? ኸመሽ አገር ሁሉ ሚያወራው እኼንኑ ማዶል? የጣ ፈንታ ነገር ይገርማል።”

“ውነት ነው፤ ዕጣ ፈንታ ነው” አለ ጥላዬ፣ የሞት ሞቱን። ሰውነቱ
እየራደ ነው። ለራሱ፣ እኔ ዕድል ፈንታየ ሁኖ ያልታደልሁ ሁኘ
የወፍታው እኼን አሰማኝ ብሎ በዐይኑ ውሃ ሞላ። እንባው እንዳይታይበት እደጅ ሲወጣ፣ አባቱ በዐይናቸው ተከተሉት።

“ያቺ አያትየው ኸደብተሮቹ ነው ውሎዋ። ኸተኙበት ቀባብታቸው
ይሆናል ይላል ድፍን ቋራ” አሉ ወይዘሮ ጌጤነሽ፣ አገልጋይዋ ራት
እንድታቀርብ በእጃቸው ምልክት እይሰጡ።

“ድፍን ቋራ ኸምኔው ሰምቶ ነው እኼን ሁሉ ሚለው? አንቺና
ጓደኞችሽ ጓሮ ሁናችሁ ያቦካችሁት ነው እንጂ። ለነገሩ ልዥቱ
ምንም አይወጣላት። ደማም... ቆፍጣና... ይገባታል፤ ይገባታል ::
ሚገባትን ነው ያገኘች። እኔ ለተክለሃይማኖት ተዋጋህ እየተባልሁ ስወቀስ የተክለሃይማኖትን ወንድም በካፋን አገባች?” አሉ ባላምባራስ፣
በመገረም ራሳቸውን እየነቀነቁ።

አገባች! እርምዎን ያውጡ እንግዲህ! በርሶው አጓጉል ጠባይ ነው እኼ ሁሉ የመጣው። እርስዎንስ ይበልዎ፣ ልጄን ጎዱብኝ እንጂ አሉ ወይዘሮ ጌጤነሽ፤ ለራሳቸው። ጮክ ብለው ሊናገሩ ፈለጉና በማታ ኸሳቸው ጋር ምን አጫጫኸኝ ብለው፣ “ኸቤታቸው ንግርት አለ ይባላል። ዘመዳቸው የሆነ ሰው ኸወለቴ ግንባር ጠሐይ ስትወጣ አይቷል” አሉ።
ባላምባራስ መልስ አልሰጧቸውም። ቁጭት ላይ ናቸው። ልዥህን ለልዤ ስባባል ቆይቶ፣ በትንሽ ነገር ኸጥብቅ ወዳጄ ተቀያይሜ፣ አሁን
እኼው ሌላ...ያውም ንጉሥ ወሰዳት። እንግዲህ ኸንጉሥ መንጋጋ አላስጥላት! ያቺ ቀን እንዴት ያለች የተረገመች ናት አሉ፣ ግራዝማች መንበርን የተቀየሙበትን ቀን አስታውሰው።

የጊዮርጊስ ማኅበር ነው። ግራዝማች መንበር ቤት ይበላል፤ ይጠጣል። ጨዋታው ደምቆ፣ እንደወትሮው ስለ ጦር ሜዳ ጀግንነት ይወሳል። ባላምባራስ ሁነኝ ራሳቸውን እንደ ጀግና ቢቆጥሩም፣ ስለ ጦር ሜዳ
ሲወራ አይወዱም።ከዚህ በፊት ሰድበውት የሚያውቁት ደብተራ ሞቅ ብሎታል። “አሁን በወፍታው ኸጦር ሜዳ ቋንጃውን የተመታ ዠግና ይባላል?” ብሎ በሳቅ
ተንተከተከ።

ማንም አልሳቀ። ሁሉም አንገቱን ደፋ። ሳቅና ቁም ነገር የሰፈነበት
ስብስብ ወደ መሸማቀቅ ተለወጠ።

ደብተራው የሳቀለት ሲጠፋ፣ “እኛ ባገራችን ምናቀው ሰው ቋንጃውን
ሚመታው ሲሸሽ ነው” አለ፣ የፌዝ ሳቅ እየሳቀ።
ባላምባራስ ከዓመታት በፊት ቋንጃቸውን ተመትተው ያነክሳሉና
እሳቸውን ሊነካ መሆኑን አውቀው ከተቀመጡበት ተነሥተው
ከዘራቸውን እየወዘወዙ፣ “አንት መተተኛ ደብተራ። እኔ ሁነኝ በንዳንተ ያለ ድግምተኛ አልሽረደድም። የት አባህ ጦር ሜዳ ውለህ ታውቃለህና
ስለ ጦር ሜዳ ታወራለህ? ጋን እያሸተትህ ኸድግስ ድግስ ዙር እንጂ።

ጥፋተኛው አንተ ሳትሆን አንተን ኸሰው መኻል የቀላቀለህ ነው” ብለው ከዘራቸውን ግራዝማች መንበር ላይ እየወዘወዙ፣ “መንበር አሰደብኸኝ ...
ያውም በዝህ በድውይ። ግድ የለም። እንዲህ ኻሰደብኸኝ ወዲያ እመቃብሬ እንዳትቆም... ኸዚህ ያላችሁ ሁሉ ቃሌን ቃል እንድትሉ”
ብለው እያነከሱ ወጡ።
ከዚያን ቀን ጀምሮ የግራዝማችና የባላምባራስ የረጅም ዘመን ጓደኝነት አከተመ፣ አብሮም የጥላዬና የወለተጊዮርጊስ ዕጮኛነት። ባላምባራስ፣
“በቤቱ አሰደበኝ” ብለው ቂም ያዙ። ግራዝማች፣ “ደብተራው ለሰደበው እኔ ምን አረግሁ?” ብለው ቅር ተሰኙ። አስታራቂ መሃከላቸው ቢገባ ባላምባራስ፣ “ሙቼ ነው ቁሜ ኸሱ ጋር ምታረቅ” አሉ። “ልዥህን
ለልጄ” የተባባሉት ጓደኛሞች ተቀያየሙ።

ግራዝማች መንበር፣ ሁነኝ ምንም ቢሆን የረጅም ጊዜ ወዳጄ ነውና
አንድ ቀን እንታረቅ ይሆናል እያሉ የወለተጊዮርጊስን እጅ ለጠየቀ ሁሉ አይሆንም እያሉ መለሱ።
👍15
#ትኩሳት


#ክፍል_አምስት


#በስብሐት_ገብረ_እግዚአብሔር

...ካንድ ስምንት ቀን በኋላ፣ ማታ ተመስገን ክፍል ቁጭ ብዬ
ስስራ፣ ተመስገን መጣና አልጋው ላይ ዘጭ ብሉ ተጋደመ፡፡ እፎይ!
ብሎ ተነፈሰ
«ሲኒማ የገባችሁ መስሉኝ» አልኩት
«ሌሎቹ ገቡ፣ እኔ ግን ተውኩት»
«ለምን ተውከው?» አልኩት። ድምፄ «አንተ ተንኮለኛ!»
እንደሚል አይነት ነበር
«ደስ አላለኝማ!» አለኝ፡፡ ትንንሽ አይኖቹ ሊደበቁ ጀምረዋል፣
ግን ጥርሶቹ ገና መታየት አልጀመሩም
«ውሸታም! ቀጠሮ ቢኖርህ ነው እንጂ» አልኩት
«ከማን ጋር?»
«እኔ አውቃለሁ እንዴ ያንተን ተንኮል? ወይ ካንዷ ብሎንድ
(ፀጉሯ ብጫ ወይም ነጭ ብጤ) ጋር፣ ወይ ከሲልቪ ጋር»
«ሲልቪ!? አላወቅክምና!»
«ምን?»
«ቀርቶ!»
«ምነዋ?»
«ምን እባክህ የሴት ነገር» አለ «አገር ጤና ብዬ እንደ ሁልጊዜያችን ወዲህ አመጣሁዋት፡፡ ከሰአት በኋላ ነበር። የከሰአት በኋላው እንዴት እንደሚጣፍጥ ታውቅ የለ? ልብሷን አወላለቀችና
አልጋው ውስጥ ገባች። እየተንገበገብኩ ተከትያት ልገባ ስል፣
ከትራሱ ላይ ኣንዲት ፀጉር እንስታ አቀበለችኝ። ረዥም የፈረንጅ
ፀጉር ነው፤ ግን ጥቁር አይደለም፣ ቡና አይነት ነው»
«ይሄ የኔ ፀጉር እንዳልሆነ እርግጠኛ ነኝ አለችኝ»
«ዝም ኣልኩ። አልገባኝም አየህ
«ተናገር እንጂ» አለችኝ። እግዜር ያሳይህ፡፡ በመጀመሪያ
አልጋው ውስጥ ልገባ ጎምበስ እንዳልኩ ኣሁንም አለሁ፡፡ ይታይሀል? ራቁቴን አልጋው ላይ ባራት እግሬ ቆሜ? እንደሚድህ ልጅ:: ልብሷን ስታወልቅ እያየሁና የሚጠብቀኝን ደስታ እያሰብኩ ግትር አድርጎ ቅንዝር ወጥሮኛል፡፡»

የተመስገን አይኖች ጨርሰው ጠፉ፣ ጥርሶቹ ተገለጡ፣ ይሰቅ
ጀመር፡፡ ከት ብሎ እየሳቀ፣ ሳቅ በሚቆራርጠው ንግግር
ገና አሁን ታየኝ ሀ! ሀ! ሀ! እንዴት እንዴት - ሀ! ሀ! U! እንዴት እንደነበርኩ ሁ! ሁ! ሁ! አንዲህ ነበርኩ» አለና በጀርባው ከተጋደመበት ተነስቶ ዞሮ በጉልበቱና በእጁ ተንበረከከ፡፡
ከስሩ ትራሱን አስተካከለና፣ ሌባ ጣቱን እያነጣጠረበት

«እኔ እንዲሀ ነኝ፣ ሂሂ!!» ትራሱን «እቺ ሲልቪ ናት።
ያቀበለችኝን ፀጉር ባንድ እጄ እንደዚህ ይዣለሁ። እንዳትበጠስ
ወይም ወድቃ እንዳትጠፋ እየተጠነቀቅኩ፣ ያቺን ነጃሳ ፀጉር እንዲህ ይዣለሁ። ቁላዬ ደሞ እዚህ ጋ ቆሞ ሲልቪን ቁልቁል ያያታል።አይ የኔ ቁላ! ቂል ነውኮ፡፡ ያንተም ቂል ነው?» እንደገና ሳቅ
አሸነፈው። አልጋው ላይ ተንከባለለ። ሳቁ ሲያልፍለት

«በኋላስ?» አልኩት

«በኋላማ ምን ልበልህ ልጄ? ቃል ሳትናገር ተነስታ ልብሷን
መልሳ ለበሰች፡፡ ረጋ ባለ ድምፅ 'የኔና ያንተ ነገር በዚሁ አለቀ”
ብላኝ ልትወጣ ስትል፣ እኔ እዚች ጋ ራቁቴን እንደቆምኩ
«ምን ነካሽ?» አልኳት፡፡ ሲያቀብጠኝ'ኮ ነው:: እስቲ ዝም ብላትስ?
«ዘወር አለችና፣ እሱ ጠረጴዛ ላይ ያለውን መፃህፍትና ደብተር
በአጇ አንዴ ገፍታ መሬት ላይ አዝረከረከችው:: እና ጠረጴዛውን
በተጨበጠ እጇ ደጋግማ እየመታች

«እኔ የእስላም ሀሪም ሴት - አይደለሁም!» ብላኝ ስታበቃ፣ ወጥታ በሩን በሀይል ጓ! አርጋው ሄደች። ልብሴን ልለብስ
ካናቴራዬን ሳነሳ በሩ ብርግድ ብሎ ተከፈተ። ማን ገባ መሰለህ?»
አለኝ

«ማን?» አልኩት

«ሲልቪ ራሷ ነቻ! የሴት ነገር! ከመቼው ሀሳቧን ለወጠች?!
እያልኩ ልገረም ስጀምር፣ ኣጠገቤ መጣች። አቅፋ ልትስመኝ
እንደሆነ ገባኝ፡፡ ትንሽ ልኮራባት አሰብኩ። ታድያ እሷ ምን አረገች
መሰለህ? እወቅ : ስቲ።»
«በጥፊ መታችህ?»
«ብጭራሽ!»
«አቅፋ ሳመችህ?»
«ትቀልዳለህ?»
«እንግዲያው ምን አረገች?» አልኩት
«ጫማዋን አረገች»
«ምን?»
«በንዴት ጫማዋን ረስታው ሄዳ ነበር፡፡ ተመልሳ አረገችውና
ወጣች። እኔ ራቁቴን ቆሜ ቀረሁ፡፡ ቁላዬ እስካሁን ተኝቷል፡፡ ከዚያ
በኋላ አናግራኝ አታውቅም»
«ጥፋቱ ያንተ ነው» አልኩት
«እንዴት?» አለኝ
«ያመጣሀቸው ሴቶች ሊሄዱ ሲሉ «ፀጉሮችሽን ሁሉ ይዘሻል?
ቁጠሪ እስቲ ለምን አትላቸውም?» አልኩት
«መቼ ሴት አመጣሁና?» አለኝ
«እ-ህ? ቡናማው ፀጉርሳ?»
«ከየት እንደመጣ እንጃለት:: ምናልባት ቤት የምትጠርገው
አልጋ የምታነጥፈው አሮጊት ያን እለት ታማ ኖሮ፣ በሷ ምትክ
ባለቡናማ ፀጉር ሴት አልጋዬን አንጥፋልኝ ይሆናል»
«ምስኪን ተመስገን!» አልኩት
ምስኪን ትላለህ ምስኪን። ይኸው እስከዛሬ ዖም ላይ እገኛለሁ
«ዛሬ ማታ ግን ለመግደፍ ያሰብክ ትመስላለህ»
«ነበር እባክህን። ፀጉሯን እንደ ወንድ ነው 'ምትቆርጠው፣
ቢሆንም ምንም አትል። ብቻ »
«ብቻ ምን?»
«የት እንደምወስዳት ጨንቆኛል»
ሲመሽ ፈረንሳዮች concierge
የሚሉት ዘበኛ ይመጣና' ወደመኝታ ቤቶቹ የሚያስገባው በር አጠገብ አንዲት ቢሮ አለችው፣ እዚያች ቁጭ ብሉ ወጪ ገቢውን ሁሉ ይመለከታል። ወንዶች መኝታ ቤት ሴት ማስገባት ክልክል ነው፡፡)

«የኔ ሆቴል አለልህ አይደለም እንዴ?» አልኩት
«አትጠቀምበትም?»
«እዚህ ልተኛ እችላለሁ»
እሱማ ጥሩ ነበር»
“ብቻ እንዳታስጮሀት አደራ፡፡ ካስጮህካትም ፎጣ አጉርሳት።
ብዬ የሆቴሌን ቁልፍ ሰጠሁት
ተመስገን ወደ ቀጠሮው ከሄደ በኋላ ተመልሼ ልስራ
በጠበጠኝ። ተነስቼ አሜሪካዊቷ ቤት ሄድኩ፡፡ ጉዳዬን አስረዳኋት።
አልቻልኩም፡፡ ሲልቪ ለኔ ስትል እንደተወችው ገባኝ፡፡ ይህ ሀሳብ
ከዚህ በፊት አገሬ እጮኛ አለችኝ ብያት ነበር፡፡ አሁን፣ እጮኛዬ
ካንቺ ጋር ያለኝን ግንኙነት አወቀች፡፡ ማን እንደነገራት እንጃ፡
ወረቀት ፃፈችልኝ። በአንድ ሳምንት ውስጥ ኣሜሪካንህን ትተሀታል
የሚል ወሬ ካልደረሰኝ ሌላ እኛ ፈልግ አለችኝ፣ ብዬ ነገርኳት።
«i derstand የዚህ መጥፎ ዜና ምክንያት በመሆኔ በጣም
አዝናለሁ» አለችኝ። ያቀድኩት ይህን ነግሬያት ደህና እደሪ ብያት
ሲልቪን ፍለጋ ለመሄድ ነበር። ግን ልጅቱ ጥቁር ስስ የሌሊት ልብስ
ለብሳ ስትራመድ በጣም ታስጎመጃለች፣ ገላዋን ታጥባ ቆዳዋን በታልከም ዱቄት አሻሽታው፣ ሽታው ይማርካል፡፡ ከሷ ጋር አደርኩ
«ራሷን በጣም ታዘብኩት። በጣም ፀፀት ተሰማኝ፣ ሲልቪን
የበደልኳት መሰለኝ»
በነጋታው ሲልቪን ከምግብ ቤት ስትወጣ ጠብቄ ኣገኘኋት።
ቡና ልጋብዝሽ አልኳት። ኤክስ ውስጥ የምወደው ካፌ የለኝም
አልኩህ? አለችኝ፣ እሺ ማርሰይ ልውሰድሽ አልኳት። መኪናዬ
ጋራዥ ናት አለችኝ፡፡ በኦቶቡስ ልውሰድሽ አልኳት። አልፈልግም
አለችኝ። እንግዲያው ምን እናርግ? አልኳት፡፡ እኔ ቡና ላጠጣህ፣ራሴ አፍልቼ፣ አለችኝ፡፡ ቤቷ ወሰደችኝ፣ ከኤክስ ትንሽ ወጣ ብሎ ባላገሩ ውስጥ ነው

«የሴዛን የነበረው ቤት በዚህ በኩል ነው። መሄድ ትፈልጋለህ?»
አለችኝ
«አልፈልግም» አልኳት
«እኔም ሄጀ አላውቅም» አለችኝ
እየሳቅኩ «Tut'en fous, ch?» አልኳት («ደንታ የለሽም፣ እ?»)
እየሳቀች፣ «Je m'en fous eperdument!» አለችኝ («እቺን ያህል እንኳ ደንታ የለኝም»)
ቤቷ ገባን። ሁለት ክፍል (አንድ መኝታ፣ አንድ ሳሎን) ወጥ
ቤት፣ መታጠቢያ ክፍል። በየግድግዳው የልዩ ልዩ አቢይ ስእሎች እትም ተለጥፏል። የቤት እቃው ዘመናዊ ነው፣ ሰማያዊና ወይን ጠጅ ቀለማት ይበዙበታል
👍25
#ምንዱባን


#ክፍል_አምስት


#ትርጉም_ከዬሐንስ_ገፃዲቅ


.....ከተማውን ጥሎ ወጣ፡፡ ከተማውን ለቅቆ ገጠር እስከገባ ድረስ እየተጣራ ነበር የሚሄደው፡፡ ወዴት እንደሚሄድ ሳያስተውል መንገድ እንደመራው ዝም እያለ ተጓዘ፡፡ ከነጋ ጀምሮ እህል አልቀመሰም:: ሆኖም የረሃብ ስሜት አልተሰማውም፡፡ ቁጣ ቁጣ ብሉታል፡፡ በማን ላይ ወይም በምን ምክንያት እንደተቆጣ ግን አያውቅም:: የሚቀጥለው ምን ይሆን ሲል ራሱን ጠየቀ፡፡
የገጠር አየር የልጅነት ጊዜውን አስታወሰው:: የልጅነት ዘመኑን ካስታወሰ በጣም ቆይቶ ነበር፡፡ ከዚያም ብዙ ኣሳቦች ተፈራረቁበት፡፡»

ፀሐይ አሽቆልቁላ ገብታ ከአድማስ ውስጥ ልትገባ ስትል ዣን ቫልዣ
እልም ካለ ጫካ ውስጥ ከአንዲት ጉብታ ላይ ቁጭ ብሎአል፡፡ የአልፕስ ተራራ በሩቁ ይታያል፡፡ ከጫካው ወጣ እንዳለ አንድ ቀጭን የእግር መንገድ አለ፡፡

ከዚህ ቁጭ ብሎ ሲያሰላስል ደስ የሚል ድምፅ ይሰማል፡፡ ፊቱን
ሲያዞር ወደ አሥራ ሁለት ዓመት የሚሆነው ልጅ እየዘመረ ወደ እርሱ ይመጣል:: ልጁ በጭንቅላቱ ሣጥን መሳይ ነገር ተሸክሞአል፡፡ ልጁ ጥቂት
ከተራመደ በኋላ ቆም ብሎ በእጁ የያዘውን ሣንቲም ወደ ሰማይ እያጎነ ይጫወታል:: የልጁ ሀብት ምናልባት ይኸው ነጭ ሽልንግ ብቻ ሳይሆን አልቀረም::

ዣን ቫልዣ ከተቀመጠበት ሲደርስ የሰውዬው ከእዚያ መኖር ሳይገነዘብ ቆም አለ፡፡ እንደ ልማዱ ሣንቲሙን ወደ ሰማይ አጎነ፡ ሣንቲሙ አምልጦት
ከመሬት ሊወድቅ ዣን ቫልዣ ወደ ተቀመጠበት በረረ:: ዣን ቫልዣ
ሽልንጉን በእግሩ ረግጦ ያዘበት:: የልጁ ዓይን ሣንቲሙን ተከትሎ ስለሄደ የት ላይ እንዳለ ያውቃል፡፡ ልጁ አልፈራም፤ በቀጥታ ወደ ሰውዬው ሄደ::

«ጌታዬ ገንዘቤን» አለ ልጁ የዋህነትና ድንቁርና በተሞላበት አንደበት::

«ስምህ ማነው?» ሲል ዣን ቫልዣ ጠየቀው::

«ትንሹ ዥራቪ ነው ጌታዬ::»

«ቶሉ ከዚህ ጥፋ» አለው ዣን ቫልዣ ::

«ፍራንኬስ?» ሲል ልጁ ጠየቀ፡፡

ዣን ቫልዣ እንዳቀረቀረ ቀረ::

«ገንዘቤን» አለ ልጁ እምባ እየተናነቀወ :: ሽልንጌን!»

ዣን ቫልዣ ምንም ነገር እንዳልሰማ ሰው ፀጥ አለ፡፡ ልጁ የሰውየውን ሸሚዝ ኮሌታ በአንድ እጁ ያዘ፡፡ በሌላው እጁ ሣንቲሙን ለማስለቀቅ የሰውየውን እግር ለማንሳት ሞከረ::

«ገንዘቤን እፈልጋለሁ ፧ ሽልጌን!» ብሎ ከጮኸ በኋላ ትንሹ ዠራቬ
ማልቀስ ጀመረ:: ዣን ቫልዣ አንገቱን ቀና አደረገ፡፡ ከተቀመጠበት ግን አልተነሳም:: ፊቱ፡ በአሳብ የተዋጠና የተጨነቀ ይመስላል፡፡ በመገረም ልጁን
አትኩሮ አየው:: ዱላውን ሳብ ኣድርጎ «አንተ ማነህ? እህ! ምንድነው የምትፈልገው? እስካሁን አልሄድክም እንዴ» ሲል በሚያስፈራ ድምፅ ጮኸበት:: ሣንቲሙን እንደረገጠ ከመቀመጫው ብድግ ብላ «ራስህን ብትጠብቅ ይሻልሃል» አለው::
ልጁ በፍርሃት ተወጦ ቀና ብላ አየወ:: ሰውነቱ ይንቀጠቀጥ
ጀመር፡፡ ወዲያው ከጥቂት ሰኮንድ መርበትበት በኋላ ልጁ አግሬ አውጪኝ ብሎ ሸመጠጠ፡፡ ዞር ብሎ ለማየት ወይም ጩኸት ለማሰማት እንኳን አልደፈረም፡፡ ሆኖም ጥቂት እንደተጓዘ ትንፋሽ አጥሮት ቆም አለ:: ግን ብዙ
አልቆመም፧ መንገዱን ቀጠለ፡፡

ፀሐይዋ ጠለቀች፡፡ ዣን ቫልዣ ከተቀመጠበት አካባቢ ብርሃን ለጨለማ ሥፍራዋን ለቀቀች:: ቀኑን መሉ ምግብ የሚሉት ነገር አልቀመሰም::ምናልባትም ትንሽ እንደትኩሳት ብጤ ሳይሞካክረው አልቀረም::

ልጁ ከሄደ ጀምሮ ከተቀመጠበት ነቅነቅ አላለም:: በኃይል ነው
የሚተነፍሰው:: ከተቀመጠበት ጥቂት ራቅ ብሎ ከነበረው የሸክላ ስባሪ ገል ላይ ዓይኑን ተከለ፡፡ ስለገሉ ይመራመር ጀመር፡፡ ግን በድንገት መላ ሰውነቱ
ተንቀጠቀጠ፡፡ የሌሊቱ ቁር እየተሰማው ሄደ፡፡

ቆቡን ሳብ አድርጎ ግንባሩን ሸፈነ:: የሸሚዙን አዝራር ለመቆለፍ
ጣቶቹ አዝራር ፍለጋ ላይ ታች አሉ:: ብድግ ብሎ ወደፊት ራመድ ካለ ከኋላ መለስ ብሉ ዱላውን ለማንሳት ጎንበስ አለ፡፡

በእግሩ ረግጦ ይዞት የነበረው ሽልንግ በማብረቅረቁ ዓይኑ ወደዚያ ተሳበ፡፡ ኮረንቲ እንደያዘው ሰው ተሸማቀቀ፡፡ «ምንድነው ነገሩ?» ሲል ጥርሱን በማፋጨት ራሱን ጠየቀ:: እንደገና ወደኋላ መለስ ብሉ ሣንቲሙን በእግሩ በመርገጥ ሸፈነው:: ሣንቲሙ ዓይን አብቅሎ የሚያየው መሰለው::

ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላ እግሩን መነጨቀና ጎንበስ ብሎ ሣንቲሙን
አነሳ፡፡ ቀና ብሎ አካባቢውን ተመለከተ:: ጋራውና ሸንተረሩ ሁሉ የሚያየው ስለመሰለው በፍርሃት ተውጦ መወጊያ እንደምትፈልግ ዱኮላ ዓይኑ በፍርሃት ተቅበዘበዘ፡፡ ከቆመበት ተገትሮ ቀረ፡፡

ምንም ነገር አላየም:: ጊዜው እየጨለመና አየሩ እጅግ እየቀዘቀዘ ሄደ:: ሰማዩ በጭጋግ ተሸፈነ፡፡

«ወይ ጣጣ» ሲል ልጁ በሄደበት አቅጣጫ ጉዞውን ቀጠለ፡፡ አንድ
ሰላሳ - እርምጃ ያህል እንደተራመደ ቆም ኣለ፡፡ አካባቢውን ተመለከቱ።
ምንም ነገር የለም:: ድምፁን እጅግ ከፍ አድርጎ «ዠራቬ» ሲል ተጣራ፡፡ ከዚያም ድምፁ
አጥፍቶ አዳመጠ:: መልስ አላገኘም፡፡

አገሩ ጭር ያለና ጭጋጋም ቢሆንም አካባቢው በግልጽ ይታያል ከዝምታና ከራሱ ጥላ በስተቀር የሚንቀሳቀስ ፍጠር ጨርሶ አልነበረም ዣን ቫልዣ መንገዱን ቀጠለ፡፡ የሚወስደውን እርምጃ ፍጥነት በመጨመር እንደ መሮጥ አለ። አልፎ አልፎ ቆም እያለ በሚያስፈራ ሻካራ ድምፅ «ዠራቬ» ሲል እንደገና ተጣራ፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ ልጁ ቢሰማው
እንኳን በፍርሃት ስለሚዋጥ ይደበቃል እንጂ መልስ አይሰጠውም:: ነገር ግን ልጁ በርግጥም በጣም ርቆ ሄዷል፡፡
ዣን ቫልዣ እንደገና ልጁ በሄደበት ኣቅጣጫ መሮጥ ጀመረ
እየተገላመጠ፣ እየጮኸ፣ እየተጣራ ብዘ ተጓዘ፡፡ ግን ማንንም አላገኘም በደረቱ ተንፏቅቆ የሚሄድ ወይም ድምፁን አጥፍቶ ያደፈጠ እየመሰለ ከአንዴም ሁለቴ፣ ከሁለቴም ሦስቴ መንገዱን ለቅቆ ወደ ጥሻው ዞር እያለ
ተመለከተ፡፡ ግን ሰው የመሰለው ነገር ጠጋ ሲል ቁጥቋጦ ወይም ድንጋ ሆኖ ያገኘዋል፡፡ በመጨረሻ ሦስት መንታ መንገዶች ከሚገናኙበት ደረሰ ከመሐል መንገድ ላይ ቆመ:: ጨረቃዋ ብቅ ብላለች:: ለማየት እስከቻለ
ድረስ አርቆ ተመለከተ:: «ዥራቬ፣ ትንሹ ዥራቬ፣ ዠራቬ» በማለት
ሦስት ጊዜ ድምፁን ከፍ አድርጎ ተጣራ:: ድምፁ የገደል ማሚቶ እንኳ ሳያዕማ ከጭጋጉ ውስጥ ተውጦ ቀረ:: «ትንሹ ዥራቬ» ሲል ዝግ በደከመ ድምፅ አጉረመረመ:: ያ የመጨረሻው ሙከራ ነበር፡፡ በዓይ የማይታይ ኃይል በዱላ እንደመታው ሰው በድንገት እግሩ ተሳስሮ ጉልበቱ እጥፍጥፍ አለበት:: ፀጉሩን በእጁ ጨብጦና ፊቱን ጉልበቱ ላይ አሳርፎ
ከቋጥኝ ድንጋይ ላይ በመቀመጥ «ምን ዓይነት እድለቢስ ሰው ነኝ» አለ ጮኸ፡፡ ልቡ እያበጠ ሄደ፡፡ ምርር ብሎ አለቀሰ፡፡ ከአሥራ ዘጠኝ ዓመት ወዲህ ሲያለቅስ የመጀመሪያው ነበር:: ዣን ቫልዣ ብዙ አለቀሰ፡፡ ከሕፃኑ መባባትና ከሴቶች መርበትበት ይበልጥ በፍርሃት ተውጦ ከዓይኑ እምባ የወጣ እስኪመስለው ድረስ በማልቀስ አንጀቱን እርር ድብን አደረገ እያለቀሰ ሳለ ከሕሊናው ውስጥ የነበረው ብርሃን እየፈካ ሄደ፡፡

የተለየ ብርሃን ነበር፡፡ ያ ብርሃን አሳደደው፤ አስፈራራው፡፡ ያለፈው የሕይወቱ ዘመን፤ የመጀመሪያው ወንጀሉ፤ የረጅም ጊዜ ስቃዩ ፧ ጨካኙ ዓለም፤ የደነደነው ልቡ ፣ ከእስር ቤት ማምለጡ፤ ከጳጳሱ ቤት በእርሱ ላይ የደረሰው! የመጨረሻው አሳፋሪ ድርጊቱ ፤ ከሕፃን ልጅ ገንዘብ መዝረፉ፤
👍22😁1
#ገረገራ


#ክፍል_አምስት


#በታደለ_አያሌው

.....“ያንቺ ነዉ” አለችኝ፣ እኛ እያለን ራሷ ወደ ጀመረችዉ የምሳ ጉድ ጉዷ እየተመለሰች፡፡ “ታዲያ አደራሽን ምንድነዉ ቅብጥርሴ እንዳትጠኝ። እኔ ምኑንም አላዉቅልሽም። ስጭ ነበር የተባልሁት፣ ይኼዉ ሰጥቼሻለሁ።
አበቃሁ” በእራፊ ጨርቅ የተጠቀለለች ትንሽ ነገር መሆኗን ቀድሞዉንም ስትሰጠኝ
ኣስተዉያለሁ፡፡ ምን እንደሆነች ለማየት ገለጥ ባደርጋትም፣ ጥቅልሉ ስለበዛ ፍሬ እቃዋን ቶሎ ልደርስበት አልቻልሁም፡፡ ስቀበላት እምነት መስላኝ ነበር። አይደለችም ማለት ነዉ? በዚያ ላይ ስንት ዙር እንደ
ተጠቀለለች! ተርትሬ ተርትሬ ስጨርስ ያገኘሁት ግን ጥፍር እንኳን የማታህል ሚሞሪ ካርድ ብቻ ነበረች፡፡ መጠቅለያ ጨርቁን ባራግፈዉም፣ ከእሷ ሌላ ምንም የለም። እመዋ ደግሞ እንዳልጠይቃት ቀድማ መንገዱን
ሁሉ ዘጋግታብኛለች፡፡ ምን ቸገረኝ ብዬ ወደ ሞባይሌ ቀፎ ከተትኋት።
ከዚያም በድምፅ ማጫወቻዉ ከፈትሁት፡፡ ከትንሽ የነፋስ እና የወፎች ጺዉጺዉታ በኋላ፤ ማሲንቆ የሚያስንቅ አንቺሆዬ ዓይነት ፉጨት መጣ፡፡

የት ነበር የማዉቀዉ ይኼን ድንቅ ትንፋሽ?

መቼ አጣኋቸዉ! ወይዘሮ ብርሃኔ ናቸዉ፡፡ እሳቸዉ ናቸዉ ትንፋሻቸዉን እንደ ፈለጉ የሚያሽሞነሙኑት። እንኳን በሴት በወንድ እንኳን የማላዉቀዉን፣ ማንኛዉንም ዜማ በፉጨታቸዉ ብቻ ሲያወጡት አያድርስ ነዉ። በዘለሰኛ ጨዋታቸዉ የሁሉን ነፍስ የሚገዙት፣ በሸክላ ሥራ ጥበባቸዉ ሁሉን የሚያስደንቁት፣ ፉጨት እና ሽለላዉን
የሚያዉቁበት፣ ወይዘሮ ብርሃኔ ናቸዉ። አትጠገቤዋ፣ ደርባባዋ ሰዉ! በእርግጥ መጀመሪያ ያወቅኋቸዉ በእሸቴ በኩል ነበር። የእሱ እናት ናቸዉ፡፡ እንደ ጣና ሐይቅ የተረጋጉት፣ እንደ ዥማ ወንዝ የልብ የሚያደርሱት ሴት ናቸዉ በፉጨት የመጡብኝ። ጥሎብኝ አንጎራጓሪ ሰዉ
አይሆንልኝም፡፡ እጅግ አድርጌ እወዳለሁ። በተለይ ዘለሰኛ! ዘለሰኛ ለመስማት ስል ምንም ነገር ቢሆን እተዋለሁ። አሁን አሁን እንዲህ እሸቴ የሚባል ስም በአፍንጫዬ ይውጣ ልል፣ ያኔ ልቤን ወለል አድርጌ
እንድከፍትለት ካደረገበት ብዙ ምክንያቶቹ አንዷ እናቱ ነበሩ።

ልዩ ናቸዋ!

ፉጨቱን ተከትሎ በድምፃቸዉ ደግሞ መጡብኝ። ያ ከእሕልም
ከመጠጥም የሚጣፍጠዉ ዘለሰኛቸዉ!

ኧኧኧኧኧኧ...
ሸክላ ሠሪ አርገህ ሾመኸኛል
የሸክላ ጥበብ ይገባኛል፡፡
ኧኸ

ሸክላ ማለት የእጄ ሥራ
እኔ ደግሞ የእጅህ ሥራ፤
የእጄ ተሰብሮ ብመኝም ሞት
የእጅህን ማትረፍ ግን አወቅህበት!

ኧ ኸ ኧ ኸ ኧ.....

ምንም እንኳን ቀረጻዉ ጥራት ያልሞላለት ሆኖ ሞገዱ እንደሚዋዥቅበት ሬዲዮ ወስድ መለስ ሲያደርገዉም፣ እየደጋገምሁ አጣጣምሁት። ከምኔዉ እንደሆነ እንጃልኝ ብቻ አሁን መረጋጋት ይታይብኛል። አሁን ከፋኝ ብዬ ስነፈርቅ አልነበር እንዴ? ፊቴን ዳበስሁት፤ እንባ የሚባል ጠብታዉ ሳይቀር የለም። ወደ መስታዎት ሮጬ ዓይኔን አየሁት። እንኳንስ ደም
ሊመስል! ልክ ምንም እንዳልተፈጠረ ሁሉ ወደ ነባሩ ቀልቤ ተመልሻለሁ። ያውም ወደ ደስተኛዋ ዉብርስት። ጃሪም የለ፣ እሸቴ የለ፣ እርግዝና የለ
ሁሉም ደህና። ፍጹም ሰላም፡፡

“እመዋ?” አልኋት፣ እንጀራ ይዛ ወደ ሳሎን ብቅ ከማለቷ፡፡

ለወጉ ያህል ብቻ ቀና ብላልኝ፣ ወደ ማዕድ ቤት አልፋኝ ሄደች። ምን ላርግሽ፣ ይልቅ ማቀራረቡን አትረጅኝም? ማለቷ መሰለኝ። ከምኔዉ እንዲህ እንደ ተረጋጋሁ እሷንም ሳይደንቃት አልቀረም።

“ማነዉ የሰጠሽ ግን?” አልኋት፣

እግር በእግር እየተከታተልኳት።
“ማን ይመስልሻል?” አለችኝ፣ ፍርጥም ብላ።

“ብቻ እሽቴ ነዉ እንዳትዪኝ በማርያም”

“እሸቴ የሆነ እንደሆንስ? ስጦታ ሁሉ ያዉ ስጦታ አይደለም ወይ?”
“እህእ?”
ስጦታ ሁሉማ ያዉ አይደለም፡፡ ከእሸቴ ነዉ ማለት ነዉ? እንደ ፈራሁት መልሶ ከፋኝ፡፡ እንደገና ስምጥ ወደ ሆነዉ ድባቴ ዉስጥ ተወርዉሬ ወደቅሁ። መቼም ከእሱ ሌላ የእናቱን ድምፅ ቀርጾ በእናቴ በኩል የሚልክልኝ አይኖርም፡፡ ለዚያዉም ድምፁ ሌሊት ወፍ ጭጭ ሲል በድብቅ የተቀረጸ ነዉ የሚመስለዉ። ስለዚህ አብሮ የሚያድር ሰዉ ነዉ ማለት ነዉ የቀረጻቸዉ፡፡ ያም ሰዉ ከእሸቴ ሌላ ሊሆን አይችልም፡፡ እሱ
ነዉ የላከልኝ። እጅ መንሻ መሆኑ ነዉ? የተጣላነዉ በእናቱ ይመስል፣ በዚህ ሊያባብለኝ መሞከሩ የበለጠ እልህ ዉስጥ ጨመረኝ፡፡

እናቱ ሌላ፣ እሱ ሌላ።

ራሴን ግን ታዘብሁት፡፡ ቶሎ የሚከፋኝ፣ ቶሎ የምደሰት ግልብ ሆኜ አርፌዋለሁ ማለት ነዉ በቃ? አሁን ለቅሶ፣ አሁን ሳቅ፣ እንደገና ለቅሶ?
ሰአሊ ለነ ቅድስት!
።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።
ሐዘንም ሐፍረትም ቀላቅሎ ከመታኝ ይኸዉ ቀናት አለፉ፡፡ ያዉም እንደ ሙጀሌያም እየተሙጀለጀሉብኝ። በእነዚህ ቀናት ሁሉ በእመዋ ቤት ተደብቼ ራሴን አዳመጥሁት። እንደ ወትሮዬ ወደ አደባባይ ሳልወጣ፣
እንደ ድሮዉ በወዳጅ ሳልከበብ፣ እንደ ሁልጊዜዉ ወደ ሲራክ-፯ ማዕከል ሳልመላለስ ዐሥራ አንድ ረዣዥም ቀናት እያለፉኝ ሄደዋል። እንዲሁ አልፎ አልፎ ብቻ ሲልብኝ፣ ክራሬን አንስቼ ለብቻዬ እያንጎራጎርሁ በእናቴ ቤት ሰነበትሁ፡፡

በዚህ ምክንያት እመዋም ሁኔታዬን እያየች ስትብሰለሰል፣ እያሳዘነችኝ መጣች፡፡ ምናልባት ዘወር ብልላት ይቀላት እንደሆነ ብዬ፣ ሲራክ-፯ ለአንዳንድ ተልእኮዎች በማሰብ በምስጢር ቀድሞም ወደ ተከራየልኝ
ምስጢራዊዋ ቤት ደግሞ ሄድሁ። ይቺ ቤት፣ በተልእኮዬ ሂደት መሀል
እንድቀራረባቸዉ የሚያስገድዱ ሰዎች ቢኖሩ ቤቴ ብዬ የማሳያቸዉ ቤት ናት። እንደ ሁኔታዉ፣ እነዚህ ዒላማ የተደረጉ ሰዎች ረዥም ጊዜ እና የተለየ መቀራረብ የግድ የሚፈልጉ ስለሚሆን፣ የቤት ቡና የምጋብዛቸዉ በእመዋ ቤት ባለኝ ክፍል ሳይሆን፣ በዚሁ ምስጢራዊ የኪራይ ቤት ነዉ።

ወደ'ዚህ ቤት እንደመጣሁ፣ እመዋ አዘዉትራ እሸቴ ምን በደለሽ?»
ስትለኝ የሰነበተችዉ ጥያቂ ድንገት ሽዉ አለችብኝ፡፡ ገና ዛሬ፣ አሁን ገና። እንደገና አስብሁበት:: እዉነትስ ግን እሱ ምን በድሎኛል? ምንም። ምንም ወንጀል አጣሁበት። ቆይ እኔ ራሴ አይደለሁ እንዴ፣ ዓለም በቃኝ ብሎ
ከመነነበት የእናቱ ከተማ ሄጄ የተዋወቅሁት? እኔ ባልሄድበት እንኳንስ መበደል፣ ጭራሽ የት ያዉቀኝ ኖሯል? ደረስሁበት እንጂ አልደረሰብኝም እኮ፡፡ ይልቅስ ራሴ ነኝ በገዛ ሕይወቴ የተጫወትሁት። እኔን ማንም አልበደለኝም። ከተበደልሁም የተበደልሁት በራሴ ነዉ። እኔዉ ነኝ ራሴንም እግዚአብሔርንም የበደልሁት። ስለዚህ ራሴን ለካህን ማሳየት
አለብኝ።

ንስሐ ያስፈልገኛል።

ወዲያዉኑ ተስፈንጥሬ ተነሳሁና፣ ነጠላዬን እንደ ነገሩ አንገቴ ላይ ጥዬ ወደ መኪናዬ ሮጥሁ። ምስጢራዊዋ ቤቴ በአዲስ አበባ ልዩ ሰፈሩ ልደታ በሚባለዉ የምትገኝ ኮንዶሚኒየም ስለሆነች፣ ተዘግቶ እስከሚከፈት
የሚያጉላላኝ የአጥር በር የለብኝም፡፡ ይቺን መከራ ቻይ መኪናዬን ዛሬም ያለቅጥ ረግጬ አበረርኋት። የትራፊክ መብራት የሚባል ለቅጽበት አላስቆመኝም። ንስሐ አባቴ የሚያገለግሉት እዚሁ ልደታ ጎን ባለዉ መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ቢሆንም፣ በዚህ አመሻሽ ግን እሳቸዉ የት
እንዳሉ አላዉቅም። በቤታቸዉ ሊሆኑ እንደሚችሉ በመገመት ነበር ቀጥታ ወደ መኖሪያ ቤታቸዉ የሄድሁ። እዚያ ስደርስ ግን አጣኋቸዉ።

አቤት ጥድፊያ! ስልክ ቁጥራቸዉ አለኝ አይደል እንዴ?
ደወልሁላቸዉ።
“እዚያዉ ልደታ እኮ ጉባዔ ላይ ነበርሁ። ምናለ ከመድከምሽ ፊት ደዉለሽ ብትጠይቂኝ ኖሮ ልጄ?” አሉኝ፣ በሐዘኔታ፡፡

“ግድየለም፡፡ እዚያዉ ልምጣ ታዲያ?”

“ምን ገዶኝ? ነይ በይ እዚሁ”
👍352
#ሳቤላ


#ክፍል_አምስት


#ድርሰት_ሚሲስ_ሔንሪ_ውድ


...አሮጌዉ ቤት በጨረቃ ብርሃን ሲታይ ጸጥ ቅዝቅዝ ብሎ ነበር " ያንለት ደግሞ ጨረቃዋ በጣም ደምቃለች « በብርሃንዋ ሰፊው ያታክልት ቦታም ዳር እስከ ዳር
ቁልጭ ብሎ ይታያል " በአየር ሁኔታ ማሳያው ያውራ ዶሮ ምሥል በበረንዳውና በባርባራ ላይም በማብራቷ ተለይተው ይታወቃሉ ባርባራ በረንዳውን ቀስ ብላ
አልፋ በፍርሃት ለጭንቀት እንዳፈጠጠች ከአትክልቱ ሥፍራ በታች ወደነበሩት እጅብ ያሉት ዛፎች ወረደች ያ ከዱሩ ወጥቶ እሷን በድብቅ ሲጠቅሳት የነበረው
ፍጡር ሌላ ተጨማሪ መዘዝ ይዞ የመጣ ሰው ይሆን ? ወይም †ፈጥሮው ከሰው የተለየ ልዩ ጉድ ነው ? ወይስ በውን የሌለ በሐሳብ ብቻ የተፈጠረ ባዶ ራዕይ ነው?
የሚሉ ጥያቄዎች በባርባራ አእምሮ ሲተራመሱባት አሁንም ቀረብ ብሎ ጠቀሳት ባርባራ ከፍራቷ የተነሣ እግሮቿ እየተንቀጠቀጡ ያንገት ልብሷን ጭምድድ አድርጋ ያዘች በጠራው ጨረቃ እሷ ወደሱ ስትጠጋ እሱ ደግሞ ወደ ዛፎቹ ጥላ አፈገፈገ" ባርባራ ቆም አለች

« ማነህ ? ምንድነህ ? » አለችው ድምጿን ዝቅ አድርጋ!«ምን ትፈልጋለህ ? »
« ባርባራ » ብሎ ጠራት በሹክሹክታ ድምፅ «አላወቅሽኝም ? » ገና ከመናገሩ
ድምፁ በትክክል ለየችው » ከደስታ ይልቅ ፍራት ያመዘነበት ድምፅ አሰምታ ተንደርድራ ወደሱ ሔዶች » በእርሻ ሥራ የዋለ ገበሬ የሚለብሰውን ዐይነት ልብስ
የለበሰ ሰው በክንዶቹ ዕቅፍ ሲያደርጋት ሥቅሥቅ ብላ አለቀሰች " የሥራ ካፖርት
ደርቦ የሣር ባርኔጣ ደፍቶ ሰው ሠራሽ ሪዝ አድርጎ ፍጹም ሌላ ሰው መስሎ ቢመጣም ወንድሟ መሆኑን ዐወቀችው

« ሪቻርድ ! ከየት መጣህ ? ከዚህ ምን አመጣህ ? እኔ ደግሞ ምናልባት ካንተ የተላከ ሰው እንደሆነ ብዬ ተጠራጠርኰ እንጂ እንደዚህ ሆነህ ትመጣለህ ብዬ
አላሰብኩም " አሁንም በጣም ነው ያስደነገጥኸኝ እውነት በጤናህ ነው ወይስ ዐብደህ የመጣኸው ? እዚህ ብትገኝ ሞት እንደሚጠብቅህ እያወቅህ እንዴት ደፍረሀ ትመጣለህ ? » አለችው እጆቿን እያፋተገች

«ያውም ከወንጀለኛ መስቀያ ላይ ነዋ እንደምገደል መች ጠፋኝ ባርባራ ዐውቀዋለሁ " »

« ታዲያ ለምንድን ነው ወደ መጥፈያህ ስተት ብለህ የመጣህ ? እማማ ብታይህ
በአድራጐትህና በድፍረትህ ደንግጣ ትሞታለች »

« ኑሮውን አልቻልኩትም ከወጣሁ ጀምሮ እስከ ዛሬ ለንደን ስሠራ ነበር ነገር ግን በዚሁ ዐይነት መግፋት አልቻልኩም
" ትንሽ ገንዘብ ባገኝ ግን ከዚህ የተሻለ ዕድል አለኝ " ስለዚህ አማማ ጥቂት ገንዘብ ብትሰጠኝ ለመጠየቅ ነው የመጣሁት»

« እስከ ዛፊ ምን ትሠራ ነበር ? »

« በአንድ የፈረሶች ጋጣ ውስጥ ነበር የምሠራው " »

« ምን ! በፈረሶች ጋጣ ? »
አለችው የእውነቷን ድንግጥ ብላ»
"ከዚህ የተሻለ ምን ዕድል ሊኖረኝ ይችላል ? ነጋዴ ? ባንከኛ ? መይስ የንድ ሚኒስትር ልዩ ጸሐፊ መሆን ? ነው ወይስ ንብረት ኖሮኝ በሀብቴ ልተዳደር?» አላት
የሆዱ ብሶት እየተናነቀው « አየሽ የምተዳደረው በሳምንት በማገኛት
ዐሥራ ሁለት ሽልንግ ብቻ ነው»

« አዬ ሪቻርድ ! » አለች እጁን ግጥም አድርጋ ይዛ እያለቀስች
« እንዴት ያሉ ጐደሎ ቀን ነው ? አየህ ......... እኛ የምንጽናናው ድርጊቱ በደም ፍላት እንጂ
ሆን ብለህ እንዳልፈጸምከው በማሰብ ብቻ ነው»

« ባርባራ እኔ እኮ ምንም ወንጀል አልፈጸምኩም »

« ምን? »

« በውነት እምልልሻለሁ ። ከደሙ ንጹሕ ነኝ እንዳያውም ሰውየው ሲገደል እኔ ከቦታወ አልነበርኩም " እስከማውቀው ድረስ በግምት ካልሆነ በቀር እገሌ ሲገድል አየሁ ብዬ በዐይን ምስክርነት መናገር እንኳ አልችልም " አላየሁም "
ግምቴ ግን ከማየት የማያንስ ትክክለኛ ነው »

ባርባራ አሁን በበላጠ አንዘረዘራት « መቸም ወንጀሉን የፈጸው ቤተል
ማለትህ እንዳልሆነ እርግኛ ነኝ »

« ቤተል ? እሱም በነገሩ የለበትም እሱ ለራሱ በድብቅ አውሬ ያድን
ነበር ፤ ወጥመዶቹን ነበር የሚከታተል »

« እማማ ግን በወንጀሉ የቤተል እጅ አለበት ያለች አላስቀምጠኝ አለች»

« ተሳስታለች እሱን እንድትጠረጥር ያዪረጋት ምንድነው ? »

« ከመጀመሪያ ይህ እምነት እንዴት እንዳደረባት ልነግርህ አልችልም እሷም ራሷ የምታውቀው አይመስለኝም " ወትሮም ቢሆን ምን ያህል ደካማ እንዶሆነችና በሐሳቧ የሚመጣባትን ሁሉ እውነት መስሎ እንደሚታያት አንተም ታስታውሳለህ አሁን ከዚያ አሠቃቂ ምሽት ጀምሮ ስለ ግድያው ሁልጊዜ ሕልም ታየኝ ትላለች በሕልሟ ውስጥ ሁሉ ቤተልም አብሮ ይታያታል " ስለዚህ ቤተል በነገሩ እንዳለበት ያለ ምንም መጠራጠር ታምናለች »

« ባርባራ እሱ በዚህ ጉዳይ አልነበረበትም »

« አንተ እንዳልነበርክበት ነው አሁን የምትነግረኝ ? »

« እኔ በዚያን ጊዜ ከሆሊጆን ቤትም አልነበርኩ " ወንጀሉን የፈጸመ ቶርን ነው»

« ቶርን ? » አለች አንገቷን ቀና አድርጋ « ቶርን ማነው ? »
« እንጃ ! ባውቀው ደስ ይለኝ ነበር ከገባበት መዝዤ ባወጣው በወደድኩ ሰውየው የአፊ ወዳጅ ነበር ። »

“ሪቻርድ !! ... ይህን ስም ስታነሣብኝ ራስህን የዘነጋህ መስልከኝ ” አልችው አንገቷን በቁጣ ወዶ ኋላ ምልስ አድርጋ

«እኔ!ኮ አንድ ጊዜ ያበላሸሁት ስለሆነ በጉዳዩ ለመነጋገር አልሻም " አሁን ስለ ንጽሕናዬ ብናገር ሪቻርድ ሔር ትንሹ በፈጸመው የግፍ ግድያ ተብሎ የተላለፈብኝን ውሳኔ ሊያስለውጥልኝ አይችልም። ግን አባባ ዛሬም እንደ ጠላኝ ነው »

«ከፊቱ ስምህን የሚያነሣ የለም " ከቤት አንድም ሰው ስምህን እንዳይጠራ ለአሽከርቹ በሙሉ ትእዛዝ ሰጥቶአል " ያቺ ኤልሳ መቸም የተነገረችውን ማስታወስ አይሆንላትም " መኝታ ቤትህን የሚስተር ሪቻርድ ክፍል " እያለች ስትናገር ሁለት ጊዜ ቢያስጠነቅቃትም እየረሳች መተው አልቻለችም " በሦስተኛው ከቤት አባረራት ። አባባኮ ምሏል ሰም†ሃል ? »

« ምን ብሎ ? እሱ ሁልጊዜ እንደማለ ነው »

« ያሁኑ ግን ከባድ መሐላ ነው ሪቻርድ።ፍርድ ከተሰጠ በኋላ ከ0ሥር ዓመት በኋላ ቢገኝ እንኳን አሳልፎ እንደሚሰጥህ ከዳኞቹ ፊት ቁሞ በመማል አረጋግጦላቸዋል እሱ አንድ ጊዜ ከተናገረ እንደማይመለስ ታውቀዋለህ » ስለዚህ ያንተ ከዚህ አካባቢ መገኘት አደገኛ ነው»

« እሱኮ ዱሮውንም እንዶ ልጁ እንዳልቆጠረኝ ሊያደርግልኝ የሚገባውን እንዳላደረገልኝ ዐውቃለሁ » አለ ምርር ባለ አነጋገር « እስኪ አንቺ ስታስቢው
ጤና በማጣቴ ምስኪኗ እናቴ ስለ ተንከባከበችኝ በየደረሰበት ላገኘው ሰው ሁሉ ተሞላቀቀ እያለ ሊያሥቅብኝ ይጥር ነበር እኔ ቢቴ የደስታ ቤት ቢሆንልኝ ኖሮ ይኸ ሁሉ መቸ ይደርስብኝ ነበር ? በይ አሁን ... ...ባርባራ እናቴ ጋር ዐይን ለዐይን ተያይተን መነጋገር አለብን»

ባርባራ ከመናገሯ በፊት ትንሽ አሰበች« እንዴት እንደ ምናሳካው አላውቅም»
« ለምን አንቺ እንደ መጣሺው እሷስ ወደኔ አትመጣም? ለመሆኑ ተኝታለች ወይስ ተነሥታለች ? »

« ዛሬ ከሷ ጋር መተያየት የማይሆን ነገር ነው አባባ ሳናስበው ሊመጣ ይችላል
አሁን ያለው ከቦሻ ቤት ነው»

« ዐሥራ ስምንት ወር ሙሉ ሳንተያይ ኖረን አሁን ደግሞ ሳላገኛት ብሔድ በጣም ከባድ ነገር ነው » አለ ሪቻርድ «የገንዘቡ ነገርስ? አንድ መቶ ፓውንድ ነውየምፈልገው »
👍24😁2