አትሮኖስ
280K subscribers
110 photos
3 videos
41 files
477 links
╔╦╦╦═╦╗╔═╦═╦══╦═╗
║║║║╩╣╚╣═╣║║║║║╩╣
╚══╩═╩═╩═╩═╩╩╩
ግጥሞች አዳዲስና ቆየት ያሉ የታዋቂ ደራሲያን መፅሐፍቶችን በ PDF እንዲሁንም
ያልተነበቡ ድርሰቶችን ግጥሞችን ታሪኮችን ያገኙበታል።


Contact. @atronosebot
please dont touch the leave button.😔😳😳
Download Telegram
#ጉዞ_በፀሎት
(አቃቂ እና ቦሌ)


#ክፍል_አስራ_ሶስት


#በዘሪሁን_ገመቹ_ዋቤ
፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧

እለቱ እሁድ ነው፡፡ከፊራኦል ጋር ለመውጣት ስለተነጋገሩ እየተዘጋጀች ነው፡፡ለሊሴ እየረዳቻት ነው፡፡
ሰው ከለገመ ከሻማ በላይ በቀላሉ ቀልጦ የሚጠፋ ከጠነከረ ደግሞ ከአልማዝም በላይ ማይቆረጥና ማይሸረፋ ተአምራዊ ፍጡር መሆኑን መረዳት ይቻላል፡፡በፀሎትም የማያልፍ የመሰላት አሰቃይ ህመም በጥቂት ቀናት ውስጥ ጥሏት ሄዶ ንፅህና ጤነኛ ልጅ ሆናለች፡፡የእግሯን ስብራት ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ድኗል…የፊቷ ቁስል ግን ምንም እንኳን ቢድንም ጣባሳውና ቁስለቱ አሁንም በግልጽ ፊቷ ላይ ይታያል… በዚህ ምክንያት አሳባ ከፊል ፊቷን ሁሌ በሻርፕ እንደሸፈነችው ነው፡፡ዋና ምክንያቷ ግን ማንነቷ በቀላሉ እንዳይለይ በማሰብ ነው፡፡አሁንም ተመሳሳይ አለባበስ አድርጋ በዛ ላይ ጥቁር መነፅር አይኗ ላይ ሰክታ ዝግጁ ሆነች፡፡

‹‹ግን እህቴ ለምንድነው እኔን የማታስከትሉት?››ለሊሴ ተነጫነጨች፡፡

‹‹አይ …መጀመሪያ ከወንድሜ ጋር የምንሄድበት ቦታ አለ…ባይሆን ከዛ ቶሎ ከጨረስን እንደውልልሽና ትቀላቀይናለሽ››

‹‹ይሁንላች ግን ታበሳጭቼባችኋለሁ››

በታክሲ ከሰፈር ሁለት ፌርማታ ያህል ርቀው ከሄዱ በኃላ ‹‹ደርሰናል እንውረድ›› አላት፡፡ያን ያህል ቅርብ ይሆናል ብላ አላሰበችም ነበር፡፡እንደወረዱ ቀጥታ ፊት ለፊት የሚገኝ በፅድና በባህርዛፍ አፅድ የደመቀ ሰፊ መናፈሻ ውስጥ ነው ይዞት የገባው…ቀጥታ ከሰው ነጠል ያለ ቦታ ይዞት ሄደና ቁጭ እንድትል መቀመጫ አመቻችቶላት ከፊት ለፊቷ ተቀመጠ‹‹እሺ ምን ትጠቀሚያለሽ?››

‹‹ቆይ እስኪ… ምን አስቸኮለህ…መጀመሪያ ትምጣ››

‹‹ማን?››

‹‹ምን ….ማንን ልናገኝ ነው የመጣነው…?ፍቅረኛህ ነቻ…በል ደውልላት፡፡››

‹‹ስልክ የላትም››

‹‹ታዲያ እንዴት ነው የምታገኘን››
‹‹የልቤን ምት አዳምጣ ትመጣለች››

‹‹ጥሩ ትቀልዳለህ….ይሄ የተለመደ መገናኛ ቦታችሁ ነው ማለት ነው…ገባኝ›› አስተናጋጁ መጣችና‹‹ምን ልታዘዝ ?››ብላ ጠየቀች፡፡

በፀሎት ቀደም ብላ‹‹ሰው እየጠበቅን ነው….››ብላ ለአስተናጋጆ መለሰችላት

‹‹አይ አሷን አንጠብቅም..ቆንጆ ፒዛ አሰሪልን…ፒዛው እስኪደርስ እሷም ትደርሳለች››

አስተናጋጆ ትዕዛዙን ተቀብላ ሄደች፡፡

ፊራኦል ወደእሷ አትኩሮ እያያት…..‹‹እስኪ ሻርፑን አንሺው››በማለት ያልጠበቀችውን ጥያቄ ጠየቃት

‹‹እንዴ ለምን?››

‹‹ሙሉ ፊትሽን ለማየት ፈልጌ››

‹‹ኖ ዌይ…..›

‹‹ምን ችግር አለው?››

‹‹እኔ  እራሴ  ሙሉ  በሙሉ  ፊቴ  እንደዳነ  እና  እንደማያስጠላ  እርግጠኛ  ስሆን እገልጠዋለው፡፡››

‹አንቺ እንዴት ልታስጠይ ትችያለሽ…ውብ እኮ ነሽ››

‹‹ሙሉ ፊቴን ሳታይ ውብ መሆኔን በምን አወቅክ…?››ኮስተር ብላ በመገረም ጠየቀችው፡፡

‹‹እኔ እንጃ ውብ እንደሆንሽ ግን እርግጠኛ ነኝ፡፡››

መልስ ልትሰጠው አፏን ስትከፍት አስተናጋጇ የታዘዘውን ፒዛ ይዛ ፊታቸው ስታስቀምጥ አፏን ያለምንም ንግግር ከደነች፡፡

‹‹‹ለእኔ እስፕራይት አምጪልኝ…..ላንቺስ ?›

‹‹እንዴ ልጅቷ ሳትመጣ….?››
‹‹ባክሽ የሆነ ነገር እዘዢ እሷ ስትመጣ የራሷን ነገር ታዛለች››

ግራ እየገባት አዘዘች …ፒዛውን ቆርሶ መብላት ሲጀምር ፣ በገረሜታ ተከተለችው… በልተው ጨርሰው እንኳን ልጅቷ አልመጣችም››

‹‹እንደዛ  ቅኔ  ምትቀኝላት  ልጅ  እስከአሁን  ካልመጣች  ከአሁን  ወዲያም  የምትመጣ አይመስለኝም፡፡››

‹‹መጣችእኮ››

‹‹የታለች?››

‹‹ይህቹት ፊት ለፊቴ ቁጭ ብላ እያወራቺኝ ነው፡፡››

‹‹እየቀለድክብኝ ነው እንዴ?››

‹‹እሺ አትበሳጪ..እኔ ምንም አይነት ፍቅረኛ የለኝም….አንቺን ወጣ አድርጌ ማዝናናት ስለፈለኩ ነው እንደዛ ያልኩሽ››

‹‹አንተ ውሸታም……..ቆይ ምንም ፍቅረኛ ሳይኖርህ ነው እንደዛ ፈዘህ በውድቅት ለሊት ቅኔ ስትዘርፍ የነበረው››

‹‹በተጨባጭ ፍቅረኛ የለኝም አልኩሽ እንጂ በምናቤ ስዬ የማስባት ሴት የለችም አላልኩሽም…..እንደዛ አወራ የነበረው በልቤ ውስጥ ተንሰራፍታ የተቀመጠችውን ልክ እንደአንቺ ውብ የሆነችውን ልጅ እያሰብኩ ነበር››

‹‹ምን አይነት አዝግ ልጅ ነህ….?እኔ ደግሞ እንዴት አይነት ቆንጆ ልጅ ትሆን እያልኩ ለሊቱን ሙሉ ሳስብና ስጓጓ ማደሬ››

‹‹ምን ያጓጓሻል…የፈለገ ውብ ብትሆን ካንቺ አትበልጥ…አንቺ እኮ ሁለመናሽ ውብ ነው…ማለት ስብዕናሽ ፖስቸርሽ..እርግጠኛ ነኝ መልክሽም ውብ ነው..ፍቅረኛዬ ልክ አንቺን ካልመሰለች ልቤን ማሸነፍ አትችልም››ፊራኦል ቀጥታ መንገር ፈርቶ ነው እንጂ ከበፀሎት ፍቅር ከያዘው ሰነባብቷል…ስሩ ሆና እራሱ ትናፍቀው ከጀመረች ቆይታለች..ለዛ ነው ሙሉ ፊቷን ማየት በጣም የናፈቀው…ቆንጆና ውብ ፊት ነው በምናቡ የሳለው…
‹‹ጥሩ ..ግን ስለውበትና ቁንጅና እኮ በእህትና በወንድም መካከል የሚወራ ኮንሰፕት አይደለም…..ባምርም ባስጠላም እንደእህትህ ነኝ…ለውጥ አያመጣም፡፡››

‹‹እንደእህት እና እህት ግን ይለያያል››

ለዚህ ንግግሩ ምን ብላ መልስ ልትሰጠው እንደምትችል ሊመጣላት አልቻለም…‹‹.እኔ የእህትህን ልብ በውስጤ የተሸከምኩ ሴት መሆኔን ብታውቅ ይሄን ሁሉ ርቀት ለመጓዝ አይዳዳህም ነበር››ስትል በውስጧ አብሰለሰለች

//////

በማግስቱ-----
እቤት ውስጥ ማንም የለም..ሌንሳ ብቻ ከበፀሎት ጎን ቁጭ ብላ እያወራቻት ነው፡፡
እህቴ ስራ በማግኘቴ በጣም ደስተኛ ሆኜያለው….ይገርምሻል ፀሀፊ ሆናለው ብዬ አንድም ቀን ኣስቤ አላውቅም ነበር…››

‹‹ላንቺ እኔ በጣም ደስ ብሎኛል… ስራውን ግን እንዴት ነው..እየለመድሽው ነው? ››

‹‹አሪፍ ነው ..ተመችቶኛል፡፡››
‹‹የፍቅርና የጋብቻ አማካሪ ነው ያልሽው?››

‹‹አዎ እህቴ …ብታይ ሰውዬው ማለቴ አለቃዬ በጣም ነው የሚያሳዝነው፡፡››

‹‹ለምንድነው የሚያሰዝነው? እሱም ፍቅር ይዞታል እንዴ?፡፡››

‹‹አይ እሱን አላውቅም … ያሳዝናል ያልኩሽ…ምንም ደንበኛ የለውም….ዝም ብለን እኔና እሱ ቢሮ ውስጥ ተፋጠን ነው የምንውለው…››ለምን ያሳዝናል እንዳለች ታስረዳት ጀመር፡፡

‹‹ምነው በስራው ጎበዝ አይደለም እንዴ?››

‹‹አረ በቅርብ ነው ከውጭ የመጣው..በሞያው ኤክስፐርት ነው…እንደነገረኝ ከሆነ አሜሪካ እያለ በሞያው ከሶስት አመት በላይ ሰርቶ በጣም ብዙ ሰዎችን ረዳቷል …እዚህ መጥቶ የራሱን ድርጅት ቢከፍትም እንዳሰበው አልሆነለትም….እንደምታውቂው የእኛ ሰው ድብቅ ነው …ባለትዳሮችም ቢሆኑ እዛው ቤታቸው ውስጥ ሲቋሰሉ ይኖራታል እንጂ ገበናቸውን ወደአደባባይ ማውጣት አያስብትም ..ባስ ቢልባቸው እንኳን እዛው የሰፈር ሽማጊሌ ጠርተው በምስክር ፊት ይጨቃጨቃሉ እንጂ ወደባለሞያ አይሄዱም፡፡ለዚህ ጉዳይ ባለሞያም እንዳለው የሚያውቅ የማህበረሰብ ክፍል አንድ ፐርሰንት የሚሞላ አይመስለኝም፡
‹‹ታዲያ እኮ የሰፈር ሽምግልናው ቀላል ነገር አይምሰለሽ…ሁለቱም ለእኛ ጥሩ ያስባል እና ያስማማናል የሚሉትን ሰው በማሀከላቸው አስቀምጠው ችግራቸውን በግልፅ በመነጋገር
ለመፍታት መሞከር ትልቅ ዋጋ ያለው ማህበራዊ እሴታችን ነው፡፡በዚህም መንገድ በጣም በርካታ ሺ ትዳሮች በየአመቱ ስንጥቃቸው ይደፈናል ስብራታቸው ይጠገናል፡፡››
👍6712🥰8👏3😱1
#ጉዞ_በፀሎት
(አቃቂ እና ቦሌ)


#ክፍል_አስራ_አራት


#በዘሪሁን_ገመቹ_ዋቤ
፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧

ሰላሞን የሆነ ሰው እየተጫወተበት እንደሆነ ነው የተረዳው‹‹ግን ማን ነው እንዲህ ያለ ጫወታ ከእኔ ጋር ለመጫወት የሚደፍረው?››በዙሪያው ያሉ ሰዎችን እያሰበ እራሱን እስኪያመው ቢያስጨንቅ በዙሪያው ካሉ ሰዎች እንዲህ መላ ቅጡ የጠፋበት ቀልድ ከእሱ ጋር ለመቃለድ የሚሞከር ሰው ሊመጣለት አልቻለም፡፡

ነገሩ ቀልድ እንዳልሆነ የተረዳው ልክ በተነገረው መሰረት ከሶስት ቀን በኃላ ተመሳሳይ ስልክ ሲደወልለት ነው፡፡በጉጉት አነሳው፡፡

‹‹ሄሎ..አወቅከኝ?››

‹‹መሰለኝ… አደናጋሪዋ ልጅ ነሽ አይደል?››

‹‹መሰለኝ….የባንክ ቁጥርህን ላክልኝ?››

‹‹ምን ለማድረግ?››

‹‹በተነጋገርነው መሰረት ስራ ማስጀመሪያ መቶ ሺ ብሩን እንድልክልህ ነዋ››

‹‹እንዴ? ስራው ምን እንደሆነ ሳላውቅ…ልስራው አልስራው መወሰን የምችለው እኮ ስራውን ሳውቅ ነው…መጀመሪያ በአካል ተገናኝነተን ስለስራው ማውራት አለብን››

‹‹ለጊዜው በአካል ላገኝህ አልችልም…ስራው በአባትና እናቴ መካከል ያለውን ችግር መቅረፍ ነው…እናትና አባቴ ያለፉትን 28 አመታት በጋብቻ አሳልፈዋል….እኔ ሀያ አንድ አመቴን ጨርሼ 22 ዓመት ውስጥ ነኝ…በእድሜዬ አንድም ቀን ሰላም ሆነው አይቻቸው አላውቅም…መኝታ  ለይተው  በየራሳቸው  መኝታ  ቤት  ነው  የሚያድሩት….ሁል  ጊዜ
እንደተጣሉና እንደተጨቃጨቁ ነው.ከዛም አልፎ አንዱ ሌለኛውን ለማስወገድም እስከመፈለግ የሚያደርስ ጥላቻ በመካከላቸው አለ..ወይ አይፋቱ ወይ እንደሰው የእውነት አብረው አይኖሩ፣….እና የፈለኩህ ይሄንን የሻገተና የበሰበሰ ጋብቻ የበሰበሰውን ቅጠል ከላዩ አራግፈህ የደረቀውን የጋብቻ ግንድ ቆርጠህ ከስር አዲስ የፍቅር ቅርንጫፍ እንዲያቆጠቁጥ እንድታደርግ ነው…ቢያንስ እንደባለትዳር መልሰው መተቃቀፍ ባይችሉ እራሱ እንደጓደኛሞች እንዲጨባበጡ ማድረግ እንድትችል ነው፡፡ይሄ ጉዳይ የእኔ የህይወቴ ትልቁ አላማ ነው…እባክህ ይሄንን ጉዳይ እንደጉዳይህ ልትይዘው ትችላለህ….?›››

‹‹በእውነቱ ከጠበቅኩት በተቃራኒ የሆነ መሳጭ ነገር እየነገርሺን ስለሆነ ቀልቤን ገዝተሸዋል…የምትይውን በደንብ እየተከታተልኩሽ ነው፡፡፡ለመሆኑ እኔን የምታናግሪው አባትሽ ወክለሽ ነው ወይስ እናትሽን…..?ማለት እኔን ለስራው እንድታናግሪኝ የጠየቀሽ ማን ነው?፡፡››

‹‹በእውነቱ ሁለቱም ስለዚህ ጉዳይ የሚያውቁት ነገር የለም….›

‹‹ይሄ ደግሞ ነገሩን ይበልጥ ውስብስብ ያደርገዋል..እሺ ቆይ ለመሆኑ እኔን ለምን…?እንዴት እኔን መረጥሽ?››

‹‹ለጊዜው ማንነቱን ልነግርህ የማልችለው አንድ አንተን የሚያውቅ ሰው ነው ሰለአንተ በሆነ ጉዳይ አንስተን ስንጨዋወት በጋብቻ ጉዳይ ላይ እንደምትሰራና በጉብዝናህም እንደሚተማመንብህ የነገረኝ..እንዳአጋጣ ሚ ሆኖ ደግሞ ያንን ሰው እኔ አምነዋለው…እሱ ጎበዝ ነህ ካለህ ጎበዝ ነህ ማለት ነው…

ተመለሰልህ?፡››

‹‹በከፊል አዎ…ግን እንደነገርሺኝ በወላጆችሽ መካከል ያለው ችግር ለረጅም አመት የተከማቸ የተወሳሰበና ዘርፈ ብዙም ነው፡፡››

‹‹በትክክል ገልፀኸዋል››

‹‹ችግሩ ምን መሰለሽ..በቀደም እንደነገርኩሽ አንድ የጋብቻ አማካሪ በጋብቻ መካከል የተፈጠረ ችግርን ለመፍታት የሚችለው ሁለቱም ተጋቢዎች በመሀከላቸው ችግር እንዳለ አምነው ያንን ለማስተካከል ከአማካሪው ጋር ለመተባበር ሙሉ ፍቃደኛ ሲሆኑ ብቻ ነው…አሁን ያንቺን ጉዳይ ስንመለከት ወላጆችሽ ጉዳዩን እንኳን አያውቁትም..ቢያውቁትም ፈፅሞ ከእኔ ጋር ለመስራት ላይቀበሉት ይችላሉ.››.

‹‹እሱን ለእኔ ተወውና አሁን የባንክ ቁጥርህን ላክልኝ… ገንዘቡን ትራንስፈር ላድርግልህ››

‹‹ይሄውልሽ ፣እኔ በነገርሺን ታሪክ በጣም ተስቤያለሁ…አንድ ወጣት ሴት በወላጆቾ ግንኙነት ተረብሻ እንዲህ ነገሮችን ለማስተካከል ስትጥር እኔም የበኩሌን እገዛ ለማድረግ ፍጽም ፍቃደኛ ነኝ..እዚህ ላይ ዋናው ገንዘብ አይደለም.. እሱ በሁለተኛ ደረጃ የሚመጣ ነው…አሁን መጀመሪያ አንቺ ራስሽ ወላጆችሽን ከቻልሽ አንድ ላይ አስቀምጠሸ ካልሆነም ለየብቻ ያሰብሽውን ንገሪያቸውና ለማሳመን ሞክሪ..እነሱ ፍቃደኛ ከሆኑ በኃላ ደውይልኝ..ከዛ ፕሮግራም እናወጣና ያለውን ችግር እያየን ለማስተካከል እንሞክራለን፡፡››

‹‹እነሱን በቀጥታ ማናገር አልችልም››

‹‹ለምን?››

‹‹ስሜ በፀሎት ኃይለልኡል ይባላል››

‹‹እሺ በፀሎት…ለምንድነው ወላጆችሽን ማናገር የማትችይው..?እነሱን ማናገር የማትቺይ ከሆነ እንዴት አድርጌ ነው ወላጆችሽን መርዳት የምችለው?››

‹‹ማለት ስሜን የነገርኩህ ስለእኔ የተወሰነ መረጃ እንዲኖርህ ነው..በፀሎት ኃይለልኡል በልና ድህረገፆች ላይ ወይም ማህበራዊ ሚዲያ ላይ ፈልግ ..ከ30 ደቂቃ በኃላ መልሼ ደውልልሀለው፡፡››አለችና ስልኩን ጆሮው ላይ ዘጋችበት፡፡

ስልኩ ቢዘጋም እሱ ግን ስልኩ ላይ እንዳፈጠጠ ነው…የገባው የመሰለው የልጅቷ ሁኔታ መልሶ እየተበታተነበት ነው‹‹…ድህረ-ገፅ ላይ ስለእሷ ምን…?ታዋቂ ሰው ነች ማለት ነው…?››

ጎግል ከፍቶ ››በፀሎት ኃይለመለኮት››ብሎ ሰርች መድረግ ጀመረ..በርካታ መረጃዎች ተዘረገፉ….እውነትም ይህቺ ልጅ ታዋቂ ነች መሰለኝ..ብሎ የመጀመሪያውን ሲያነብ

‹‹የታዋቂ ቢሊዬነሩ የኃይለመለኮት ብቸኛ ወራሽ በውድቅት ለሊት ከቤት ወጥታ ከጠፋች 14 ቀን አልፏታል፡፡››

‹‹ታዋቂው ቢሊዬነር ብቸኛ ልጅ በፀሎት ለምን ከቤቷ ጠፋች?››
‹‹በጸሎት ኃይለመለኮትን ያለችበትን የጠቆመ የ5 ሚሊዬን ብር  ሽልማት እንደሚሸልሙ አባቷ ለፋና ቴልቨዥን በሰጡት መግለጫ አሳወቁ››

በሚያነበው ዜና ሁሉ ደነዘዘ…..ማንበቡን አቆመና..ደወለላት

‹‹ሄሎ ..››

‹‹አሁን በመጠኑ ገባህ?››

‹‹ማለት አሁንም እንደጠፋሽ አይደለሽም አይደል…..?ማለቴ ወደቤት ተመልሰሻል?››

‹‹አይ  አልተመለስኩም…ወደቤት  እንድመለስም  እንደወጣው  በዛው  እንድቀርም የምታደርገኝ አንተ ነህ፡፡››

‹‹አልገባኝም››

‹‹ከእቤት የጠፋሁት የወላጆቼ ጭቅጭቅና የእርስ በርስ ጥላቻ ምርር ብሎኝ ነው….እኔ የእነሱን ሀብታቸውንም ሆነ ውርሳቸውን አልፈልግም፡፡ እኔ የምፈልገው ፍቅራቸውን ነው..ቢያንስ የሁለት ጓደኛሞችን አይነት እርስ በርስ የመግባባት እና የመረዳዳት ደረጃ ላይ እስኪደርሱ ወደዛ ቤት አልመለስም…እና እቅዴ ምን መሰለህ..ለእነሱ ደብዳቤ ፅፌ ልክልሀለው….በዛ ደብዳቤ ላይ ግልፅ የሆነ ፍላጎቴን አሰፍራለሁ…ማለቴ በግልፅ ከአንተ ጋር ሰርተው በማሀከላቸው ያለውን ግንኙነት ካስተካከሉ…እናም ያንን አንተ ካረጋገጥክልኝ ወደቤት እመለሳለው..ካለበለዚያ በቃ እኔም እነሱን እረሳለው አነሱም እኔን ይረሱኛል ማለት ነው፡፡›

‹‹በተሰቀለው..ነገሩ ካሰብኩት በላይ የተወሳሰበና ..አደገኛም ጭምር ነው፡፡››

‹‹ለዚህ እኮ ነው አምስት ሚሊዬን ብር እንድታገኝ የማደርግህ..ገብቷሀል አይደል አባቴ እኔን ላገኘ ወይም ያለሁበትን ለጠቆመ ሰው የ5 ሚሊዬን ብር ሽልማት አዘጋጅቷል ..ያ ማለት ነገሮች እንደተሳኩ እርግጠኛ በሆንኩ ጊዜ አንተ እንድታገኘኝና ለቤተሰቦቼ እንድታስረክበኝ አደርጋለሁ…እናም ለሽልማት የተዘጋጀውን ብር ከአባቴ ተቀብዬ ለአንተ አስረክብሀለው፡፡››
👍61🥰123