አትሮኖስ
286K subscribers
118 photos
3 videos
41 files
566 links
╔╦╦╦═╦╗╔═╦═╦══╦═╗
║║║║╩╣╚╣═╣║║║║║╩╣
╚══╩═╩═╩═╩═╩╩╩
ግጥሞች አዳዲስና ቆየት ያሉ የታዋቂ ደራሲያን መፅሐፍቶችን በ PDF እንዲሁንም
ያልተነበቡ ድርሰቶችን ግጥሞችን ታሪኮችን ያገኙበታል።


Contact. @atronosebot
please dont touch the leave button.😔😳😳
Download Telegram
#ያልታበሱ_እንባዎች


#ክፍል_ስድስት


#ድርሰት_በአሰፋ_በቀለ_ገየሱስ

...ወይዘሮ እልፍነሽ አጭር ወፍራም ናቸው፣ ከወገባቸው ጎንበስ ያሉ ፀጉራቸወም በአጭርና ሸበቶ፤ በባህሪያቸው ወራኛ የሚባሉ ናቸው፤ አንዷን ከአስር
በላይ የሚያባዙ፤ ለውሸት ልክ የሌላቸው:: ከዚሁ ባህሪያቸው በመነጨ የጎረቤት ሰው ሁሉ እልፍነሽ ወሬ እፈሽ ይላቸዋል፡፡

ሽዋዬ ቤት ወስጥ ገብታ ራሷ ወንበር ሳብ አድርጋ ስትቀመጥ ወይዘሮ እልፍነሽ እጆቻቸውን በወገባቸው ላይ አጣምረው ከፊቷ ቆሙ፡፡ ለወሬው በጣም
የቸኮሉ ይመስላለ::
«እንደው ምን አግኝቶሽ ይሆን ልጄ?» ሲሉ ጠየቋት::
«ቁጭ በሏ!» አለቻቸው ሸዋዬ ከንፈሯን በምላሷ እያራስች፡፡ የእጆቿን መዳፎች አጋጥማ በጉልበቶቿ መሀል አጥብቃ ይዛቸዋለች፡፡
ወይዘሮ እልፍነሽ ለወሬው ሰፍ ብለዋል። ጠበብ ካለች አፋቸው ውስጥ ከአራት በላይ የማይታዩ ጥርሶቻቸውን ገለጥ አድርገው ፈገግ እያሉ ተቀመጡና፡-
«እስቲ ንገሪኝ ልጄ!» አሏት፡፡
«ጉድ የምትሰሩኝ እኮ እናንተ ጎረቤቶቼ ናችሁ!» አለቻቸው ሽዋዬ ምላሷን በከንፈሮቿ ዳር እና ዳር ግራና ቀኝ ወጣ ገባ እያረገች ወይዘሮ እልፍነሽ ደረታቸውን በእጃቸው ደሰቅ አረጉና «ውይ በሞትኩት! ምነው? ምን አደረግን?»
«የእህቴ ህይወት ሲበላሽ እያያችሁ ዝም ትሉኛላችሁ?»
«ምነው? ምን አገኛት?»
«አርግዛ ትምህርቷን ብታቋርጥስ?»
«እንዴ!» አሉ ወይዘሮ አልፍነሽ ነገሩን እንደማቃለል ዓይነት በሚያስመስል አነጋገር፡፡ «እጮኛዋ ባለሙያ አይደል እንዴ! ችግር ቢፈጥር ኣሽቀንጥሮ ይጥልላት የለ!» ካሉ በኋላ አፋቸውን የበለጠ ወደ ሸዋዬ ጠጋ በማድረግ «አአሁን ቀደምስ
ችግሩ ተፈጥሮ ገላገላት ተብሎ ብለው ሳይጨርሰ ሽዋዬ ቀደመቻቸው::
«ምን አሉ?» አለች ዓይኗን ፍጥጥ አድርጋ እያየቻቸው። እጮኛዋ ያሏት ነገር ከተቀመጠችበት አንጥሮ ሊያነሳት ሲል ደሞ የወርጃ ነገር ጨመሩባትና
በአለችበት ኩርምትምት አለች።
«ኧረ ተይኝ እቴ!» ብለው ወይዘሮ እልፍነሽ እንደ መግደርደር ዓይነት ወደ ውጭጉዳይ አየት ካደረጉ በኋላ እንደገና ወደ ሽዋዬ መለስ በማለት «በአንቺ እህት ስንት
ልጃገረዶች እየቀኑባት ደሞ እንዲህ ያለ ሥጋት ይደረብሽ እንዴ? ሆሆይ...»
ሸዋዬ በባሰ ድንጋጤ ሰውነቷ ሽምቅቅ ብሎ መንፈሷ ድክም፣ ልቧም ስንፍ አለና በተራዘመ የቃል አወጣጥ «አ ሶ ር ዳ ለ ች ነው የሚሉኝ ስትል ጠየቀቻቸው::
«ገላግሏት!»
ሸዋዬ አሁንም ድክም ባለ መንፈስ «አ መ ስ ግ ና ለ ሀ:!» አለቻቸውና
ከተቀመጠችበት በቀስታ ብድግ አለች። ወይዘሮ እልፍነሽ እወነትም አፍሰው አቃሟት፡፡
«ጠሐይ ይብረድልሽ እንጂ!» አሏት ወይዘሮ እልፍነሽ እኚያኑ
ጥርሶቻቸውን ገለጥ እያደረጉ፡፡
«ቤቴ ሄጄ ማረፍ እፈልጋለሁ። ደህና ዋሉ!» ብላቸው ወጣች፡፡

ወይዘሮ እልፍነሽ አሁንም እጃቸውን በወገባቸው ላይ አጣምረው እስር እስሯ እየሄዱ በሹክሹክታ ዓይነት «እይው ልጄ፧ እኔ እኮ ቀድሜ ጠርጥሪያለሁ፣
ብታይ አንቺ እግርሽ ወጣ ያለ ጊዜ እሱ ዘሎ ጥልቅ! ትናት ዘሎ ጥልቅ! ዛሬም ዘሎ ጥልቅ ሲል እያየሁ ሆዴ በጣም ይፈራ ነበር፡፡» አሏት፡፡
ከቤት ይዟት ወጥቶ ያውቃል?»
«ኧረ በገዛ ቤትሽ ውስጥ እቴ! ደሞ የምን ወደ ውጪ ሆይ…?» አሉና
«ማናት ይቺ እቴ ስሟን አምጪልኝ፡ ይቺ የወይዘሮ ዘነቡ ሠራተኛ?»
«ፋንታዬ?»
“እ! እሷ ቲራቲር ስታይ አይደል እንዴ የምትውለው፤ እሷን ብትጠይቂያት እኮ ጉድ ትነግርሻለች፡፡»
ሽዋዬ ነገሩ ሁሉ ገባት። ወሬው ሁሉ ከፋንትዬ እንደሚመነጭ ተረዳች፡፡
ይሁንና ብትጠይቃት ደፍራ እውነቱን ላትነግራት እንደምትችል ገመተች። ለነገሩ ወሬ በቅቷታል፡፡ ከእንግዲህ ታፈሡ ብቻ ቀረቻት፣ በእሷ ግምት አስቻለውና
ሔዋንን የምታገናኝ ታፈሡ እንደምትሆን በማመን፡፡

ሸዋዬ በዕለቱ እህል ውሃ አላሰኛትም ሔዋን ምሳ አዘጋጅታ እየጠበቀቻት ቢሆንም ቤቷ እንደ ደረሰች የሔዋንን ዓይኖች ቀና ብላ እንኳ ሳታይ በቀጥታ አልጋዋ ላይ ወጥታ ጥቅልል ብላ ተኛች፡፡ በዚያው መሽ፡፡ ቀኑም በለሊት ተተካ፡፡ ያ ሁሉ ሆና ሽዋዬ በዓይኗ ላይ እንቅልፍ አልዞረም፡፡ ይልቁንም እንኳን ራሷ ለአልጋዋም አልመቻት ብላ በየደቂቃው በመገላበጥ ስታንቋቋት አደረች፡፡

በማግስቱ ጠዋት ሔዋን ወደ ትምህርት ቤት ስትሄድ ልክ እግሯ ከቤት እንደ ወጣ ሸዋዬ ልታደርግ ስታስብ ከአደረችው እቅድ ውስጥ የመጀመሪያውን መፈፀም ጀመረች:: ሔዋንና አስቻለው የተፃፃፉት የፍቅር ደብዳቤ ካለ ብላ ደብተሮቿን መፈተሽ ያዘች ፤ ገፅ በገፅ እያገላበጠች፣ የደብተሮቹን መሸፈኛ እየገለጠችና ዘቅዝቃ እያራገፈች በረበረቻቸው። የሔዋን ቅያሪ ልብሶች
አልቀሯትም፡፡ ኪሶቿን ሁሉ ዳበሰቻቸው፡፡ ግን ምንም ነገር ሳታገኝ ቀረች፡፡
ሲደክማት አልጋዋ ላይ ቁጭ አለች:: ግን ደግሞ አንድ ነገር ትዝ አላት። የድካሟ ምክንያት ርሀብ ጭምር ነው:: ከትናንት ምሣ ጀምሮ እስከ ዛሬ ቁርስ ሰዓት ድረስ ምንም አልቀመሰችምና ወደ ምግብ አዘነበለች፡፡ በእርግጥም ከነውዝፉ አጠቃለለችው:: በንዴት ውስጥ ስለነበረች አጎራረሷ እንኳ ጤናማ አልነበረም ቶሎ
ቶሎ ጎሰጎሰችው።

ከታፈሡ ጋር የምትገናኝበት ስዓት በመከራ ደረሰ። ጠዋት ወደ ታፈሡ ቤት መሄድ አልቃጣችም፤ በአንድ በኩል ለጠብ ነው የምትፈልጋት! በሌላ በኩል ደግሞ አስቻለውም ቢሆን ከታፈሡ ቤት አይጠፋምና፡፡ በሁለተኛው ፈረቃ
የዕረፍት ሰዓት ነው ከታፈሡ ጋር የተገናኘችው፡፡ በዲላ አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ቅጥር ግቢ ውስጥ መሀል ላይ በምትገኘው ባንዲራ ሥር ሆና
ጠራቻትና አብረው እንደተቀመጡ ሸዋዬ ዓይኗን እፍጣ፣ ጥርሷን አግጣ፡-

«ስሚ አንቺ!» አለቻት፡፡
«ወይ» ታፈሡ ድንግጥ በማለት፡፡
«እህቴን ከአበ-ልጅሽ ጋር አቃጥረሽ አበላሽሻት አይደል?? »
«ኦ» ታፈሡ ሁለመናዋን ነዘር እያደረጋት።
« አላደረኩም በያ?»
«ጓደኛዬ ምን እያልሽ ነው?»
«ኧረ ጓደኛሽን ወዲያ ፈልጊ!»
«ከአንቺ የበለጠ ምን ጓደኛ እለኝ?» አለቻት ታፈሡ ነገሩ እየገባት ሂዶ ፈገግ እያለች።

«ጥሩ አቃጣሪ ኖረሻል፤ ጉድሽ ሁሉ ወጣ?»
«አቀዛሽው ሽዋዬ»
« አቃጣሪ ማለቱ? እንዲያውም ሲያንስሽ ነው»
«ጨምሪልኛ ኪም ኪም ኪም ኪም!
« አሁን ሳቂ! የምታለቅሽበት ጊዜ ይመጣል::»
«እጠብቃለኋ ኪም ኪም ኪም ኪም» ታፈው እሁንም፡፡
«እንዲህ ስትንከተከች ትንሽም አታፍሪ?» ሽዋዬ ውስጧ ብግን እያለ፡፡
«ምንም አላፍር ሽዋዬ! ምንም በማላውቀው ነገር ይህን ያህል ካልሽኝ ምናልባት ሁለቱ ተዋድደው ከአገኘኋቸው እንዲያውም እንዲያውም አጋባቸዋለሁ::»
«ኣ» ሸዋዬ ቆሽቷ እያረረ፡፡
«በእርግጥ ሁለቱ ተዋደው ከሆነ ወደ ኋላ አልልም! ታይኝ የለ!» ብላት ታፈሡ ከሸዋዬ ፊት ዘወር አለች።

ሸዋዬ ግራ ግብት እንዳላት ነበር ከዚያ በኋላ ያለውን ጊዜ ያሳለፈችው፡፡
የታፈሠ ሁኔታ ስለ ሔዋንና አስቻለው ፍቅር ብዙም ፍንጭ አልሰጣትም።
በእርግጥ ስለዚሁ ጉዳይ ባለፈው ለሊት በምታስላስልበት ጊዜ በተለይ ከወይዘሮ እልፍነሽ የሰማችው ወሬ ለጊዘው ቢያናድዳትም በእውነትነቱ ግን ተጠራጥረዋለች፡፡
👍3
#ምንትዋብ


#ክፍል_ስድስት


#ድርሰት_በሕይወት_ተፈራ


....“አባቱን ላስገደለ ለርጉም ተክለሃይማኖት ያደረ ርጉም ነው” እየተባሉ ሲታሙ ያዘነላቸውን ያህል፣ ያን ቀን አዘነባቸው፤
ዓመጸባቸው።የሚሉትን ሊፈጽም፣ ሊያነጋግራቸው ቀርቶ፣ በዐይኑ
ሊያያቸው ቸገረው።

ጉልምስና ዕድሜ ላይ ከደረሰበት ጊዜ ጀምሮ ሁለት ነገር ተመኝቶ
አደገ - ወለተጊዮርጊስን አግብቶ ሥዕል እየሣለ መኖር፡፡
ወለተጊዮርጊስን ብዙ ጊዜ የሚያያት እሑድ ቤተክርስቲያን ከቅዳሴ በኋላ ሲሆን፣ ከቤተክርስቲያኑ ቅጥር ግቢ ውጭ ያለው ዋርካ ስር
ጥምጥሙን አድርጎ፣ ዱላውን መሬት ላይ፣ ዐይኑን ደጀሰላሙ ላይ ተክሎ የሷን ከግቢ መውጣት ይጠባበቃል። በመልኩ ማማርና በቁመቱ ርዝመት የተማረኩ ኮረዶች እሱን እያዩ ሲሽኮረመሙ፣ እሱ ዐይኑ ደጀሰላሙ ላይ ልቡ ወለተጊዮርጊስ ጋ ነው። ነጠላ ተከናንባ ብቅ ስትል ልቡ ይደልቃል። ዐይኖቹ የሚያርፉበት ይጠፋቸዋል ። ከአያቷና
ከእናቷ ኋላ እየተራመደች ዐይኖቻቸው ሲጋጩ ፈገግታ ይመጋገባሉ። ሰላምታ ይለዋወጣሉ።

ይህ ለሳምንት ስንቅ ይሆነዋል።
በዚህ የተነሳ ዋርካውን ይወደዋል ፤ ለእሱ ብቻ የተተከለለት
ይመስለዋል። ዋርካው ሥር ቆሞ የወለተጊዮርጊስን መውጣት
ሲጠባበቅ፣ ብቅ ስትል ልቡ ሲመታ፣ ዐይኑ ማረፊያ ሲያጣ፣ ፍቅሩ ሲግል፣ ምኞቱ ሲበረታ፣ ጊዮርጊስ ዝም ብሎ አይመለከተኝም፣ ያባቴን
ልብ ያራራልኛል እያለ ዐዲስ ተስፋ ውስጡ ሲጫር ይሰማዋል።
ሌሎች ጎረምሶች አጠገቡ ሲቆሙ፣ አቅሉን ያጣል። ወለተጊዮርጊስ ከቤተስኪያኑ ከመውጣቷ በፊት ቢሄዱ ደስ ይለዋል። “እስቲ ዞር በሉ”
ለማለት ይቃጣዋል።

ወለተጊዮርጊስና እሱ ቁጭ ብለው የልባቸውን ተነጋግረው ባያውቁም፣ አባቶቻቸው ቢቀያየሙም፣ የጊዜ ጉዳይ እንጂ አብሮ መኖር ዕጣ ተርታቸው እንደሆነ ሁለቱም በልባቸው አምነዋል፤ ሳይነጋገሩ ቃል
ተገባብተዋል። አንዱ ለአንዱ ልቡንና ሕይወቱን ሰጥቷል። ምንም እንኳን እሱ ያ ንፋስ አሸዋውን አንስቶ የተሸፈነበት የእሷ ምስል ልቡ ውስጥ ተቀርጾ አልፎ አልፎ ፍርሐት ቢያሳድርበትም፣ አላገኛት ይሆን?
የሚል ጥርጣሬ ውስጥ ቢከተውም፣ ሁለቱም በአባቶቻቸው መሃል ዕርቅ
ወርዶ የሚጋቡበትን ቀን በተስፋ ተጠባብቀዋል።

ጥላዬ፣ አባቶቻቸው የገቡትን ቃል አጥፈው፣ ለዓመታት እንደ
ጠላት ለመተያየታቸው ብቻ ሳይሆን፣ ወለተጊዮርጊስን ሳያገባ
ለመቅረቱ ምክንያቱ የእሱው አባት በመሆናቸውና ሥዕል የመሣል
ፍላጎቱን ሊያመክኑበት የሚታገሉትም እኝሁ አባቱ በመሆናቸው ቁርሾ ይዞባቸዋል።


ዐይናቸውን ላለማየት፣ እናቱን በሆነ ባልሆነው ሲጨቀጭቁና ቀን ያገኙትን ሁሉ ማታ ሲራገሙ ላለመስማት፣ ማታ ዳዊታቸውን ደግመው እስኪተኙ ውጭ ጨለማ ውስጥ ተቀምጦ ራቱን በልቶ መግባትና መተኛት፣ ጠዋት ውዳሴ ማርያማቸውንና ዳዊታቸውን ሲይዙ እናቱ
የሚያስጨብጡትን ቂጣ ቋጥሮ መውጣት የዘወትር ተግባሩ ሆነ።

ለእናቱ ቢያዝንም፣ ምኞቱና ፍላጎቱ ሁሉ ከዚያ የቁጭትና የበቀል ስሜት ከተጠናወተውና “የግዞት” ቦታ መሄድ ብቻ ከሆነ ሰንብቷል።የት እንደሚሄድ ያሰላና የወለተጊዮርጊስን ቁርጥ ሳያውቅ ቋራን ጥሎ ለመሄድ አንጀቱ አልችል ይለዋል።
ዛሬ ግን ወለተጊዮርጊስ ለንጉሥ መታጨቷን ሲሰማ ማመን አቃተው፤ ለዘላለም እንዳጣትም አወቀ። ከጥቂት ዓመታት በፊት ምስሏ በአሸዋ ሲዳፈን የተመለከተው ትዝ አለውና በእርግጥም ያ ንፋስ ንግርት
እንደነበረው ተረዳ ። ሕይወቱ በዐይኑ ሥር ስታልፍ፣ ስታመልጠው ተሰማው። ምንጊዜም ቢሆን የሚፈራውና ባሰበው ቁጥር የሚባንንበት፣
አካሉ ቦታ የማይበቃው የሚመስለው ነገር ዛሬ በመድረሱ አባቱን ወነጀለ።

ወለቴን ንጉሡ አልወሰዱብኝም፡ አባቴ አሳልፈው ሰጡብኝ እንጂ
አለ። እንባውን በኩታው እየጠራረገ፣ ለመሆኑ ወለተጊዮርጊስ ለንጉሡ
መታጨቷን ስትሰማ ምን ብላ ይሆን? መቸም ልብ ለልብ ተገናኝተናልና ምንስ ቢሆን እኔን ሳታስብ ትቀራለች? አለ፣ ሲተያዩ ፊታቸው ላይ የሚዋልለውን ደስታ እያሰበ። ስለምን እስታሁን ተያይዘን አልጠፋንም ነበር? ብንጠፋ ንሮ እኼ ሁሉ አይመጣም ነበር፡፡ ነገሩን እያሰበው ሲመጣ ድንጋጤውና ቁጭቱ ወደ ንዴት ተለወጡበት። ድንገት ንዴቱ እንደ ቋያ እሳት በሠራ አከላቱ ተሰራጨ።

እጆቹ ተንቀጠቀጡ፣ ጉሮሮው ደረቀበት፤ ቁና ቁና ተነፈሰ።
እናቱ ራቱን አመጡለት። መብላት እንደማይፈልግ ነገራቸው። ቤት
ውስጥ ተመልሰው ገብተው ቆሎ በአነስተኛ ቁና፣ ውሃ ደግሞ በቅምጫና ይዘው መጥተው፣ ቅምጫናውን መሬት ላይ አስቀምጠው ቁናውንም
በእጁ እንዲቀበላቸው ጥቂት አባብለው አስይዘውት አጠገቡ ተቀመጡ።

“አይዞህ የኔ ልዥ ። ዕድሜ ኻላነሰው፣ ጊዜ አለው ሰው ይላል ያገሬ ሰው። አንድ ቀን ሰው ትሆናለህ” ብለውት ለመውረድ ያቆበቆበውን እንባቸውን በእጅጌያቸው ጠራረጉ።

“እነየ አትጨነቂ።”

“ያባትህ ነገር መላ የለው ሁኖ አንተም ተቸገርህ። እኔስ እንዳሻው::ኸዝኸ ወዲያ ምን አረጋለሁ። የሳቸው ነገር ያስቸጋሪ በሬ ነገር ሆነ እኮ።”
“ያስቸጋሪ በሬ?”

“የሴቲቱ ባል ማልዶ ተነስቶ ወደርሻ ሲኸድ በሬው ገደል ይገባበታል።ዛዲያ ዳገት ላይ ቁሞ፣ 'ኧረ እርዱኝ በሬየ ገደል ገባ! ብሎ ይጮሀል። ያን ግዝየ ምሽቱ ኸቤት ትወጣና ኸየት ያመጣኸው በሬ ነው? በራሴ
በሬ' ብላው ትገባለች..” ሲሉ ጥላዬ ከት ብሎ ሲስቅ ትን አለው።

“ውሃ ፉት በልበት” አሉና ቅምጫናውን አቀበሉት። ውሃውን ጨልጦ ሲጨርስ ጠብቀው፣ “እናልህ እንደዛ ብላው ቤት ስትገባ ባልየው፣ ኧረ በሬያችን ገደል ገባ እርዱኝ አለ። ሴትየይቱ እንደገና ወጥታ፣ ኸየት
ያመጣኸው በሬ ነውና ነው በሬያችን ምትለው? የድሮ ባሌ የሰጠኝን ብላው ቤት ገባች። በመጨረሻ ሰውየው ሚለው ቢያጣ፣ እረ ያስቸጋሪ በሬ ገደል ገባ እርዱኝ አለ ይባላል አለ” አሉት።

ጥላዬ እንደገና ከት ብሎ ሳቀ። እናቱ ለሁሉ ነገር ምሳሌ የሚሆን
ተረትና ጨዋታ አላቸው። “አይ እነየ” ብሎ መልሶ ሳቀ። “የግዞት”
ቦታ የሚለውን ቤታቸውን እናቱ በተጫዋችነታቸው፣ ነገሮችን ቀለል አድርገው በማየታቸው፣ በተረቶቻቸውና በቀልዶቻቸው ነፍስ ባይዘሩበት ኖሮ፣ ኑሮ ከባላምባራስ ሁነኝ ጋር ምን ያህል አስቸጋሪ ሊሆን ይችል
እንደነበረና እናቱ የቻሉትን፣ የታገሱትን፣ ስቀውና ቀልደው ያሳለፉትን አሰበና፣ “እነየ ስንኳንም አንቺን ሰጠኝ” አላቸው።

ወይዘሮ ጌጤነሽ ሳቅ ብለው፣ “አየ ያንተ ነገር... እንኳንም አንተን
ሰጠኝ እንጂ አለበለዚያማ...” አሉት። ትንሽም ቢሆን ሊያስቁት
በመቻላቸው ደስ ብሏቸው፣ “አሁንስ ራት አትበላም?”

ራሱን በአሉታ ነቀነቀ።

ቅር እያላቸው ወደቤት ሲገቡ እሱ ስለ ሕይወቱ ማሰላሰል ጀመረ።
አንተ የወፍታው ምነው ዝም አልኸኝ? አለ ኹለት ነገር ጠይቄህ
ስንኳ አላውቅ። እኔ ልቤ ውስጥ እሳት አለ - ወለቴና ሥዕል፡ ወለቴን
ኸነጠቅኸኝ፣ ሥዕል መስጠት አቃተህ እኔ ጠበቅሁ፤
ጠበቅሁ፤ ሰው እስተመቸ ይጠብቃል? ለመጠበቅ ብቻ መፈጠርማ የለብኝም፡፡
ኸንግዲህ ምጠብቀው ነገር ስለሌለ ቋራ ሚያስቀምጠኝ ነገር የለም። እሳቸውን ችየ የኖርሁት ወለቴን አገባለሁ ብየ እንጂ፣ እሷ ለንጉሥ ኸተዳረችማ መኸድ በቀር ሌላ ምን አለኝ? ወለቴን ንጉሥ ኸወሰዳት እኔ የሥዕል ንጉሥ ማልሆን? አለ፣ ለራሱ።

ወለተጊዮርጊስን ማጣቱና እናቱን ለአባቱ ትቶ መሄድ ማሰቡ
ቢያሳዝነውም በወጣትነት ዕድሜው ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ በራሱ መወሰን መቻሉ ዐቅም ሆነው፤ አደፋፈረው፣ የነፃነት መንፈስ አለበሰው። አባቱ ከፊቱ የደነቀሩበትን ጋሬጣ፣ ዙርያውን የተበተቡበትን ገመድ
በጣጥሶ የወጣ መሰለው።
👍12🔥1