አትሮኖስ
286K subscribers
117 photos
3 videos
41 files
567 links
╔╦╦╦═╦╗╔═╦═╦══╦═╗
║║║║╩╣╚╣═╣║║║║║╩╣
╚══╩═╩═╩═╩═╩╩╩
ግጥሞች አዳዲስና ቆየት ያሉ የታዋቂ ደራሲያን መፅሐፍቶችን በ PDF እንዲሁንም
ያልተነበቡ ድርሰቶችን ግጥሞችን ታሪኮችን ያገኙበታል።


Contact. @atronosebot
please dont touch the leave button.😔😳😳
Download Telegram
#ህያብ
:
:
#ክፍል_አምስት


#ድርሰት_በኤርሚ


አንዳንዶች ለወደዱት ብቻ ጥሩ ይሆናሉ.... አንዳንዶች ደግሞ እንዲሁ በተፈጥሯቸው ጥሩነትን ይታደሉታል። ቢኒ እንደዛ ነው መልካምነትን የታደለ ጥሩ ልብ ያለው ልጅ ነው። ድሀ ወይም ሀብታም፣ ክርስቲያን  ሙስሊም ወይም ሌላ እምነት፣ ቆንጆ ወይም መልከ ጥፉ፣ ቢኒ ጋር መስፈርት አይደሉም። ለሁሉም እኩል ፍቅርና እንክብካቤ ሲሰጥ ታዩታላችሁ..... ግቢ ውስጥም ሆነ ከተማ ውስጥ ያሉ የበጎ አድራጎት ስራዎች አያመልጡትም.....

"ቢኒዬ ግን እርግጠኛ ነህ እዚህ ብሆን አረብሽህም.." እረጅም ሰዓት ተጨቃጭቀን እስከፈለኩ ድረስ ቤቱ እንድኖር ከነገረኝ በኋላ ሀሳቡን ቢቀይር ብዬ ጠየኩት

አጠገቤ መጣና ቁጭ አለ.... እጆቹን ልኮ ሁለት እጆቼን ያዘና አይን አይኔን እያዬ "ህዩ አንቺ ጓደኛዬ ነሽ... ጓደኝነት ውስጥ ደግሞ እኔ የሚባል ነገር የለም በተለይ እኔ ካንቺ እኔን ላስቀድም አልችልም ምክንያቱም......" ከንፈሮቹ ተንቀጠቀጡ።

"ምክንያቱም ምን ቢኒዬ" እጄን ለቆ ተነሳና ጀርባውን ሰቶኝ ከመስኮት ዳር ቆመ።

"ህያብ ጊዜ የነገሮች ጌታ ነው ብዬ አምናለሁ... እናም ሁሉም በጊዜው ሲሆን ደስ ይላል። አሁን ከኔ ምክንያት በላይ ያንቺ ሁኔታዎች ናቸው መስተካከል ያለባቸው...." ክትክት ብዬ ሳቅሁ... የእብደት ሳቅ
ከሳቄ በኋላ

" እስኪ ንገረኝ ምኑን ነው የምታስተካክለው.... እናቴን ልጄን ወይስ ከሀዲው ባሌን ማንን መልሰህ ልታመጣልኝ የምትችል ይመስልሀል..." ድጋሚ አመመኝ... መቋቋም አቃተኝ... በሁለት እጄ ጭንቅላቴን ጥፍንግ አድርጌ ያዝኩት። የሆነ ሽክርክሪት ውስጥ እንዳለሁ ይሰማኛል ዥውውውውውውውው.... ሳቅ ከዛ ደግሞ ዝምምምምታ.... ከዛ ደግሞ ሌላ ሳቅ.... ይሄኛው አለም የተሻለ ይመስለኛል።

የሆነ ሰው አፌ ውስጥ የሆነ ነገር ለማስገባት ታገለኝ አልከለከልኩትም ዋጥኩት ከዛ ሁሉም ነገር ፀጥ አለ።

ምን ሰዓት እንደተኛሁ ባላውቅም ራሴን ጋቢ ለብሼ ሶፋ ላይ ተኝቼ አገኘሁት። ቀና ብዬ ተስተካክዬ ቁጭ ስል ቢኒን ከእግሬ ስር ቁጭ ብሎ መፅሀፍ ቅዱስ ሲያነብ አየሁት።

"ይቅርታ ቢኒ ረበሽኩህ መሰለኝ.." መፅሀፍ ቅዱሱን ዘግቶ ከሳመ በኋላ የኔንም ግንባር ነካ አደረገበትና ተነስቶ አስቀምጦ ተመለሰ።

"ሁለተኛ እንደዚህ እንዳትይኝ ማስቸገር ገለመሌ የሚባል ታሪክ የለም ያራቅሺኝ ነው የሚመስለኝ..."

"እሺ በቃ አይለመደኝም..... ይልቅ እስኪ ንገረኝ የውጪ ቆይታህ እንዴት ነበር የተመለስከውስ መች ነው"

"ቆይታዬን በደፈናው ጥሩ ነበር ልበልሽ መሰለኝ። የተመለስኩት ሁለት ወር አካባቢ ሆነኝ ግን ቀጥታ ቤተሰብ ጋር ክፍለ ሀገር ነው የሄድኩት ከተመለስኩ ገና ሳምንትም አልሞላኝ"

"እና ለምን ልትፈልገኝ ወደ ቤት አልመጣህም..." ክፍት ነው ያለኝ ምንም እንኳን የሱን ስም ሲሰማ ባሌ ቢናደድም ቢኒ ላጣው የማልፈልገው ጓደኛዬ ነው እና እንዴት...

"ወዳንቺ ጋር እየመጣሁ እያለ እኮ ነው መኪና ውስጥ የገባሽብኝ"

"ኦ እሺ እንደዛ ከሆነ"

"አልተዋጠልሽም አይደል ህያቤ ብዙ ጊዜ እንዳልደወልኩልሽ አውቃ..." አቋረጥኩት

"ምን ብዙ ጊዜ ትላለህ ከሄድክ ጀምሮ ሁለቴ ብቻ እኮ ነው የደወልከው.... እናም አልዋሽህም ተቀይሜሀለሁ"

"ምክንያቴን ስታውቂ እንደምትረጂኝ ስለማውቅ ችግር የለውም.... የሆነ ነገር መብላት አለብን ምን ትፈልጊያለሽ..." አለኝ ወደ ኪቺን እየገባ

"ፍላጎትሽን አትናገሪም ካለዛ ዱባ ወጥ ነው የምሰራው ሀ ሀ ሀ" ሽርጡን አገልድሞ ብቅ አለ

" ዱባ ስራና ሶስት ቀን ውጪ አሳድሬ ነው የማበላህ.... አንተ ደግሞ ሼፍ መስለህ የለም እንዴ"

"ነይ አሁን ተነሺ ቢያንስ ዱባውን እንኳን በመክተፍ አግዢኝ" ከስሙ ጭምር እንደምጠላው ስለሚያውቅ እኮ ነው ...ዱባን....

"ሀ ሀ ሀ አንተ እብድ ትቀልድብኛለህ አ" ከረጅም ጊዜ በኋላ ሳቅሁ
......

፨፨፨ ፨፨፨፨ ፨፨፨፨
ጎንደር ዩንቨርስቲ ሁለተኛ አመት

"ቢኒ ዮናታንን እወደዋለሁ ከዚህ በላይ መቋቋም አልችልም እናም እነግረዋለሁ"

"ህያብ ዮናታንን ታውቂዋለሽ.... እሺ አለሽ እንበል ከዛ እነኝህን ሁሉ ሴቶች ትቶ ካንቺ ጋር ብቻ የሚሆን ይመስልሻል"

"አላውቅም ግን እድሌን ልሞክር.."

"ተይ ህያብ ይቅርብሽ"

"አይሆንም ቢኒ እድሌን እሞክራለሁ" ይሄን ሁሉ የምንጨቃጨቀው ዮናታን የሚያመሽበት ጭፈራ ቤት በር ላይ ሆነን ነው። ወደ ውስጥ ገባሁ... አይኔን ዞር ዞር እያደረኩ ፈለኩት ጥግ ሶፋ ላይ ከአንዲት ሴት ጋር የተሰፋ ያክል ተጣብቋል.... በደንብ ቀረብኳቸው... አንገቱ ስር ስማው ቀና ስትል አይን ለአይን ተገጣጠምን... የትናዬት....

ደንዝዤ አንደቆምኩ የሆነ ሰው እጅ ትከሻዬ ላይ አረፈ "የኔ ቆንጆ በዛኛው በኩል ቦታ አግኝቻለሁ.... እንሂድ አይደል"  ውጪ ቆይ አላልኩትም ነበር.... ቢሆንም ግን ወሳኝ ሰዓት ላይ ነው የደረሰው።

"አየሽ አይደል በራስሽ ላይ ምን እያመጣሽ እንደሆነ"

ሲጀመር እሱን ብቻውን አገኘዋለሁ ብዬ ማሰቤ ነው የኔ ጥፋት እርር ድብን ብሽቅቅቅቅ ብያለሁ እኮ

"አረጋጊው እንጂ ውዷ ጉበትሽን መትፋት አማረሽ እንዴ"

"ተወኝ ባክህ ልጠጣበ" ከነ ጠርሙሱ አንስቼ ለመጠጣት ስሞክር ከእጄ ቀማኝና

"ነይ በቃ እንሂድ ግቢ ይዘጋል" አለኝ

"የትም አልሄድም ተወኝ"

"ይሄንን ነው መፍራት... ኧረ ህያብ በፈጠረሽ..." ጠርሙሱን ተቀብዬው እየተንገዳገድኩ እነሱ ወዳሉበት ቦታ ሄድኩ....

"ህያብ አንቺ ህያብ" የእናቴ ድምፅ መሰለኝ.... እየጠራችኝ ነው።

"አቤት እማ መጣሁ" ብዬ ከተኛሁበት ለመነሳት ስሞክር ሀይለኛ ራስ ምታት አናቴን ይዞ እየፈለጠኝ ነው። ጭንቅላቴን በሁለት እጄ ጥፍንግ አድርጌ ይዤው ከቆየሁ በኋላ አይኔን በደንብ ከፍቼ ሳይ ያለሁት እናቴ ቤት አይደለም....

ከፊት ለፊቴ ቢኒ ተቀምጦ የማደርገውን ነገር ያያል።

"ኡፍፍፍፍ የት ነው ያለሁት ምን ተፈጥሮ ነው.... ቆይ እማዬ የጠራችኝ አልመሰለኝም.."

"ባክሽ እኔ ነኝ የጠራሁሽ ክፍል ልቀቁ እየተባልን ነው ተነሺ..." ቢኒ እንደዚህ አውርቶኝ አያውቅም....

"ምንድነው ቢኒ ችግር አለ እየተነጫነጭክ እኮ ነው ምነው ማታ አስቀየምኩህ እንዴ.... ማታ....ቆይ ቆይ እንዴት ወደዚህ ልመጣ ቻልኩ? ማነው ያመጣኝ? ማለት ምን ተፈጥሮ ነው?..." የጥያቄ መአት አከታተልኩበት

"በመጀመሪያ ተነሽና ታጠቢ ከዛ ወደ ግቢ እንመለስና ዶርም ገብተሽ እረፍት አድርጊ ከዛ ተገናኝተን ጥያቄዎችሽን እመልስልሻለሁ እስከዛው ትዝ የሚልሽ ነገር ካለ ራስሽ ጥያቄሽን መመለስ ትችያለሽ" እንዴ ምንድነው ጉዱ ቢኒ እንደዚ ከረር ብሎ አይቼው አላውቅም ጭራሽ የማላውቀው ሰው ነው የሆነብኝ። ተጨማሪ ጥያቄ ሳልጠይቅ ጭንቅላቴን ደግፌ እየተጎተትኩ መታጠቢያ ቤት ገባሁ።
ሰውነቴ ስብርብር ያለ ያክል እየተሰማኝ ታጥቤ ጨረስኩ

፨፨፨፨ ፨፨፨፨፨ ፨፨፨፨፨

"አንተ ቢኒ ግን አልተኛህም እንዴ አይንህ እኮ በርበሬ ነው የሚመስለው" ወደ ግቢ እየሄድን ጠየኩት
👍448😁1
#ተአምራተ_ኬድሮን


#ክፍል_አምስት


#በዘሪሁን_ገመቹ_ዋቤ

///

እለቱ እሁድ …ሰማይና ምድሩ ከመላቀቁ በፊት በሚባልበት  የለሊቱ የጊዜ ክፍል ላይ ነው፡፡ ኦርቶዶክሶቹ ቤተሰቦቾ ተነስተው  አምላካቸውን ለመማፀን ቅ/ሚካኤል  ቤተክርስቲያን ተያይዘው ግቢውን ለቀው እንደወጡ እሷም ተስፈንጥራ መኝታዋን ለቀቀችና እቤቱን በታናናሽ ወንድሞቾ ላይ ከውጭ መለስ አድርጋባቸው ግቢውን ለቃ  ቁልቁለቱን በመንደርደር እንቅፍት እያላተማት  ወደ ያዶት ሩጫዋን ቀጠለች..ይገርማል ጄሬካን እንዳልያዘች  እንኳን ትዝ ያላት  የወንዙን የለሊት ሿሿታ ድምጽ ለጆሮዋ ከደረሰ በኃላ ነበር፡፡

‹‹ወይ ጉዴ….ምን መሆኔ ነው …? እሱስ እንዴት ይታዘበኝ…?›ስትል በውስጧ እራሷን ታዘበች፡፡
እንደዛም ቢሆንም ግን እርምጃዋን አልጋታችም ….ቀጥታ ወደ ወንዙ አመራች…፡፡ በእለቱ  የተለየ መንቀዥቀዥ፤ የተለየ መቀበጥበጥ.፤የተለየ መቁላላት 🤭 እየታየባት  ነበር… ምክንያቱ ስታስብ ሀሳቡን ካልቀየረ በስተቀር  እቤቴ እወስድሻለሁ ስላላት ያ በውስጧ የፈጠረባ ጉጉተና ደስታ ይመስላታል… .‹‹.እስኪ እሱ ቤት መሄድ እንዴት ነው እንደዚህ ሊያጓጓኝ የቻለው..?›እራሷን ጠየቀች፡፡

ከዚህ በፊት ዘመድ ካልሆነ በስተቀር ወንድ ልጅ ቤት ሄዳ ጣዕሙን ቀምሳ  እንኳን አታውቅም…
.‹‹ወስዶ ሌላ ነገር ቢያደርገኝስ…?››.ሀሳቡን በማሰቧ እራሱ ሰውነቷ  ተንቀጠቀጠባት……ማድረግ ቢፈልግ ስንት ቀን ሙሉ በውድቅት ለሊት ማንም በሌለበት እየተመላለሰችለት አይደል…? እርቃን ገላዋን ከገላው አጣብቃ ስትዋኝ አልነበር እንዴ?እንደዛ ማድረግ ቢፈልግ ማን ይከለክለው ነበር….?እንደዚህ ማሰቧ አጽናናት ፤ እና ፈገግ አለች፡፡

‹‹ ..ፈገግታሽ ያምራል››አላት ወንዝ ውስጥ ብቅ ጥልቅ እያለ ..ለካ  ሳታስበው ደርሳ  ወንዙ ጠርዝ አካባቢ ቆማ ነበር በሀሳብ ስትባዝን የነበረው፡፡

‹‹ደህና አደርክ››አለችው  እንደመባነን ብላ

‹‹አዎ አድሬለሁ…ነይ ግቢ››አላት

‹‹ወዴት ነው የምገባው?››

‹‹ወደ ወንዙ ነዋ››

‹‹አልገባም …ቀጠሮ እኮ ነበረን ፤እረሳኸው እንዴ…?››

በሚያበሽቅ ና ተስፋ በሚያስቆርጥ የንግግር ቃና‹‹የምን ቀጠሮ?›› አላት ፡ 

ትንሿን ለንቦጯን ጥላ‹‹ተወው በቃ››አለችው፡፡ 

ፈገግ አለና‹‹..ኩሪፊያሽን እኮ በጣም ስለምወድልሽ ነው..እቤቴን ላሳይሽ አይደል ቀጠሯችን….?ነይ ግቢና አምስት ደቂቃ አብረን ዋኝተን እንሄዳለን..››

‹‹አምስት ደቂቃ ብቻ!!!››

‹‹አዎ.. አምስት ደቂቃ ብቻ››
‹‹..ተስማምታ  ቀሚሷን አወለቀችና ደረቅ ቦታ አጣጥፋ በማስቀመጥ በፓንት  ብቻ  ዘላ እጠገቡ ቦጭረቅ አለች››..….አንጠልጥሎ አቀፋትና ይዞት ወደ ውሀ ውስጥ ሰመጠ …ከእቅፉ ለመውጣት ተንፈራገጠች… አልቻለችም፡፡ ይዟት ውስጥ ለውስጥ እየዋኘ ነው፡፡ ሳታስበው ከንፈሩን ከንፈሯ ላይ አጣበቀው..የሆነ በቃላት ልትገልፀው  የማትችለው የኤሌክትሪክ ንዝረት አይነት ሞገድ ከጎረሰው ከንፈሯ ተነስቶ እላይ ጭንቅላቷ. ድረስ እንደገና ከዛው ከተጎረሰው ከንፈሯ  ተነስቶ ወደታች እግር ጥፍሯ  ድረስ በመሰራጨት አንዘፈዘፋት ….የምትዋኝ ሳይሆን የምትንሳፈፍ ነበር የመስላት… ለ5 ደቂቃ በእንደዛ አይነት ሁኔታ ውስጥ ለውስጥ ከዋኙ በኃላ የተደረመሰ ጉድጓድ  ያለው  የመሬት ስንጥቅ የወንዝ ወለል ላይ  በአይኗ  ገባ ….
‹‹አለየውም ይሆን ?››ብላ በማሰብ  ልታስጠነቅቀው ፈልጋ ለመናገር ከንፈሯን ለማለቃቀቅ ብትጥርም አልቻለችም …ይዟት እያመራ ያለው ወደዛው አቅጣጫ ነው….የሚያስፈራ አይነት ጉድጓድ ነው …እንደውም አስፈሪ የአውሬ አፍ ይመስላል…ዳሩ ምንም ማድረግ ሳትችል ይባስ ብሎ ከንፈሩን ከከንፈሯ ሰውነቱን ከሰውነቷ እንዳጣበቀ በስንጥቁ መሬት  አፉ ውስጥ    ገባና ወደጥልቁ. ይዞት  ጭልጥ አለ….

‹‹ወይኔ ልጅት …..ምን አይነት ተአምር ነው….?ምን አይነት ቀበጥ ልጅ ነኝ…?እንዴት ደፍሬ ነው ከዚህ ሰይጣን ጋር የተወዳጀሁት…?.መወዳጀቱንስ እሺ ልወዳጅ እንዴት የማያስብ አዕምሮ ቢኖረኝ ነው ቤትህን ካላሰየህኝ ብዬ ወጥሬ የያዝኩት…?›ስትል ግትልትል ጥያቄዎችን እራሷን ጠየቀች…መልስ መላሽ ግን አልነበረም .. ወደ ሲኦል ይዞት እየጠለቀ ያለ ነው የመሰላት…, ‹‹ግን ሲኦል የት ነው የሚገኘው››.…..? ከምድር በላይ ሰማይ ላይ ነው ወይስ ከምድር በታች ካለ ስምጥ ጨለማ ውስጥ….?አይ አሁን ይዞኝ እየሰመጠ ያለው ከምድር እንብርት ከሚገኝ ጨለማ ነው   ..››በፍራቻ ተቀፍድዳ ነፍሷ ጭምር እየቃተች ቢሆንም እዕምሮዋ ግን በሀሳብ ግትልትል ከመብሰልሰል እራሷን መግታት አልቻለችም፡፡ አዎ ምንም እየታያት አይደለም‹‹….ደግሞ አንደርስም እንዴ…?›አለች ፡፡

..በቃ ሲኦል ውስጥ መቼስ ያለው የሚንቀለቀል እቶን እሳት ነው…ነፍስ አባቷ ብዙ ጊዜ ሲናገሩ ሰምታለች…አይ እሳት ብቻም አይደለም ሰውነትን የሚበጣጥስ ቀዝቃዛ በረዶም አለ ብለዋታል…‹‹ግን እቶን እሳት እና ቀዝቃዛ ግግር በረዶ በአንድ የሲኦል ካምፕ ውስጥ እንዴት መገኘት ይችላሉ…?ሁለቱ እርስ በርሳቸው አይጠፋፉም እንዴ…?››ሀሳቧ ለራሷ አስገረማት.‹‹ የእኔ ነገር አሁን ስለዚህ የማስብበት ሁኔታ ላይ ነኝ…?›› ቤተሰቦቾን እሬሳዋን እንኳን ሳያገኙት ቀጥታ በጎሮ በር ወደሲኦል መሄዷ በጣም ልብ ሰባሪ ገጠመኝ ነው የሆነባት…?ከሀሳብ ቅርቃር ውስጥ ሳትወጣ  ከንፈሩን ከከንፈሯ  ድንገት ሲያነሳ የተለየ አዲስ አይነት ከልብ የመነጠቅ አይነት ስሜት ተሰማት ፡፡

…አዎ እግሮቾ ለስለስ የሚል ነገር ላይ ቆመዋል…እጆቹ ከሰውነቷ ተላቀቁ  .. ሰውነቱንም ከሰውነቷ አለያየው… ግን በጨለማ ደብዝዞ እና ጨፍና  የነበሩትን አይኖቾን መግለጥ ፈራች…‹‹.ሲኦል ደርሰናል ማለት ነው..?››ስትል ጠየቀች.. ግን የእሳቱም ወላፈን እያቃጠለት አይደለም.. የበረዶው ቅዝቃዜውም ለሰውነቷ እየተሰማት  አይደለም…በተቀራኒው   ከገነት የሚመነጭ አይነት   አየር በአፍንጫዋ እየሳበች  ነው::እንደዛ መሆኑ ደግሞ ጥሩ ነገር እንዲሰማት  እያደረገ ነው፡፡

‹‹ደርሰናል ግለጪ››የሚል ድምጽ ሰማች…

ይቀጥላል
👍165😱3720👏1
#ትንግርት


#ክፍል_አምስት


#በዘሪሁን_ገመቹ_ዋቤ


ለታደሉ ጋብቻ ገነታዊ ደህንነት የተላበሰ የደስታ ቅፅር ይሆንላቸዋል ለሌላው ደግሞ በእቶን እሳት የታጠረ ሲኦላዊ የግዞት ቦታ ነው…፡፡

ከሠዓት በኋላ ወደ ማተሚያ ቤት መላክ ያለባቸውን የጋዜጣ ፅሁፎችን ለመጨረሻ ጊዜ ተመልክቶ ጨረሰና በድካም ስሜት ወደ ኋላው ተንጠራራ፡፡ለወትሮ ለአስራ ስድስት ሠዓት ያለዕረፍት ሲሠራ የድካም ስሜት የማይሠማው ሠውዬ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የሁለት እና ሦስት ሰዓት ስራም ያዝለው ጀምሯል፡፡

‹‹ኢንጅነር ሠሎሞን ዛሬ ደግሞ ምነው ይበልጥ አጠርክ?›› ድንገት በራፉን ከፍቶ ወደ ቢሮው እየገባ ያለውን ጓደኛውን በተረብ ተቀበለው፡፡

‹‹ዓይንህ ነው››

‹‹አይመስለኝም፡፡ ኧረ ይሄንን ቦርጭ ቀንስ፡፡ የድሮዎቹ ኢንጅነሮች ኪሳቸውን ብቻ ነበር የሚቆዝሩት፤ያሁኖቹ ደግሞ ሆዳችሁንም ሳይቀር በስብ ትቆዝራላችሁ፡፡››

‹‹ባክህ አትጨቅጭቀኝ፡፡›› በማለት ወንበር ስቦ ፊት ለፊቱ ተቀመጠ ፡፡

‹‹ፕሮጀክትህን ለማየት ባህርዳር የሄድክ መስሎኝ ነበር?››

ቀረሁ ባክህ ከሶስት ቀን በኋላ የልጆቼ ልደት ነው፤ ዘንግቼው ነበር ሄዳለሁ ያልኩህ፡፡››

‹‹ኦ ..! መንታዎቹ ስምንተኛ ዓመታቸው መሆኑ ነው? >>

‹‹አዋ! ደረሱልኝ፡፡ ብቻ ለአቅመ ሄዋን ሲደርሱ እንደአንተ አይነቶቹን አዳሞች ከምድር ሚጠራርግልኝ ነገር ቢፈጠር ፍቃዴ ነው፡፡››

‹‹እንዴት ባክህ?›› ሁሴን በገረሜታና በፈገግታ ጠየቀው፡፡

‹‹ምን እንዴት ትለኛለህ...በሄዋኖች ላይ እየተጫወትክ፤ ደግሞ በቀደም ምንድነው የሠራኸው?››

«...ምን ሰራው?»

‹‹ሁለቱን ሴቶች በአንድ ላይ ጠርተህ ልታቧቅሳቸው ነው ወይስ ልታሳስማቸው?››

‹‹ኧኧ .. ማን ነገረህ ደግሞ?››

‹‹ኤደን ደውላልኝ ተገናኝተን ነበር፡፡ የእሷ ልጅ እምባ ከፀረ አርያም የደረሠ ቀን ምን እንደሚውጥህ እኔ አላውቅም፡፡ ቆይ ምን እያስነካሀቸው ነው እንደሙጫ ተጣብቀው እኝኝ የሚሉብህ?›› ግርምት በተቀላቀለ ስሜት ነው የሚጠይቀው፡፡

‹‹እሱን እራሳቸውን ብትጠይቃቸው አይሻልም ..ቆይ ምን ሆንኩ አለችህ?››

‹‹እሷማ በእሱ ያልሆንኩት ነገር የለም ነው የምትለው...እኔም እውነቷን ነው እላለሁ፡፡ እንደውም ምን እንዳልኳት ታውቃለህ፡፡ይሄን ያህል ከተንገሸገሺበት ተይው፤ እኔም በሚስቴ ተማርሪያለሁ፤ ስለዚህ ልፍታትና እንጋባ፤ሁለት ብሶተኞች ቢገናኙ የደስታ ኑሮ ሊገጥማቸው ይችል ይሆናል፡፡ ››አልኳት፡፡

‹‹ድንቅ መፍትሄ ነው፤እንደተስማማች እገምታለሁ፡፡››

‹‹ምን ትስማማለች፡፡ እኔ በቁም ነገር ችግሬን ሳዋይህ አንተ ታሾፋለህ አለችኝ፡፡ አልተረዳችኝም እንጂ እኔስ ከአንጀቴ ነበር፡፡ ያቺን የመሠለች መልዐክ ከእንዳንተ አይነቱ ነጂስ ባድናት እርግጠኛ ነኝ ከፃድቃን ተርታ ያሰልፈኛል፤እኔም ከዛች መሠሪ ሚስት ተብዬ እገላገል ነበር፡፡››

‹‹መስሎሀል... ያህቺ አሁን መልዐክ የመሠለችህ ወደ ትዳር ይዘሀት ስትዘልቅ የባሰች ሠይጣን ልትሆን ትችላለች፡፡

ከማግባትህ በፊት ለየውብዳር እንዴት
ትንሰፈሰፍላት እንደነበር ዘነጋኸው? የፍቅር
ግንኙነትና የጋብቻ ጥምረት ፍፁም የተለያዩ ሂደቶች ናቸው፡፡አየህ በፍቅረኝነት ሃያ ሠላሳ ዓመት ጣፋጭ የስምምነት ህይወት መኖር
እምብዛም የሚከብዱ አይደለም፡፡ ምክንያቱም
የተወሰነ ክፍተት .. መፈናፈኛ ቦታ .. ነፃነት
እንዲሁም እኔ እና እሱ የሚል ልዩነት አለና፡፡

በጋብቻ ውስጥ ግን ከተወሰኑ ዓመታት በላይ
ፍቅርን ከእነ ጣዕሙና ወዙ ማቆየት ለጥቂቶች ብቻ ነው የሚቻለው፡፡ እኔ እና እሷ የሚለውን ቃል ፍፁም ደምስሶ እኛ በሚለው ቃል
ለመተካት ጥረት ይደረጋል፡፡ ዳሩ ግን ሃያ ሰላሳ ዓመት በተለያየ የኑሮ ዘየ በተለያየ ቤተሰብ ውስጥ የኖሩ ሁለት የተለያዩ ግለሰቦች አንድ
ይሆናሉ ብሎ ማሰብ በራሱ እብደት ነው፡፡

የፍቅር ተቋም ከጋብቻ ተቋም ፍፁም የተለየ
ነው፡፡አየህ አብዛኞቹ በምድራችን የተከሰቱ
የፍቅር ታሪኮች (ልብ ወለዶቹ ሳይቀሩ)
የሚያረጋገረጡት ይህንን ሀቅ ነው፡፡

የሼክስፒሮቹ ሮሚዮና ጁልዮት፤ የአዲስ አለማየሁ በዛብህና ሠብለ ወንጌል ሁሉም በመከራ እንጂ በጋብቻ አልተፈተኑም፡፡ምን ' አልባት ተሳክቶላቸው ከዛ ሁሉ የህይወት ፈተና በኋላ ወደ ጋብቻ አምርተው ቢሆን ኖሮ ዛሬ ታሪካቸው ሌላ መልክ ይይዝ ነበር፤በፍቺም ሊጠናቀቅ ይችል ነበር፡፡ፈተና ለፍቅረኞች ብርታት ነው፣ ወኔ ነው፣አቅም ነው፡፡ በተለይ ሁለቱን ለመነጣጠል የሚደረግን ማንኛውንም አሻጥርን ለመበጣጠስ ያላቸው እምቅ ጉልበት ከኒውክሌር ይስተካከላል፡፡ ጉልበታቸው የሚመነጨው ከፍቅራቸው ብቻ ሳይሆን ከመከልከላቸው ውስጥ ነው፡፡ መከልከል ከሠው ልጅ የስነ ልቦና ታሪክ ጋር ትልቅ ትስስር አለው፡፡››

‹‹ገባኝ፡፡ ያንተዋ ኤደን ቢጤ ማለት ነው፡፡ ይሄኔ ላግባሽ እያልክ ብትለምናት ኖሮ ጉዳዩ ተቃራኒ ይሆን ነበር፡፡›› ሠሎሞን ነው ቦርጩን እያሻሸ በመሀከል ገብቶ ሀሳብን የሠነዘረው፡፡

ሁሴን ንግግሩን ቀጠለ ‹‹በተወሰነ መልኩ ትክክል ነህ፡፡ የሠው ልጅ የተከለከለውን ነገር
ለመጨበጥ ቀን ከሌት ይጥራል፡፡ እስኪሳካለትም እረፍት አልባ ይሆናል፡፡ ስለ ግብ አይጨነቅም፡፡ የተከለከለውን በእጁ ካላስገባ ደካማ ነኝ ብሎ ያስባል እንጂ ነገሩ ለእኔ ምን ያህል ያስፈልገኛል፤ ከውስጣዊ ፍላጎቴስ ጋር ምን ያህል ትስስር አለው? ብሎ መጨነቅ ብዙ አይስተዋልበትም፡፡ የአብዛኞቻችን የፍቅር ታሪክም ይህን መሠል ነው፡፡የፍቅር ጉዞ ይጀመራል... በጉዞ ውስጥ እንቅፋት ይደነቀራል.... በዚህ ወቅት ፍላጎት በእጥፍ ይጨምራል፡፡ እንቅፋቱን ለማስወገድ የዓመታት ፍልሚያ ይጀምራል፡፡ በፍልሚያው ሜዳ ላይ  የሚከፈለው የመስዋዕትነት መጠን የፍቅር መጠን መለኪያም ተደርጎ ይወሠዳል፡፡ የታገለ ማሸነፉ ወይም መሸነፉ አይቀርምና በመጨረሻ በስኬት ከተጠናቀቀ ቀጥታ ፍቅር ወደ ጋብቻ ይሸጋገራል፡፡ክፍተት የሌለበት ውህደት፤ አንዱ የሌላው የግል ንብረት ይሆናል፡፡ታዲያ ሲሰነባብት ጀብዱ የለ...ትግል የለ...ግራ መጋባት ይከሰታል፡፡ከውጭ የሚታገላቸው ሲያጡ ፊታቸውን ወደ ጋብቻ




ተጣማሪያቸው ያዞራሉ፤እርስ በርስ ፍትጊያ ይጀመራል…፡፡ ውጫዊ ትግል በውስጣዊ ጭቅጭቅና አንባጓሮ ይተካል፡፡ እሱ እሷ ላይ ይጮኸል…እሷም እሱ ላይ ታንቧርቃለች፡፡ በስተመጨረሻም ውጤቱ ሁለት ይሆናል፤ አንድም የትግሉ ውጤት በመሸናነፍ ይጠናቀቅና ‹ጨዋታ ፈረሠ ዳቦ ተቆረሠ› ተብሎ ትዳሩ ይፈርሳል፤ሁለተኛው ደግሞ ለይሉኝታ ሲባል .. በመሀከል ለተፈጠሩ ልጆች ሲባል ወይም በጋራ ላፈሩት ቁሳዊ ሀብት ሲባል ጋብቻው የዕድሜ ልክ የፍልሚያ ሜዳ ሆኖ ይቀጥላል፡፡

ጥቂት በነፃነት ላይ የተመሠረተ ፍቅር ግን በእጮኝነትም ሆነ በጋብቻ ጊዜ ተመሳሳይ አንድምታ ሊኖረው ይችላል፡፡ከተለያዩ ሁለት ቤተሰብ የመጣን ሁለት የተለያየን ሠዎች ስለሆንን በሁሉ ነገር ላይ መስማማት አይጠበቅብንም፤በሚያስማማን ነገር ላይ እንስማማለን፤አንዳችን የሌላችንን የተለየ ፍላጎትም እናከብራለን፡፡›› በማለት ተግባብተው ከፍቅር ዘለው ወደ ጋብቻ የዘለቁ
ጥቂቶች ችግር አልባ የሆነ ጣፋጭና ምቹ ህይወት ለመምራት ይታደላሉ፡፡ >>

‹‹ፍልስፍና መዘባረቅና ህይወትን ቀጥታ መኖር ሁለት የተለያዩ ነገሮች ናቸው፡፡ ምን አለበት የእኔን ትዳር ለሦስት ወር ብትሞክረው እሳቱ እንዴት እንደሚያቃጥል ትረዳልኝ ነበር፡፡››

‹‹ያንተን ሳይሆን የራሴኑ እሞክረዋለሁ፤ደራሲዋን ሳገባ፡፡ ግን እስቲ ንገረኝ አሁን የውብዳር ፍታኝ ብትልህ ትፈታታለህ?»

<<እኔንጃ>>

‹‹እንዴት እኔ እንጃ?››
👍1107😢2😁1
#ቤርሙዳ_ዘ_ካሳንቺስ


#ክፍል_አምስት


#በዘሪሁን_ገመቹ _ዋቤ

እንደምንም ራሷን ተቆጣጥራ ያዘዛትን መድሀኒት በስርዓቱ ተጠቅማ በቀጠራት ቀን ከሳምንት በኋላ በሰዓቱ ሄደች።እንደደረሰች  በሞቀ  ፈገግታና  ጠበቅ  ባለ ሠላምታ  ተቀበላትና።

"ቁርስ በልተሻል?›› ሲል ጠየቃት፤ግራገባት፡፡ አሰበች   ቁርስ   አልበላችም
..ጭርሱኑም ትዝ አላላት።ሳትመልስለት  የለበሰውን  ነጭ  ጋዎን  አውልቆ መስቀያው ላይ እያንጠለጠለ

"ጥሩ እኔም አልበላሁም...ወጣ ብለን እንብላ"አላትና ወደ መውጫው መራመድ ሲጀምር ቀድማው ከክፍሉ ወጣች፡፡ቆለፈውና ጎን ለጎን እየተራመዱ መኪናውን ወዳቆመበት ቦታ እየመራ ወሰዳት ፡፡ጋቢናውን ከፈተና ካስገባት  በኋላ  እሱ  ዞሮ ገባና አንቀሳቀሰው… ሆስፒታሉን ለቀው ወጡና አስር ደቂቃ ያህል ከተጓዙ በኋላ የመናፈሻ ድባብ ያለው አሪፍ ሆቴል ይዟት ገባ።ቁርስ እዛው በሉ…ማኪያቶ እየጠጡ ወሬ ጀመሩ።

"ሳምንቱ ጥሩ አለፈ አይደል?"

  "ምንም አይል?"

"እንዴት ምንም አይል... አመመሽ እንዴ ...ደውይልኝ ብዬሽ ነበር?››
"አይ ያን ያህል አላመመኝም..ግን ያው ወጣ ገባ ነበር"
"ያው እንዲህ አይነት ህመም በፍጥነት የሚወገድ አይደለም..  የረጅም  ጊዜ ክትትልና ትዕግስት ይጠይቃል።በተለይ ያንቺ ጥረት ወሳኝነት አለው፡፡

  ምክንያቱም ከበሽታው እንድታገግሚ ለማድረግ የሚያግዙሽ ነገሮች ምን ምን እደሆኑ በዝርዝር ብታውቂያቸውም በሽታው ግን በራሱ ከአንቺ በተቃርኖ ስለሚቆም ተግባራዊ ማድረጉ ፈተና ነው››

‹‹አልገባኝም››

‹‹በቀላሉ ላስረዳሽ… ለምሳሌ ጨጓራ በሽታ ያለበት ሰውን መድሀኒት ትሰጪውና ከዚህና ከዚያ አይነት ምግቦች ተጠበቅ ብለሽ ምክር ብትሰጪው  ትዛዙን ለመተግበር የምግብ አምሮቱን መገደብ ብቻ ነው የሚጠበቅበት፤ ስለዚህ በቀላሉ ይከውነዋል፡፡ እንደአንቺ አይነት ችግር ያለበት  ሰው  ግን  ለምሳሌ  ጠዋት እንደተነሳሸ አልጋሽን አንጥፊ ብትባይ እሺ አነጥፋለሁ ልትይኝ ትችያለሽ፡፡ግን በተጫጫነሽ ቀን እንኳን ተነስቶ አልጋ ማንጠፍ ይቅርና ..አንሶላውንም ከፊትሽ ላይ ማንሳት ላትችይ ትችያለሽ. .ምክንያቱም ነገሮችን እንድትከውኚ የሚያዘው አእምሮሽ ነው…ችግር የተፈጠረው ዋና  ማዘዣ  ጣቢያው  ላይ  በመሆኑ  ነገሮች ሁሉ ቀላል አይሆኑም ፡፡እርግጥ በጣም ጥሩ ነገር አሁን ባለው ሁኔታ አንቺ አስቸጋሪው ደረጃ ላይ አልደረስሽም…እንደምንም ተረባርበን ወደኋላ መመለስና ሁሉን ነገር ማስተካከል አለብን፣አሁን ካለሽበት አንድ ስቴፕ ወደፊት ከሄደ ግን ከባድ ነው የሚሆንብን….ለዚህ ነው ሁሉን ነገር እርግፍ አድርገሽ በከፍተኛ ትእግስት ጤናሽ ላይ ብቻ ማተኮር እንዳለብሽ ከማስጠንቂያ ጋር የምነግርሽ፡፡

"እኔ ደግሞ ትዕግስት ነው የሌለኝ....በቃ ምን ለማግኘት ነው ይሄንን ሁሉ ስቃይ ታግሼ ለመኖር የምጥረው? የሚለው መልስ ያላገኘሁለት ጥያቄ ነው።›

‹‹ግድ የለም፤ መጀመሪያ ካለሽበት የተጨናነቀ ህይወት ራስሽን አላቂና ዘና ባለ መንፈስ ከዛ በኋላ የምትፈልጊውን ሞት ትሞቺያለሽ››

‹‹አይ ዶክተር እየቀለድክብኝ  ነው አይደል?››

‹‹አይ እየቀለድኩ አይደለም..ለመሆኑ ስራ እረፍት ላይ ነሽ አይደል?"

"አዎ  እረፍት ወስጄያለሁ ..››

‹‹...ምን ያህል?"

‹‹አንድ ወር...ግን ከዛም በኋላ የምመለስ አይመስለኝም  ።››

‹‹ሳባ ...ኑሮ አያሳስብሽም አይደል..?.ማለቴ ፋይናንሺያል?"

"ለመጪው መቶ አመት በዚህ ምድር ላይ ብንኖር  ገንዘብ የሚቸግረኝ አይመስለኝም።››

"ጥሩ አሁን ወደሆስፒታል እንመለስና በቀደም ካቆምንበት እንቀጥል፤››  አላትና ተያይዘው ወደሆስፒታል ሄዱ።ለአንድ ሰዓት ያህል ካወሩ በኋላ ተጨማሪ አንድ ኪኒን አዘዘላትና ሳምንት በተመሳሳይ ቀን እንዲገናኙ ቀጠሮ በመስጠት አሰናበታት።ስትመጣ ከነበረችበት የበለጠ ተደብራ ነበር የተመለሠችው።ይሄ ሳምንት እየጠበቁ እሱ ጋር መመላለስ ብዙም ምቾት እየሠጣት አይደለም። መኪናዋን እየነዳች ወደቤቷ እየተጓዘች ሳለ ስልኳ ጠራ ...አሁን የያዘችውን ቁጥር በጣም ጥቂት የራሴ የምትላቸው ሰዎች ናቸው የሚያውቁት።ከነዛ ውስጥ ማን እንደደወለላት ለማወቅ በመጓጓት በአንድ እጇ መሪውን እንደያዘች በሌላ እጇ  ወደኪሷ  ገባችና  ስልኩን  አወጣች  የደዋዩን  ማንነት  ስታይ   ደነገጠች

...መኪናውን ወደዳር አቆመችና አነሳችው ።

"ሄሎ ራጂ"የ12 አመትና የ5ተኛ ክፍል ተማሪ የሆነው ብቸኛና ተወዳጅ ታናሽ ወንድሟ ነው የደወለላት።እሱን እንኳን ደውላ ካናገረችው አንድ ወር ሊሞላት ነው።‹‹ጨርቄን ጥዬ አልሄድኩም እንጂ እኔማ በትክክል አብጄያለሁ››  ስትል በውስጧ አሰበች።ከእዛኛው ጫፍ ወንድሟ እያወራ ነው።

‹‹እህቴ. ምነው ጠፋሽብን...?ብዙ ጊዜ ስንደውል ስልክሽ አይሰራም››ቅሬታውን አሰማ፡፡

‹‹የእኔ ማር ደህና ነኝ..ትንሽ ስራ ስላጨናነቀኝ ነው..ለመሆኑ እናትህ ደህና ነች››

ከራጂ ጋር በአባት እንጂ  በእናት  አይገናኙም።ግን  የራጅ  እናት  ለሳባ  የእንጀራ እናቷ ብቻ ሳትሆን የልጅነት አብሮ አደግ ጓደኛዋ ጭምር ስለሆነች ቀረቤታቸው ዘመናት ያስቆጠረና የተለየ አይነት ነው።

‹‹እማዬማ...ደህና ነች ማለት ይከብዳል?››

ሳባ ደነገጠች"እንዴ ምን ሆነች...?  አመማት እንዴ?››

‹‹እኔ እንጃ እህቴ?.ካንቺ ጋር ተጣልታቹሀል እንዴ?››

‹‹ማንና ማን.. እኔና ስንድ? የት ተገናኝተን...ይሄን ወሬ ከየት አመጣኸው?››

‹‹እህቴ ባትቀየመኝ ኖሮ እንዲህ አትረሳኝም ነበር...አንድ ልጄን አስቀይሜ የአባቷ መንፈስስ እንዴት ይታዘበኛል? እያለች ቀኑን ሙሉ ስታለቅስ ነው የምትውለው.. አይኗ እንዳይጠፋ ፈርቼ ነው የደወልኩልሽ››

ሳባ ጭንቅላቷ ላይ ብው ብሎ የሚነድ እሳት የተነሰነሰባት መሰላት‹‹የእኔ ማር...እናትህ ተሳስታለች...እሷ መቼም  እኔን  ልታስቀይመኝ  አትችልም...  ደግሞም በሆነ ነገር ብቀየምስ በግልፅ እንዲህ አድርገሽኛል እላለሁ እንጂ  እንዴት እቀየማለሁ፤ ከአንተና ከእሷ ውጭ ሌላ ቤተሠብ አለኝ እንዴ?››

‹‹እሱማ የለሽም...ግን?››

‹‹ግን ምን?››

‹‹እኔ እንጃ ባትቀየሚ.ዛሬ እኛ ጋ ትመጪ ነበራ...››

‹‹የት አሰላ?››

‹‹አዎ ››

ብዥ  አለባት  ...መድሀኒት  ስትወስድ  የሚሰማትን  የመደንዘዝ  አይነት ስሜት ይሰማት ጀመረ..፡፡

‹‹ዛሬ ለምን?››

‹‹ነገ  የአባዬ  የሰባት  አመት  መታሰቢያው  አይደለ  እንዴ....?ባትቀየመኝ  በአባቷ መታሰቢያ ቀን ከቤቷ አትቀርም ነበር ብላ እኮ ነው የምታለቅሰው..››

‹‹ራጂ ቆንጆ...አሁን መኪና እየነዳሁ መጥፎ ቦታ ነኝ ያለሁት...ማታ ልደውልልህ››

‹‹እሺ እህቴ እወድሻለሁ፡፡››

‹‹እኔም   እወድሀለሁ    የእኔ    ማር፡፡››ስልኩን    ዘጋችና    ..መኪናዋን    አንቀሳቀሰች ...ወደአስፓልት መሀል ካስገባች በኃላ መጠምዘዣ እስክታገኝ ወደፊት ነዳች፡፡ ከዛ አቅጣጫዋን ለውጣ መንዳት ጀመረች.፡፡

💫ይቀጥላል💫

ቤተሰቦች እባካችሁ #Subscribe እያደረጋቹ።

#Share #like and #subscribe my #YouTube 

👇Sebscribe

YouTube link👇
https://www.youtube.com/@atronose
👍9111🔥1
#ኢትዬጵያዊቷ_ሰላይ
( በአመዞን ደን ውስጥ)


#ክፍል_አምስት


#በዘሪሁን_ገመቹ_ዋቤ


ፔሩ/አማዞን ወንዝ ላይ
ደግላስ እና ኑሀሚ እታች ወርደው ካፌ ቁጭ ብለው ያዘዙት ቁርስ እስኪመጠ ያነሳቸውን ፎቶና ቪዲዬ ትናንት ከተማውን እየዞሩ ሲጎበኙ የተነሱትንም ጭምር በኢሜሉ ላከችለት፡፡ሁለት ሰዓት ሲሆን ቁርሳቸውን በልተው ጨርሰው ወደ ኤርፖርት ለመሄድ ዝግጁ ሆነው ነበር፡፡እርግጥ ኤርፖርቱ ካረፉበት ሆቴል 15 ደቂቃ ያህል ብቻ ነው የሚርቀው፡፡ቢሆንም ቀድመው ሄደው እዛው ለመጠበቅ ተስማሙና ለሆቴሉ አስተናጋጅ ታክሲ እንዲጠራላቸው ነገሩት፡፡በአምስት ደቂቃ ውስጥ የፈለጉት ታክሲ መጣና ጫናቸው፡፡ሁለቱም ከኋላ ወንበር ተጠጋግተው ተቀምጠው በፀጥታ ጉዞቸውን ጀመሩ፡፡ሹፌሩ ታክሲ ከሚነዳ ይልቅ ቱርቦ ወይም ግዙፍ ተሳቢ መኪና ቢነዳ ከአቋሙ ጋር ይሄድ ነበር…እጆቹና አንገቱ ጠቅላላ በንቅሳት የተዝጎረጎረ.. ግዙፍ ግን ባለ አስፈሪ ጡንቻ ባለቤት የሆነ ሰው ነው፡፡የከተማውን ግራና ቀኝ ፎቆች እና የንግድ ተቋሞችን እየተመለከቱ ለ15 ደቂቃ ከተጓዙ በኃላ ሹፌሩ ወደኃላ በመዞር…‹‹ካላስቸገርኳችሁ እዚህ ፊት ለፊታችን ካለው ቅያስ ጋር የምቀበለው እቃ ነበረኝ..ሁለት ደቂቃ ባዘገያችሁ ነው››ሲል በተሰባበረ እንግሊዘኛ ፍቃድ ጠየቃቸው፡፡
ቢያንስ ከ30 ደቂቃ በላይ ትርፍ ሰዓት ስላላቸው እና ከዛ ላይ አንድ 5 ደቂቃ ቢለግሱት የሚጎዳቸው መስሎ ስላልተሰማቸው አልተቃወሙትም፡፡
‹‹..ችግር የለም.. እንችላለን፡፡››ስትል ሁለቱንም ወክላ ፍቃዱን የሰጠችው ኑሀሚ ነች፡፡ እንዳለውም በመጀመሪያው ቅያስ ወደግራ ታጠፈና ጠባብ የድንጋይ ንጣፍ የሆነ መንገድ ውስጥ ገባ፡፡ጭር ያለ መንገድ ነው፡፡ሁለት መቶ ሜትር ያህል ከተጓዘ በኃላ ጥግ አሲይዞ መኪናውን አቋመና ፡፡‹‹መጣሁ ሁለት ደቂቃ›› በማለት ሞተሩን ሳያጠፋ ታክሲዋን ለቀቀና ወጥቶ አንድ የብረት በር ግቢ ገፋ አድርጎ ገባ ፡፡ሁለቱም አይናቸውን እሱ የገባበት ግቢ ላይ ተክለው ከአሁን አሁን ወጣ እያሉ ሲጠብቁ በቅፅበት ከግራና ከቀኝ ያለው በራፍ ተከፈተና ጭንብል ያጠለቁና ሽጉጥ የደቀኑ ሰዎች የመኪናውን በራፍ ከፍተው ገቡና ሁለቱን አንድ ላይ አጣብቀው ከመሀላቸው በመክተት በሽንጣቸው አቅጣጫ ሽጉጣቸውን ደቀኑባቸው፡፡ ኑሀሚም ሆነች ዳግላስ በድንጋጤ ትንፋሽ አጠራቸው፡፡ ልክ ቀድመው እንደገቡት ጭንብል ያጠለቀ ሌላ ሰው ከፊት ለፊት የሹፌሩን ቦታ ያዘና መኪናውን አንቀሳቀሳት፡፡ቀጥታ ወደፊት ለፊቱ ነው እየነዳ ያለው፡፡ከ10 ደቂቃ በኃላ ሙሉ በሙሉ ከከተማ ወጡና ረግረግ የሆነና ግራና ቀኙ በደን በተሸፈነ ከዛም አልፎ በጭቃ የላቆጠ ወጣ ገባ መንገድ ውስጥ ገቡ፡፡

‹‹ምንድነው የምትፈልጉት….?ገንዘብ ነው…?››ኑሀሚ ነች ጠያቂው፡፡
አንደኛው መናገር ጀመረ፡፡ኑሀሚ ግን ምንም እየገባት አይደለም፡፡ቋንቋው እስፓኒሽ ነው፡፡እሷ ደግሞ ከእንግሊዘኛ ውጭ ሌላ የውጭ ቋንቋ አታውቅም፡፡ እርግጥ ራሺኛ ትችላለች..ያ ግን እዚህ አካባቢ እርባን ያለው መስሎ አልተሰማትም፡፡አጠገቧ ወዳለው ዳግላስ ዞረችና አፍጥጣ አየችው‹‹አፍሽን ዝጊ ነው የሚሉት፡፡››ሲል ተረጓመላት፡፡
‹‹ቋንቋውን ትችላለህ እንዴ?››

‹‹የሚሉትን መስማት የቻልኩት ብችል ነዋ››ሲል መለሰላት፡፡

አስር ደቂቃ በኋላ ጫካና ቁጥቆጦ እያቆራረጡ ከተጓዙ በኃላ መኪናዋ ቆመች፡፡ግራና ቀኛቸው ተቀምጠው ሽጉጥ የደቀኑባቸው ሰዎች አንዳንዳቸውን ይዘው ከታክሲዋ ወረዱ፡፡ሹፌሩም የታክሲዋን ሞተር አጥፍቶ ወረደ ፡፡

መኪናዋን ሲሾፍር የነበረው..ከጃኬቱ ኪስ ውስጥ እነሱ የለበሱትን አይነት ጥቁር የፊት ጭንብል አወጣና ተራ በተራ አጠለቀባቸው፡፡፡ከዛ ሌላ ጥቁር ጨርቅ አወጣና በአይናቸው ዙሪያ በማሽከርከር አሰረና ሙሉ በሙሉ እንዳያዩ አደረጋቸው፡፡ከዛ እየጎተቱና እያመናጨቁ በእግር ይዘዋቸው መጓዝ ጀመሩ፡፡ኑሀሚ በጣም ተረበሸች፡፡በቀልቃላነቷም እራሷን በጣም ወቀሰች፡፡‹‹እንዴት ሰው በማያውቀው ሀገር የማያውቀውን ሰው ለመርዳት ይሄን ሁሉ ርቀት ይጓዛል ?ለዛውም ምን እንደሆነ እና ማን መሆኑን ለማያውቅ ሰው?ከእኔ እንደዚህ አይነት ስህተት ፈፅሞ አይጠበቅም፡፡››ስትል አሰበች፡፡
.እርግጥ ኑሀሚ በህይወቷ ከህፃንነቷ ጀምሮ ብዙ ይሄንን መሰል አደጋዎችና አሳልፋለች፡፡ሞትኩ በቃ አበቃልኝ ካለች በኋላ ባልተጠበቀ ቅፅበታዊ ገጠመኝ ከመከራውም ወጥታ ህይወቷንም ያተረፈችበት አጋጣሚ በርካታ ናቸው፡፡ግን ያን ሁሉ ፈተና ያን ሁሉ ተስፋ መቁረጥ አጋጥሟት የነበረው በገዛ ሀገሯ በገዛ ህዝቦቾ ውስጥ ነው፡፡በሀገር ውስጥ በገዛ ምድር ላይ እየተራመዱ ተስፋ መቁረጥ በሰው ሀገር ውስጥ የሰው ምድር ላይ እየተራመዱ ተስፋ ከመቁረጥ ፍፁም የተለየ ነው፡፡በገዛ ሀገር ሆኖ ተስፋ መቁረጥ ማለት ሁል ጊዜ የተደበቀች ተስፋ ትኖራለች፡፡ያቺ ተስፋ ከእናት የምትገኝ ወይ ከአባት የምትቸር ወይም ወንድም የሚለኩሳት..ወይ ደግሞ እህት የምታበራት የአይዞህ ባይነት ተስፋና አለውልህ የሚል ማፅናኛ ነች፡፡ያ ቃል ደግሞ የተገነዘ ተስፋን ከሞት የሚያስነሳ ይሆናል፡፡በሰው ሀገር ተስፋ ሲቆረጥ ግን እነዚህ ሁሉ የሉም፡፡
እየተደናበሩና እየተገፋፉ 15 ደቂቃ ከተጓዙ በኃላ ተረጋጉ፡፡ከአይናቸው ላይ የታሰረው ጥቁር ጨርቅም  ሆነ  ጭንብል  ተነሳላቸው፡፡ከጀርባቸው  ጥቅጥቅ  ጫካ  …ከፊት  ለፊታቸው የተንጣለለ የአማዞን ወንዝ ነው የሚታየው፡፡እነሱ ከቆሙበት በሁለት ሜትር ርቀት መለስተኛ የሞተር ጀልባ መልህቋን ጥላ ቆማለች፡፡አንዱ እጇን ያዛትና እየጎተተ ወሰዳት እና አንደኛው ጀልባ ላይ ጫናት…ልክ እንደእሷ ሁሉ ዳግላስንም አምጥተው ከጎኔ ያስቀምጡታል ብላ ስትጠብቅ..በተቃራኒው ወሰዱና ሌለኛው ጀልባ ላይ ጫኑት፡፡
‹‹ለምንድነው የምትለያዩን..?ወዴት ነው የምትወስዱን ..?እኔ እኮ ምንም አላውቅም፡፡ከእሱ ጋር የተገናኘሁት ትናንትና ነው፡፡ምንም ማውቀው ነገር የለኝም…?››ኑሀሚ ለፈለፈች፡፡ቁብ ሰጥቶ እያዳመጣት ያለ ሰው የለም፡፡እሷ ራሱ ያንን ሁሉ ስትለፈለፍ የነበረው በአማርኛ ነበርና ያ ትዝ ሲላት የምሬት ፈገግታ ፈገግ አለች፡፡ሁለት ሽጉጥ የደቀኑ አጋቾች በአንድ ሜትር ከእሷ ፈንጠር ብለው ሁለት ሌላ መሳሪያ የታጠቁ ደግሞ ከጀርባዋ ተቀመጡ፡፡ጀልባዋ አስደንጋጭ የሞተር ጩሀት ድምፅ አሰማችና ወደባህሩ መሀከል ተፈተለከች፡፡…ወንድሟ ትዝ አላት…፡፡እህቴ ከዛሬ ነገ ትመጣለች እያለ ሲጠብቅ…..መኖር መሞቷን እንኳን ማረጋገጥ ሳይችል በስቃይ ሲኖር አሰበችና ስቅጥጥ አላት ..አይኖቾን አሻግራ ላከችና ዳግላስ የተጫነበትን ጀልባ ለማየት ሞከረች፡፡እነሱ እየተጓዙ ካሉበት አቅጣጫ በተቃራኒው ነው ይዘውት እየሄዱ ያሉት፡፡በቃ መቼም እንደማይገናኙ አሰበች…..እሷ እራሷ አሳዛኝ ሁኔታ ላይ ብትሆንም ለእሱ ከማዘን እራሷን ማቀብ አልቻለችም፡፡

ፔሩና/ኮሎምቢ ድንበር
በአለም ላይ በውሀ ከተከበብት ከተሞች መካከል ግዙፍ የሆነችውንና እስከ 200 ሺ ህዝብ በላይ ከሚኖርባትን የኢኩኢቶስ ከተማ ነጥቀው በአማዞን ወንዝ ላይ እያንሳፈፉ አርቀው ወሰዷትና አማዞን ደን ውስጥ ከተቷት።ከጀልባው ወርዳ መሬት ላይ ስታርፍ ይዛዋት የመጡት አራት ሰዎች በመጡበት ጀልባ ወደኃላ ሲመለሱ …መሬት ላይ ቆመው ሲጠብቋት የነበሩ ከነዛኞቹ በላይ አስፈሪ የሆኑ በቁጥር 9 አካባቢ ሰዎች ነበሩ የተቀበሏት፡፡‹‹በዚህ ሁሉ ትጥቅና አጀብ የሚቀበሉኝ ማነች ብለው ነገሯቸው ይሆን?›› ስትል በውስጧ አልጎመጎች፡፡አራቱ ከኃላዋ አራቱ ደግሞ ከፊት አንዱ ከመሀከላቸው በአቋሙ ቀጠን የሚል በአለባበሱ ስርአት ያለውና ..ለስላሳ ቢጤ የሆነ ሰው ወደእሷ ቀረበና
👍844🤔3👎2🤩1
#ጉዞ_በፀሎት
(አቃቂ እና ቦሌ)


#ክፍል_አምስት


#በዘሪሁን_ገመቹ_ዋቤ


፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧

ከጥዋቱ ሁለት ሰዓት ለመጀመሪያ ጊዜ የቀኝ እጇ የመሀል ጣት ተነቃነቀ…እቤቱ ውስጥ ያለው ሰው ሁሉ በደስታ ፈገገ ..ከአስር ደቂቃ በኋላ አይኖቾ ተከፈቱ፣አራቱም የቤቱ አባላት የተኛችበትን ፍራሽ በሁሉም አቅጣጫ ከበው በፈገግታ ያዩት ጀመር….ግራ ገባት፡፡መልሳ አይኖቾን ጨፈነች…፡፡መንቃቷ እራሱ የእውነት ሳይሆን በህልም አለም ውስጥ የተፈጠረ መንቃት ነው የመሰላት ፡፡ለዛ ነው ዳግመኛ እይኖቾን የጨፈነችው..፡፡መልሳ ስትገልጥ ያየችው ተመሳሳይ ነገር ነው….አራት ወዛቸው የተመጠጠ የለበሱት ልብስ የነታተበ ..በአባቷ ግቢ ውስጥ አትክልቶችን ከሚንከባከቡ ሰራተኞች በላይ ኑሮ የጠበሳቸው ጠና ያሉ ሰውዬ…ቆዳቸው የተሸበሸበ እናት… የ ሀያ አመት ልጅ እግር የምታምር ግን ደግሞ ያልተመቻት ልጃገረዶች..ባለጡንቻ ፈርጣማ እና ባለኮስታራ ፊት ሀያ አምስት ወይም ስድስት የሚሆነው ወጣት ..ጭስ የጠጣና ያረጀ የማዳበሩያ ኮርኒስ ያለው ጠባብ ክፍል…መሬት ላይ የተነጠፈ ፍራሽና ያረጀ በህይወቷ እንኳን ለብሳው አይታው የማታውቀው አይነት ብርድ ልብስ ለብሳ ነበር እራሷን ያገኘችው፡፡ግን እንደዛም ሆኖ የተለየ እና የማታውቀው ቦታ ያለች መስሎ አልተሰማትም….የሆነ ከዘመናት በፊት ታውቀው የነበረ እና ስትናፍቀው የቆየችው ቦታ ተመልሳ እንደመጣች አይነት ስሜት ነው እየተሰማት ያለው

‹‹…የት ነኝ?››

‹‹ልጄ…አሁን ሰላም ነሽ …ትንሽ አደጋ ደርሶብሽ ነው?››

‹‹የምን አደጋ?››

‹‹አሁን ሰላም ነሽ..በውድቅት ለሊት ሞተር ስትነጂ ነበር…ተገልብጠሸ ነው፡፡››

‹‹ሞተር››

‹‹አዎ..ሞተር..ከማን ስትሸሺ ነበር….?እስከአሁን ለፖሊስ አላሳወቅንም…..ይሄውሽ እኔና ቤተሰቦቼ በህይወት ፈተና ጋር ግብግብ ገጥመን በትግል የምንኖር ሰዎች ነን…ከሆነ ወንጀል ጋር የተያያዘ ታሪክ ካለሽ እባክሽ.እኛንም ጣጣ ውስጥ እንዳንገባ ከአሁኑ ንገሪን››ሲል ፊራኦል ተናገረ፡፡

‹‹ምነካህ ልጄ? ልጅቷ ገና አሁን መንቃቷ ነው…ተው እንጂ ነውር ነው›እናትዬው ገሰፁት..አባትዬውም ለባለቤታቸው ድጋፍ በመስጠት‹‹ልጄ አዎ..አሁን ዋናው ያንቺ መትረፍ ነው ፡፡ሌላውን ቀላል ነው…የሰው ልጅ በህይወት ካለ የማያልፈው መከራ የማያሸነፍው የህይወት ትግል የለም..አሁን አንቺ ምንም አታስቢ..እኔነኝ የተባለ ውጌሻ ጠርቼያለሁ፡፡ ወለምታ ወይም ስብራት ነገር ካለሽ ያዩልሻል…ከዛ ካገገምሽ በኋላ ለቤተሰቦችሽ እንደውልላቸውና መጥተው ይወስዱሻል››
በፀሎት ለሊት በውድቅት ለሊት ከቤቷ አምልጣ እንዴት እንደወጣችና ምን እንዳደረገችና አሁን ያለችበት ቤትም የእነማን እንደሆነ ትዝ እያላት ሲመጣ ….የመረጋገትና የደስታ ስሜት ተሰማት

‹‹አመሰግናለሁ…ምንም ወንጀል አልሰራሁም….ፖሊስም እየፈለገኝ አይደለም…አሁን ደክሞኛል ልተኛ..››አለችና መልሳ አይኖቾን ጨፈነች፡፡

‹‹ሰማችሁ አይደል..ምንም ወንጀል አልሰራሁም ብላለች..አሁን ዞር በሉላት …ትንፋሻችሁ እራሱ በሽታ ነው የሚሆናባት››አባትዬው ተቆጡ፡፡

‹‹አባዬ ደግሞ ፣አንተ ሁል ጊዜ ሰው እንዳመንክ ነው.. ሚገርመው ደግሞ ሰዎች ቃላቸውን እያጠፉ አንተን ማሳዘናቸውን አያቆሙም… አንተም ደግሞ ደግመህ ደጋግመህ እነሱን ማመንህን አታቆምም››ፊራኦል ተነጫነጨ፡፡

‹‹ልጄ ገለባ ቢዘሩት አይበቅልም ተጠራጣሪ ሰው አይፀድቅም ይባላል..ያገኘሁትን ሰው ሁሉ በመጠራጠር ህይወቴን ሳሰቃይ ከመኖር እያመንኩ ብከዳ ይሻለኛል…ቢያንስ በማመኔ ምክንያት የሚደርስብኝ ችግር ምክንያቱ እኔ አይደለሁም..››
ፊራኦል በወላጆቹ ውሳኔ ባለመስማማት ‹‹በሉ እሺ እኔ ወደ ስራ ሄጃለሁ፡፡››በማለት ቤተሰቡን ተሰናብቶ ግቢውን ለቆ ሲወጣ በራፍ ላይ ውጌሻዋ ወደውስጥ ስትገባ ተላለፉ፡፡

‹‹ቤቶች አቶ ለሜቻ››ሁሉም ግር ብለው ወጥተው ውጌሻዋን ተቀበሉና ወደውስጥ አስገቧት፡፡

‹‹የትኛው ልጅህ ነች… ለሜቻ?››
‹‹የወንድሜ ልጅ ነች ከድሬደዋ ልትጠይቀኝ መጥታ ነው››

‹‹እና ምን ገጥሟት ነው?››

‹‹ባኮት ከሆነ የሰፈር ልጅ ጋር ሞተር ተፈናጣ ስትሄድ ሞተሩ ተገለበጠባቸውና ትንሽ ተጎዳች..ምን አልባት ስብራት ወይም ወለምታ ይኖራት እንደሆነ ብለን ስለተጠራጠርን ነው ያስቸገርኖት፡፡››

በፀሎት የሚነጋገሩትን ሁሉ አይኖቾን ጨፍና እየሰማች ነው…

‹‹ታዲያ ተኝታለች?››
‹‹አሁን ነቅታ ነበር…እንዴት ነው እንቀስቅሳት?››ወ.ሮ እልፍነሽ ጠየቁ፡፡

‹‹አይ ቆይ ተዋት ..ህመሙ እራሱ ይቀሰቅሳታል፡፡››አሉና ስሯ ፍራሽ ላይ ተቀመጡ…

‹‹ እስቲ እሱን የከሰል ፍም አቅርቡልኝ››ትዕዛዝ ሰጡ፡፡
ማንደጃው ቀረበላቸው…‹‹ እስኪ አንዳችሁ ኑና የለበሰችውን ልብሷን አውልቁላት…..››ለሊሴ ፈጠን ብላ መጣችና ከላይ የለበሳቸውን ጃኬት… ቦዲ ተራ በተራ አወለቀችላት… በጡት ማስያዣ ብቻ አስቀረቻት ፡፡አንገቷ ላይ ያለው የእጅ መዳፍ የሚያህል አብረቅራቂ እንቁ ፈርጥ ያለበት ጌጥ የሁሉንም አይን በቅፅበት ተቆጣጠረ
….ጆሮዋ ላይም ያንጠለጠለችው የጆሮ ጌጥ ከአንገት ሀብሏ ጋር እንዲናበብ ተደርጎ የተሰራ ለልደት በዓሏ ከአባቷ የተበረከተላት ልዩ አይነት ጌጥ ስለሆን በተለይ የሌሊሳን ትኩረት በደንብ ነው የተቆጣጠረው…ሁሉም ግን አርቴ እንጂ ትክክለኛ ነው ብለው አላሰቡም ነበር፡፡
ውጌሻዋ ቦርሳቸው ውስጥ እጃቸውን ሰደዱና በብልቃጥ ከለጋ ቅቤ ጋር ተለውሶ የተዘጋጀ መዳህኒታቸውን አወጡና ፊት ለፊታቸው አስቀምጠው በሌባ ጣታቸው ዛቅ እያደረጉና በመሀል አጣታቸው ላይ አድርገው በመላ መዳፋቸው ላይ ለቀለቁና ስራቸው በቀረበላቸው የከስል ፍም ላይ ጠጋ አድርገው ሙቀት እንዲያገኝ ካደረጉ በኃላ ከአንገቷ ጀምሮ ትከሻዋን እያሹ መፈተሽ ጀመሩ‹‹ ..ምንም አልሆነችም እስኪ ሱሪዋን አውልቁልኝ››ሌላ ትዕዛዝ ሰጡ..በዚህ ጊዜ አቶ ለሜቻ ከተቀመጡበት ተነሱና ወደውጭ ወጡ..ሴቶቹ እንደምንም

ታጋግዘው የለበሰችውን ጅንስ ሱሪ ከላዮ ላይ አወለቁና በፓንት ብቻ ለውጌሻዋ አስረከቧት
…ውጌሻዋ ተመሳሳዩን እሽት ከጭኖቾ ጀመረው ወደታች መውረድ ጀመሩ…ቀኝ እግሯ ቁርጭምጭሚቷ ጋር ደርሰው ጨበጥ..ጨበጥ ሲያደርጓት ግን ከተኛችበት እንደመብረቅ አጓርታ ተነስታ ቁጭ አለች…ሁሉም በድንጋጤ የሚያደርጉት ጠፋቸው..‹‹አዎ እዚህ ጋር ችግር አለ‹‹አሁን በደንብ አድርጋችሁ ግራና ቀኝ ትከሻዋን ያዟት፡፡››የውጌሻዋን ትዕዛዝ ስትሰማ አይኖቾ በፍራቻ ተጉረጠረጠ፡፡በእድሜዋ መርፌ ለመወጋት እሩሱ በስንት እዝጊዎታና ማባበያ ነው...ታዲያ አሁን እንዲህ ላይቨ በስቃይ ስትፈተን እንባዋ ረገፈ
፡፡እናትና ልጅ ግራና ቀኛ ትከሻዋን አጥብቀው እንዳትነቃነቅ ያዙዋት..ሴትዬዋ እየጨመቁና እያሽከረከሩ ያሾት ጀመር…በህይወቷ ተስምቷት የማያውቀው አይነት ህመም…..ተሰማት..የሆነ መጋዝ ጥርስ ያለው አዞ በሁለት መንጋጋዎች መሀከል እግሮቾን አስገብቶ እያኘካት ነው የመሰላት..እንባዋ ብቻ ሳይሆን ንፍጦም በአፍንጫ ላይ እየተዝረከረከ እንደሆነ ይታወቃታል…ለዛ ግን የምትጨነቅበት ሁኔታ ላይ አይደለችም…..ውጌሻዋ ከ10 ደቂቃ በኃላ የተሰበረውን አጥንት ወደቦታው ከመለሱ በኃላ እንዳይነቃነቅ በቀርከሃ በደንብ አድርገው ካሰሩት በኋላ በፋሻ ጠቅልለው አጠናቀቁ…ከዛ እቃቸውን ሰብስባው ተነሱ…ለሊሴ የራሷን ቢጃማ አለበሰችትና መልሰው አስተኞት፡፡

‹‹እልፍነሽ››

‹‹አቤት እማማ››
‹‹ለሜቻ ድሬደዋ ሀብታም ወንድም አለው እንዴ?››

ወ.ሮ እልፍነሽ ጥያቄው መደናገር ውስጥ አስገባቸው‹‹ለምን ጠየቁኝ?››
👍879🥰1
#የጣት_ቁስል


#ክፍል_አምስት


#ድርሰት_በአብርሃም_ቃሉ

#ያሬድ

ሁሉም ተሳካለት፡፡ ከዚያው አካባቢ አበበች የምትባል ልጅ አገባ፡፡ ኑሮውን ለማሻሻል ከግብርና ስራው በተጨማሪ የንግድ ስራ ለመስራት አቀደ፡፡ ለባለቤቱ ማማከር እንዳለበት ወሰነ፡፡

አንድ ቀን ከባለቤቱ ጋር እራት እየበሉ ነው፡፡ "እንዴው ይሔ የግብርና ስራ ከእጅ ወደ አፍ ብቻ ሆነ፡፡ በትርፍ ሰዓቴ እንኳን ንግድ ብሞክር ፤ ሳይሻል አይቀርም" አላት ያሬድ ለባለቤቱ አበበች፡፡ በእጁ የተቀለለውን እንጀራ እየጎረሰ፡፡

"ሃሳብህ ጥሩ ነው፡፡ ግን ምን ዓይነት ንግድ ነው የምነግደው? አለች አበበች፡፡

ጥያቄን በጥያቄ እንዲሉ መልሶ "ቡና ይሻላል ወይስ አልባሳት?'' አላት፡፡

ሁለቱም አማራጮች ጥሩ ናቸው፡፡ ግን ከየት አምጥተህ ነው የምትነግደው ?፡፡

ያሬድ ተጨማሪ የንግድ ስራ ለመስራት እንጅ ከየት አምቶ እና ምን እንደሚነግድ እንኳን በደንብ አላሰበበትም፡፡

አልባሳት በቅርብ ባይገኝም ወደ ድሬደዋ በመሔድ ማግኘት እንደሚቻል ግን ያውቃል፡፡

"ድሬደዋ በውሎ ገባ መድረስ ይቻላል እንዴ"? አለችው፡፡

ያሬድ ድሬደዋ ሔዶባት አያውቅም፡፡ "ሰዎች ሲያወሩ ሰምቻለሁ፡፡ ውሎ ገባ አይደረስም፡፡ መኪና ከተገኘ ሁለት ቀን ቢወስድ ነው"፡፡

ያሬድ ከባለቤቱ ተስማምቶ ፤ ማምጫ ገንዘብ ለሰው አበድሮት የነበረውን ሰበሰበ፡፡ ከቤትም ትንሽ ስንዴ ሸጦ ለመነገጃ የሚሆን ገንዘብ አጠራቀመ፡፡

ታዲያ ወደ ድሬደዋ ሲሔድ ቤቱን ፣ ከብቶቹንና ባለቤቱን ብቻዋን ጥሏት እንዳይሄድ ስጋት አደረበት፡፡

ተመስገን ለቤተሰቦቹ ውሃ ሊቀዳ አህያ ላይ ጀሪካን እየጫነ ነው፡፡

"ደህና አደርህ ተመስገን" አለ፡፡ ቤቱን እና ከብቶቹን እስከሚመለስ እንዲያይለት ሊጠይቀው በጥዋት የመጣው

"እግዚአብሔር ይመስገን ደህና አደርህ ያሬድ" አለ፡፡ ጀርካን መጫኑን ተወት አድርጎ ወደ ያሬድ እየተጠጋ፡፡ የእጅ ሰላምታ ሰጥቶት ወደ ቤት ግባ አለው ተመስገን፡

"አልገባም ይሁን" ብሎ "አንተጋር ነበር የመጣሁት" አለ

"ምነው በሰላም" ?

"አይ! በሰላም ነው፡፡ አንድ ነገር ላስቸግርህ ብየ ነው የመጣሁት"፡፡

"ምን ችግር አለው የምችል ከሆነ"፡፡

"አይ! ቀላል ነው"፡፡ እኔ ወደ ድሬደዋ ለመሄድ ስለፈለግሁ ቤቴን እንድትከታተልልኝ ፈልጌ ነበር፡፡

"ምነው በሰላም ነው፡፡ ወደ ድሬደዋ የምትሄደው ?

"ለራሴ ጉዳይ ነው፡፡ ትንሽ አልባሳት ለመነገድ ስላሰብኩ ለማምጣት ነው የምሔደው ፡፡

"አይ! ደህና ነው፡፡ እከታተልልሃለሁ ግን ለምን አብረን ብቻህን እዛ ድረስ ከምትሄድ ለኔም ታስተዋውቀኝ ነበር አለ ተመስገን፡፡

"ሐሳብህ ጥሩ ነው፡፡ ግን እኔም ገና አዲስ ስለሆንኩ መጀመሪያ ልየውና የሚያዋጣ ከሆነ አብረን እንሔዳልን እስከዛ ገንዘብ አጠራቅም፡፡ ብሎት ተሰነባብተው ተለያያዩ።

እድላዊት

ሲሻለኝ ውለታቸውን በጉልበቴም ቢሆን አግዠ እከፍላቸዋለሁ ብላ አሰበች፡፡ ግን ያሰበችው ቶሎ አልሆነም፡፡

ከህመሟ ሳይሻላት እየባሰባትና እየጠናባት ሄደ፡፡ ሁለት ወር ከ18 ቀን የአልጋ ቁራኛ ሆና አሳለፈች፡፡ ምነው እዛው ጫካ ሞቼ በቀረሁ ኖሮ፡፡ እንደዚህ የአልጋ ቁራኛ ሆኘ ሰው ከማስቸገር ምን አለ ፈጣሪየ መከራና ስቃየን ከምታበዛብኝ ብትገላግለኝ?፡፡ ፈጣሪዋን እየተማፀነች እና እያማረረች ውላ በተራው ጨለማውን ተገን አድርጎ ሌሊቱ ይተካል፡፡

እድላዊት ሌሊትም ሆነ ቀን የምትተኛበት የእንቅልፍ ሰዓት በሃሳብና በጭንቀት ሳይታወቃት ቀን መሽቶ ይነጋል፡፡ በብርድልብስ ውስጥ ተሸፍና የምታለቅሰው እንባ ቢጠራቀም ዘመዶቿንና ቤተሰቦቿን ይቀብርላት ነበር፡፡

አንዳንዴ ሲጨንቃት የተሻላት ይመስላታል፡፡ ለመሄድ አስባ ትነሳለች፡፡ አሁን ልሂድ በቃ ተሸሎኛል፡፡ እናንተንም
አስቸገርኳችሁ፡፡ ተነስታ ለመሄድ ስታስብ አቅም ያንሳታል ፤ እራሷን ያዞራታል፡፡ ተመልሳ መቀመጥ አትችልም፡፡

የእድላዊት ቶሎ አለመዳንና የአልጋ ቁራኛ መሆኗ አሳስቧቸዋል ፤ ወ/ሮ በሰልፏ፡፡ ምነው ፈጣሪዬ ይህችን አንድ ፍሬ ህፃን የአልጋ ቁራኛ ከምታደርግብኝ ለኔ ብሰጠኝ፡፡ እያሉ ፈጣሪያቸውን እየተማፀኑ ውለው ማደራቸው ሳያንሳቸው እድላዊት ደግሞ በሽታዋን ሳታስብ አስቸገርኳችሁ ስትላቸው የባሰ ያስጨንቃቸዋል፡፡

እባክሽን ልጄ ተለመኝኝ ; እባክሽ ስለፈጠረሽ አምላክ ; በደንብ ሲሻልሽ ትሔጃለሽ፡፡ ልጄ እባክሽ ለኔ ምንም አታስቢ፡፡ አንቺ ብቻ ዳኝልኝ፡፡ ለሁሉም ይደረሳል፡፡ ብለው ምንም እንዳታስብና እንዳትጨነቅ ይማፀኗታል ፡፡

እድላዊት በትንሹም ቢሆን እየተሸላት መጣ፡፡ መጀመሪያ ውለታቸውን ከፍየ እሄዳለሁ ብላ ያሰበችውን አረሳችም፡፡

ገና በደንብ ሳይሻላት ለመርዳት ተቻኮለች፡፡ ቡና ሲያፈሉ እኔ አፈላለሁ እያለች ወ/ሮ በሰልፏን ታስቸግራቸውም ጀመር፡፡ ቆይ በደንብ አልተሻለሽም፡፡ በደንብ ሲሻልሽ ታፈያለሽ፡፡ ቢከለክሏትም እሽ አትላቸውም ነበር፡፡

እድላዊት በቤቱ ውስጥ ያለውን ስራ በመስራት መርዳትና ማገዝ ጀመረች፡፡ ትንሽ ሲሻለኝ እሄዳለሁ ያለችውን ሰረዘች፡፡ ውለታቸውን በደንብ ለመክፈል ህሊናዋ አስገደዳት፡፡

የተባረከች ልጅ የእግዚአብሔር ቸርነት ያደረባት፡፡ የትንሽ አዋቂ በማለት ያመሰግኗትም ነበር ፤ ወሮ በሰልፏ፡፡

ከባለቤታቸው አንድ ወንድ ልጅና ሁለት ሴት ልጆችን ወልደዋል፡፡ያለመታደል ሆኖ ግን ሁለቱን ሴት ልጆቻቸውን በአንድ ወቅት በተከሰተው የኩፍኝ ወረርሽኝ በሞት ተነጥቀዋል፡፡

የሴትን ልጅ ጥቅም በደንብ ያወቁት በእድላዊት እንጅ በልጆቻቸውም አልነበረም፡፡ እርጅናቸው ገፋ ባይባልም በባለቤታቸውና በልጆቻቸው ሞት በመከራ ላይ መከራ አሳልፈዋል፡፡ አቅማቸው እየደከመ ፤ ጤንነታቸው ከቀን ቀን እየባሰባቸው ሄደ፡፡ የጤና ማጣታቸው ታዲያ አልጋ እንዲይዙ አስገድዷቸዋል፡፡

እድላዊት ከቤተሰቦቿ የተፈጠረችበትን ቀን ስታስታውስ አምርራ ትረግማለች፡፡ ቤተሰቦቿ እንደ ወ/ሮ በሰልፏ ቅን ፤ የሰውን ሃሳብ የሚረዱ ቢሆኑ ኖሮ ዛሬ ትምህርቷን ጨርሳ እሩቅ የመድረስ ፤ አላማዋና ተስፋዋ በተሳካላት ነበር፡፡

አንዴ ለመከራ የታደለች አድርጎ የፈጠራት እድላዊት፡፡ ከአልጋ ቁራኛ ተነስታ ውለታቸውን በጥቂቱም ቢሆን በጉልበቷ ከፍላ ለመሔድ ተነሳች፡፡ ግን አልተሳካላትም፡፡ ያስታመሟት ወሮ በሰልፏ ተረኛ የአልጋ ቁራኛ ሆኑባት፡፡

ጥላቸው እንዳትሄድ በእጃቸው በልታ ፣ ጠጥታ ያደረጉላት ውለታ ፤ መቼም የማይረሳ ሆነባት፡፡ ብትሔድ እንኳን  የማይቀናትና የማይሳካላት መስሎ ታያት፡፡ ከስራቸው ሆና ለማስታመም ተገደደች፡፡

ወላጅ እናቷን እንደምጠራው እማዬ ምን ላምጣሎት ? ምን ላድርግሎት ? ምን ይሻላል ? እያለች አቅሟ የፈቀደውን ሁሉ እያደረገች አስታመቻቸው፡፡

ታዲያ ስትወጣና ስትገባ አይን አይናቸውን ስትመለከት ህመማቸው ፤ ህመሟ ይሆንባታል፡፡ ሁለት ወር ከ18 ቀን የአልጋ ቁራኛ እያለች

ያደረጉላት ሁሉ በሃሳቧ ይመጣ፡፡

አይኖቿ በእንባ ይሞላሉ፡፡ ስታለቅስ እንዳያዩዋት ወደ ውጭ ወጥታ ልውጣ ልውጣ እያለ በሃይል የሚያስቸግራትን ፤ የእንባ ጎርፍ ፊቷንና አይኖቿ እስከሚቀሉ ድረስ ታዘንበዋለች፡፡

ወ/ሮ በሰልፏ የራሳቸው በሽታና ስቃይ ሳያንሳቸው በእድላዊት ማሰብና መጨነቅ አንጀታቸው አልችል አለ፡፡
👍747😁2🔥1
#የድንግሊቷ_አፍቃሪዎች


#ክፍል_አምስት


#ድርሰት_በዘሪሁን_ገመቹ
================

አለማየሁና አስካለ ግንኙነት ከጀመሩ ከሰባት  ወር በኃላ
ግንኙነታቸውን ድንገት የሚያከስም  ችግር ተከሰተ፡፡በሁለቱም አእምሮ ያልታሰበበት ቅድመጥንቃቄ ያልተደረገበት አስደንጋጭ ችግር ነው፡፡
ደግሞ ወቅቱ የማትሪክ  ውጤት ከዛሬ ነገ ይለቀቃል ተብሎ እየተናፈሰ ስለሆነ አራቱም  ጓደኛሞች በጉጉት  በምጠበቅበት ወቅት ነበር፡፡ አስካለ ለአላዛር ደወለችለትና በአስቸኳይ እንዲገናኙ እንደምትፈልግ ነገረችው፡፡ከሰፈሯ ብዙም የማይርቅ ካፌ ተቀምጣ ትጠብቀው ጀመር፡፡ብዙም ሳያስጠብቃት እያለከለከ ተገኘ፡፡ እውነተኛ ስሜቱን የሚገልፅ መሸበር ፊቱ ላይ እየታየበት‹‹የእኔ ቆንጆ እንደደወልሽልኝ እየሮጥኩ ነው የመጣሁት.. በአስቸኳይ ፈልግሀለው ስትይኝ ደንግጬ ነበር፡፡››አላት፡፡፡

አስካለ ለእሱ ስሜት እና መሸበር ብዙም ሳትጨነቅ‹‹አዎ …ችግር ተፈጥሯል››አለችው ኩስትርትር እንዳለች፡፡

‹‹የምን ችግር …?ጋሼ ግንኙነታችንን አወቀ እንዴ?››ከፊቷ መኮሳተር እና መገርጣት ከበድ ያለ ነገር እንደተፈጠረ የሚያሳብቅ ነው፡፡ለዛ ነው እንደዛአይነት ጥያቄ የጠየቃት፡፡

‹‹አይ አስከአሁን አላወቀም…››ቅዝዝ እንዳለች መለሰችለት፡፡

‹‹እስከአሁን አላወቀም ስትይ..?ምን ለማለት ነው?››

‹‹ሰሞኑን ሲያዞረኝና ሲያቅለሸልሸኝ ነበር ስልህ ሰምተሀል  አይደል?››

‹‹አዎ !!ምነው ባሰብሽ እንዴ?››

‹‹አይ ..ጤና ጣቢያ ሄጄ ነበር…››

‹‹እና ምን አሉሽ..?መድሀኒት አዘዙልሽ?››

‹‹አይ..አርግዤለሁ››

‹‹ምን ..?አርግዤለሁ››

‹‹አዎ አርግዤለሁ››

‹‹‹ወይኔ ጉዳችን..ከእኔ ነው አይደል?››ሲል እራሱን ይዞ በድንጋጤ አይኖቹን እንዳጉረጠረጠ ጠየቃት፡፡‹‹አዎ ካንተ ነው ያረገዝኩት…››ብትለው ምን እንደሚያደርግ አያውቅም፡፡ይሄ በህይወቱ የጋጠመው እውነተኛው ሰበር ዜና ነው፡፡

እሷ ግን እንደዛ አላለችውም፡፡‹‹እሱ ምን ያደርግልሀል…? የጠራሁህ ልጁ ያንተነው ወይም አይደለም ልልህ አይደለም ››

‹‹እና ለምንድነው?››

‹‹ከዛሬ ጀምሮ  ግንኙነታችን መቀጠል እንደማንችል እንድታውቅ ነው፡፡››ያላሰበውን ሁለተኛ መርዶ ነገረችው፡፡

‹‹ማለት …ምን አጠፋው?አቅጄና ፈልጌ አይደለም እኮ እንድታርዢ ያደረኩሽ››

‹‹እኔም እንደዛ አልልኩም…አንተ ምንም አላጠፋህም..ግን አሁን እንደምታየው ብቻዬን አይደለሁም …በማህፀኔ ልጅ ይዣለሁ…ለራሴ ሳይሆን ለልጄም ደህንነት መጨነቅ አለብኝ፡፡

እስከዛሬ ካንተ ጋር  የቆየሁት ስለማፈቅርህ ነው…ምንም ነገር ቢፈጠር እወጣዋለሁ ብዬ አስቤ ነው…አሁን ግን ነገሮች ተቀይረዋል፡፡በልጄ ላይ እንደዛ ማድረግ አልችልም፡››

አለማየሁ ይሄ ቀን ለዛውም እንደዚህ በቅርብ ይመጣል ብሎ አስቦ አያውቅም ነበር፡፡ይህቺን ሴት በጣም አፍቅሯት ነበር፡፡ከሰሎሜ ቀጥሎ ልቡ የደነገጠባት ሁለተኛዋ ሴት ነች፡፡

ወንድነትን ያጎናፀፈችው  ብቸኛዋ ሴት ነች፡፡በህይወቱ አይቶት የማያውቀውን ፍቅር አስኮምኩመዋለች፡፡ብዙ የደስታ ቀናትን እንዲያሳልፍ አድርገዋለች፡፡ በአለም ተወዳጁና ተፈቃሪው ሰው እንደሆነ እንዲሰማው አድርገዋለች..ይህቺን ልጅ እንዲህ በቀላሉ ‹‹በቃ እሺ እንዳልሺው ግንኙነታችንን እናቁም›› ሊላት አልፈለገም፡፡አዎ እሷ የተናገረቻቸው እያንዶንዷቹ ቃላት ከበሳል ሴት የተሰነዘሩና የፀነሰችውን ልጅ ደህንነት ብቻ ሳይሆን የእሱንም የወደፊት ህይወት አደጋ ላይ ላለመጣል አስባበት ያደረገችው ነው፡፡ለዛም እግሯ ስር ተንበርክኮ ሊያመሰግናት ይገባ ነበር፡፡ግን እንደዛ ማድረግ አልቻለም፡፡እንደውም በተቃራኒው ‹‹እባክሽ…ተረጋግተሸ አስቢበት…እኛ መለያየት የለብንም…ከፈለግሽም ተያይዘን መጥፋት እንችላለን፡፡››ሲል በአይኖቹ ጭምር እየተለማመጠ ተማፀናት፡፡
እሷ ግን የተናገረችውን ሁሉ ለቀናት አስባበት..አውርዳና አውጥታ  የወሰነችው ስለነበር ከአቋሟ ሽብርክ ልትል አልቻለችም‹‹እባክህ የምታፈቅረኝ ከሆነ ያልኩህን አድርግ….ሁለተኛ ቤት እንዳትማጣ… እንዳትደውልልኝ..መንገድ ላይ እንኳን ብታየኝ ልታናግረኝ እንዳትሞክር፡፡››ብላው እንባዋን እያንጠባጠበች…ለጠጡት ማኪያቶ ክፍያ የሚሆን ድፍን መቶ ብር ጠረጴዛ ላይ አስቀምጣ በተቀመጠበት ጥላው ሄደች፡፡

አለማየሁም ጓደኞቹ ግራ እስኪገባቸው ድረስ ለአንድ ወር ነበር ያዘነው፡፡ለሌላ የማይነግሩት የብቻ ሀዘን ደግሞ ውስጥን እንዴት እንደሚበላ የደረሰበት ነው የሚያውቀው፡፡በጣም ነበር የተጎዳው፡፡የሀዘኑ ምንጭ ከእሷ ጋር ያለው ግንኙነት ስለተቋረተ ብቻ አይደለም..እሱንማ ትክክለኛ ቀኑን አይወቅ እንጂ አንድ ቀን እንደሚሆን ከበፊቱ ያውቅ ነበር፡፡በጣም የጎዳው የተፈጠረው ሁኔታ ነው፡፡በመሀከላቸው ልጅ መፈጠሩ….ልጁ በተሳሳተ አባት እጅ ማደጉ….
በጣም የሚገርመው ደግሞ ከገባበት ደባሪ ሀዘን ሳይወጣ በተጨማሪ ሌላ ህይወት መንሸራተት ገጠመው ፡፡ የማትሪክ ውጤት ተነግሮ ከሁሴን በስተቀር እሱን ጨምሮ ሁሉም ጓደኞቹ ዝቅተኛ ውጤት ማምጣታቸው ታወቀ፡፡እርግጥ ከአራቱ ጓደኛሞች ዩኒቨርሲቲ መግቢያ ውጤት  ሁሴን ብቻ ማምጣቱ  ከበፊቱም የሚጠበቅና ሚገመት ነበር፡፡ቢሆንም የቁርጡ ቀን መጥቶ ሁሉም በግልፅ ሲታወቅ ቅሬታ መፍጠሩ አይቀርም፤ቢሆንም ለዚህኛው ሀዘን አብረውት የሚያዝኑ ጓደኞች አሉት፡፡የእሱ  መከፋትን እነሱም ሚከፉት ስለሆነ እርስ በርስ ለመፅናናት ቀላል ነው፡፡እና እንደመጀመሪያው ችግር አልከበደውም፡፡
ሁሴን ጎንደር ዩኒቨርሲቲ ደርሶት ደግሰውና መርቀው ከላኩት በኋላ እነሱ ምን ማድረግ እንዳለባቸው መማከር ጀመሩ..እርግጥ ከበፊቱም ጀምሮ  አላዛር የራሱ ሱቅ ያለውና በንግድ የሚተዳደር ስለሆነ ከእነሱ በተለይ የሚፅናናበት እና ሚመካበት ነገር ስላለው ነገሮች ብዙም አላስጨነቁትም….አንድ ቤት እንደእህትና ወንድም የሚኖሩት አለማየውና ሰሎሜ ግን ምንም አማራጭ የላቸውም..በተለይ አለማየሁ ከገጠመው የፍቅር ስብራት ጋር አንድ ላይ ተጨማምሮ ተራራ የተሸከመ አይነት ስሜት ነበር እየተሰማው ያለው፡፡ ቢሆንም እንደምንም በጓደኞቹ ጎትጓችነት እንደምንም ከቁዘማ ወጥቶ ለገጠሙት ችግሮች መፍትሄ መፈለግ እንዳለበት በማመን መንቀሳቀስ ጀመረ….፡፡

በድንገት ወደህይወቱ ገብታ የፍቅር  አልኮል ስትግተው የሰነበተችው የጓደኛው የአላዛር የእንጀራ እናት ‹‹አርግዤለሁ እና ከአሁን ወዲህ አልፈልግህም ››ማለቷ ከፈጠረበት  ድባቴ መች ሙሉ ለሙሉ ማገገም እንደሚችል አያውቅም ፡፡ፈጽሞ ከአእምሮው ሊፍቀው የሚችል ሁኔታ አልሆነለትም፡፡በ19 አመቱ የልጅ አባት ከመሆኑም በላይ ከባለትዳር ሴት  መወስለቱ  በአሳዳጊው እቴቴ ዘንድ እንዲሁም በሚያፈቅራት በልጇ  ሰሎሜ ዘንድ  ምን አይነት ስሜት እንዲሚፈጥር እያሰበ እየተሳቀቀ ነው፡፡ደግነቱ ልጅቷ ለራሷ ደህንነት ስትል ሚስጥሩን ላለመናገር ወስናለች…በዛም የተወሰነ እፎይታ ተስምቷታል ፡፡ከአስካለ ጋር የነበረው አጭር ግን ደግሞ ጣፋጭ ፍቅር ግንኙነት በአጭሩ እና ባልሆነ መንገድ መቀጨቱ አሳዛኝ ቢሆንም አሁንም ዋናው የህይወት ህልሙ ሰሎሜ ስላለች ለእሷ በቂ ሰው ሆኖ መገኘት እንዳለበት አሰበ….ለዚህም ይረዳው ዘንድ እንደምንም ብሎ ትምህርቱን በመጠኑም ቢሆን ወደፊት መግፋት እንዳለበት ስለወሰነ...ከአላዛርና ከራሷ ከሰሎሜ ጋር በመመካከር ሶስቱም የሞያ ትምህርት ለመማር ተግባረእድ ኮሌጅ ተመዘገቡ…በዚህም የተወሰነ የመንፈስ  መነቃቃት አሳየ ….ትምህርቱ ከዛሬ ነገ ይጀመራል በሚል  ተስፋ መጠባበቅ ጀመሩ፡፡ ግን ደግሞ አንዳንዴ ሕይወት ከፊት ለፊታችን እንቅፋት መደርደር ከጀመረች
👍778👏2🔥1
#የእግዜር_የአደራ_ልጅ


#ክፍል_አምስት


#በዘሪሁን_ገመቹ


‹ከሃያ ደቂቃ በኋላ ቢሮዬ እንገናኝ።››

በእሺታ ራሷን ነቀነቀች፣ ከዚያም አልፋው ጥላው ሄደች፡፡

ከግማሽ ሰአት በኋላ ራሄል ቢሮው መጥታ  ከጠረጴዛው ማዶ ተቀመጠች፣ በአንድ እጇ እስክሪብቶ፣ በሌላ እጇ ማስታወሻ ደብተር ይዛለች። ሁኔታዋ አስገረመው ፡፡

ዶ/ር ዔሊያስ መናገር ጀመረ ‹‹ፀጋ በቴክኒካል ተርሙ ሄሚፕሌጂያ ተብሎ የሚጠራ  በሽታ ተጠቂ ነች፡፡በሌላ አነጋገር ሴሬብራል ፓልሲ ታማሚ ነች ማለት ነው፡፡ በሰውነቷ አንድ ጎን በግራ እጇ እና በግራ እግሯ ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖ አሳድሮባታል..አጥንቶቾ በጣም ደካማ ስለሆኑ እንደልብ ለመንቀሳቀስ ትቸገራለች…በተወሰነ መልኩ የመስማትና ቃላቶችን አቀላጥፎ የማውራት ችግርም አለባት።የእሷን  ጤና ሁኔታ ለማሻሻል በሚደረገው ሂደት ውስጥ የሚሳተፉትን  - ፊዚዬ ቴራፒስት  ጨምሮ፣ ብዙ ባለሞያዎች አሉ.. እና እያንዳንዱን መቼ መቼ  ማየት እንዳለባት አስረዳት፡፡

‹‹በተጨማሪም የጆሮ ኢንፌክሽንን እየተዋጋች ስለነበረ አንቲባዮቲክ ትወስዳለች።››ዔሊ የራሔልን እይታ በመሸሽ እስክሪብቶውን አንሥቶ መሞነጫጨር ጀመረ።

ራሄል ትዕግስት በማጣት‹‹ዶክተር ሌላ ልትነግረኝ የሚገባ ነገር እንዳለ ይሰማኛል››አለችው.

‹‹ትሁት  ከጊዜ ወደ ጊዜ በንዴት በሽታ እየተሰቃየች ነው ። ስለዚህ ስሜቷን በጥንቃቄ መከታተል እና የሚያበሳጮትን ነገሮች ማስወገድ ያስፈልግሻል ማለት ነው ።ያው እንድትናደድ ከፈቀድሽላት የሚጥል በሽታ ስላለባት ነገሮች ይባባሳሉ… እንደ አለመታደል ሆኖ ይሄንን ጉዳይ በመድኃኒቷን ማስተካከል አልቻልንም።››

‹‹ትሁት ማለት?››ግራ በመጋባት ጠየቀችው

‹‹ይቅርታ..ፀጋ ወደእናንተ ቤት ከመምጣቷ በፊት ወላጅ እናቷ ትሁት ብላ ነበር ስም ያወጣችላት….ከዛ ነው አባትሽ ፀጋ ያለት፡፡እና እኔ ትሁት የሚለውን ስም ለረጅም ጊዜ ስለተጠቀምኩበት በቀላሉ ከአእምሮዬ ላወጣው አልቻልኩም…..››

‹‹አይ ችግር ለውም..ትሁትም ደስ የሚል ስም ነው››

‹‹አዎ…እና እንዳልኩሽ ፀጋ ማለት ከፍተኛ ጥንቃቄ የሚያስፈልጋት ልጅ ነች፣፣በተለይ መናደድ የለባትም….ምክንያቱም ከንዴቷ በኋላ የሚከሰተው የሚጥል በሽታ ሌሎች ብዙ የጤና ችግሯቾን ነው የሚያናጋባት››

በራሔል ፊት ላይ የፍርሃት ብልጭታ ሲያይ ተገረመ።

‹‹የሚጥል በሽታ ሊነሳባት መሆኑን  እንዴት አውቃለሁ እና ምን ያህል መጥፎ ነው?››

‹‹ትለይወለሽ…እጆቿ  ይንቀጥቀጣሉ… የዐይን ሽፋኖቿን ይርገበገባሉ እነዚህን እና የመሳሰሉት ምልክቶችን ታሳያለች፡፡የዛን ጊዜ አጓጉል ወድቃ እራሷን እንዳትጎዳ ጥንቃቄ መውሰድ ይገባሻል፡፡ ማንኛውም አሳሳቢ የጤና ችግር ሲያጋጥማት በአፋጣኝ ወደሆስፒታል ልትወስጂያት የግድ ነው፡፡ በመደበኝነት በሳምንት ሶስት ቀን ሆስፒታል የህክምና ክትትል አለት፡፡በመሀል አስፈላጊ ሲሆን ለእኔ በማንኛውም ሰዓት ልትደውይልኝ ትችያለሽ ፣ ወዲያውኑ ልመጣ እችላለሁ።..›› ዔሊያስ መጀመሪያ ያሰበው ለፀጋ  ነው።‹ራሔል በዚህች ልጅ ላይ ያለውን ችግር  በሙሉ ማወቅ አለባት› ሲል በውስጡ አሰበ፡፡

‹‹ፀጋን  ከተወለደች ቀን ጀምሮ እየተንከባከባት ነበር…እናትዬው ተስፋ ቆርጣበት በሆስፒታል አልጋ ላይ ማሽን እንደተሰካካባት ጥላት ስትሰወርም አንደኛ እናትዬውን ከልጅነት ጀምሮ የሚያውቃት ጓደኛው ስለሆነች ሲሆን ሁለተኛም ከራሱ ህይወት ጋር አያይዞ ሲንከባከባትና እንደወላጅ ስለሚጨነቅላት ነው፡፡በመጨረሻም ከስድስት ወር የሆስፒታል ቆይታዋ በኃላ የራሄልን ወላጆችን በግሉ ፈልጎ በማግኘት  በጉዲፈቻ እንዲወስዷት በማድረግ ሂደት ላይ የአንበሳውን ድርሻ የእሱ ነው፡፡ከዛም በኃላ በቃ በኃላፊነት የሚያሳድጓት እና የሚንከባከቧት ወላጆች አግኝታለች ብሎ አልተዋትም፤ በቆሚነት የእሷ ሀኪም በመሆን እነ  አቶ ቸርነት ቤት ድረስ እየተመላለሰ ሁኔታዋን ይከታተላል፤ ታማለች ብለው ሲደውሉለት ያለምንም ማቅማማት ሞተሩን ተረክ አድርጎ በሮ ይሄድና ያያታል…እናም ይህቺ ልጅ ለእሱ እንደአንድ ታካሚው ብቻ አይደለችም…የህይወቱ አካል ነች….ስቃዮ ያመዋል…ለቅሶዋ ይሰማዋል….ፈገግታዋ ያስቀዋል….ለዛ ነው ራሄልን በትክክል እናቷ በምትንከባከባት መጠን ትንከባከባታለች ብሎ ሊያምን ያልቻለው፡፡

‹‹ራሄል ምን መሰለሽ ፀጋን እንዲህ ስታያት በአካላዊ እይታ ጥሩ ሁኔታ ላይ ያለች ሊመስልሽ ይችላል, ግን ውስብስብ በሆነ የህክምና ሂደት ውስጥ እያለፈች ነው፡፡ ሰውነቷ እየሰጠ ያለው መልስ  በጣም ደካማ ነው. ለሚቀጥሉት ጥቂት ዓመታት በጤና እሷን ማቆየት ከቻልን ትልቅ ድል ነው…በህክምናው ሂደት ከባድ ችግር እያጋጠመን ነው ››

ራሔል በፍጥነት ማስታወሻ እየወሰደች ሲሆን  በእጇ ላይ ትንሽ መንቀጥቀጥ አየ፡፡‹‹ስለ ምን ዓይነት የሕክምና ችግሮች ነው የምታወራው?››

‹‹በአእምሯዋ ውስጥ ፈሳሽ መከማቸት ጀምሮል እና  ተጨማሪ ኢንፌክሽኖች እና ሌሎች ችግሮችም እየተከሰቱባት ነው፡፡››

እሺ፣ ምናልባት ትንሽ አክብዶባት ሊሆን ይችላል ግን ማወቅ አለባት። የበለጠ መረጃ ባላት ቁጥር እሷ ማድረግ የምትችለው የተሻሉ ውሳኔዎች ትወስናለች፣ ።

‹‹ወላጆቼ ግን ፀጋ ያለባትን ይሄን ሁሉ የጤና ችግር ያውቃሉ?››

‹‹አዎ..እንደውም ለአንቺ በጥቅሉ ነው የነገርኩሽ እንሱ ግን እሷን ለማሳደግ ከመወሰናቸው በፊት እያንዳንዱን  በዝርዝር አስረድቻቸዋለው…..ግን ለምን ጠየቅሺኝ?››

‹‹እኔ እንጃ…..በዚህ ሁሉ የጤና እክል ውስጥ ሆኖ ምን አልባትም የመሞቻ ቀኗን እየተጠባበቀች ያለች እና ክፉና ደጉን የማታውቅ ልጅ እንዴት ለማሳደግ እንደፈቀዱ ግራ ስለገባኝ ነው፡፡››

‹‹ትክክል ነሽ….እኔም ወላጆችሽን በጣም የማከብራቸውና ከልቤ ማደንቃቸው በዚህ ውሳኔያቸው ነው…እነሱ ያደረጉትን ማንም ሌላ ሰው ያደርገዋል ብዬ አላስብም..እነሱ ለእኔ የህይወት ዘመን ጀግናዎቼ ናቸው፡፡››አለና ካርዱን ከጠረጴዛው ላይ አንስቶ  ሰጣት። ‹‹ይህ የሆስፒታሉ የድንገተኛ አደጋ ቁጥር፣የቤቴ ቁጥር እና የሞባይል  ቁጥሬ ነው። በፈለግሺኝ ጊዜ  ደዉይልኝ››ራሄል መረጃውን እንደያዘች ረጅም እና ዘገምተኛ ትንፋሽ ወደ ውስጣ ሳበች ከዛ ወደ ውጭ ተነፈሰች፡፡  ወረቀቱን  እና ካርዱን በቦርሳዋ ውስጥ አስገባች።

‹‹ከመሄዴ በፊት ግን አንድ የመጨረሻ ጥያቄ ልጠይቅህ?››

‹‹የፈለግሽውን ጠይቂኝ››አላት በጉጉት፡፡

‹‹ፀጋን ቤተሰቦቼ  እንዲያሳድጓት በግል የጠየቅካቸውና ያሳመንካቸው አንተ ነህ….ለሌሎችም ታካሚዎችህ እንደዛ ታደርጋለህ?››ስትል ያለሳበውን ጥያቄ ጠየቀችው፡፡

‹‹እውነቱን ለመናገር የፀጋ እናት የልጅነት ጎደኛዬ ነች…አንድ ሰፈር ነው ያደግነው…ህይወት ባልሆነ መንገድ መርታ ያልሆነ ማጥ ውስጥ ጨመረቻት እንጂ  እንዲህ እንደቀልድ ልጇን ጥላ የምትሰወር ልጅ አልነበረችም….እና ፀጋን ዝም ብዬ ችላ ብዬ ማደጎ ቤት ስትገባ ማየት አልቻልኩም…የምተማመንባቸው  አሳዳጊዎች መፈለግ  ጀምርኩ..መጀመሪያ የራሴ ወላጆች ነበር የመጡልኝ..ግን የጽጌረዳ ሰፈር እዛው ስለነበረ ትንሽ ልክ መስሎ አልተሰማኝም….ከዛ ምክንያት ነው ወላጆችሽን ያገኘሁት…እናም ደግሞ ሁሉንም ነገር በግልፅ ነግሬያቸዋለው….ምንም የማያውቁት ነገር የለም፡፡››

‹‹አባቷስ?››

‹‹ምን ያህል እውነት እንደሆነ አላውቅ…አባቷ እንደሞተ ነው የነገረችኝ… ሌላ ጥያቄ ይኖርሻል?››

‹‹ አይ የለኝም..አመሰግናለው…. ››አለች… ቆመች… እጁን ለመጨበጥ ከጠረጴዛው አሻግራ እጇን ዘረጋች፡፡
75👍3🥰1
#ቋጠሮ_ሲፈታ


#ክፍል_አምስት


#ድርሰት_በዘሪሁን_ገመቹ

///

አቶ ፍሰሀ በቀይ ቆዳ በተለበጠ መቀመጫው ላይ ተቀመጦ ስልክ እያወራ ነው። ከድሮም ጀምሮ ይህን ወንበር ይወደዋል፡፡

"ተረጋጋ ክቡር ዳኛ"

ጁኒየር በበሩ ደጃፍ ላይ ቆሞ  ተመለከተውና እና እጁን አውለበለበለት።
እያወራ የነበረውን የገመድ አልባውን ስልክ በእጁ ሸፍኖ ለልጁ በሹክሹክታ፣ ‹‹ዳኛውን እያወራሁት ነው›› አለው..ከዛ ወደስልኩ ትኩረቱን ሰብስቦ"አሁን ወደ ድምዳሜ እየዘለልክ ነው እናም እንዲሁ በከንቱ ነው እየተበሳጨህ ያለኸው " አለው

"..ፍሰሀ ነገሩን አቃለህ ልታየው አይገባም….እሷ እናቷ ተገድላበታለች።አሁን የህግ ድግሪ እና የከፍተኛ አቃቤ ህግ ስልጣን በእጇ አስገብታለች..በዚህም ምክንያት የመስቀል ጦርነት ላይ ነች። እነዚህ ወጣት ሴቶች አካሄዳቸው እንዴት እንደሆነ መገመት ከባድ ነው…. ታውቃለህ?። ››

ለአፍታ አዳመጠ። “ክብር ዳኛ ተረጋጋ፣ ምንም ሚከሰት አዲስ ነገር የለም፣አንተ ብቻ ዝም ብለህ አፍህን ዝጋ፣ ይሄ ሁሉ ነገር በቅርብ ያልፋል። የሰሎሜን ልጅ ለእኔ ተውልኝ፡፡››አለው ልጁ ጁኒየር ላይ ዓይኑን ተክሎ ንግግሩን ቀጠለ።"ከጥቂት ሳምንታት በኋላ ጅራቷን በውብ እግሮቿ መካከል ሸጉጣ ወደ መጣችበት ከተማ ትመለሳለች ።ምንም አታስብ የእኔም ልጅ ምርጫውን በከፍተኛ ድምፅ አሸንፎ ፓርላማ ይገባል…፣ አንተም ጊዜህን ጠብቀህ በክብር ጡረታ ትወጣለህ፣ እና ያ እስኪሆን አንድ አመት አለን።››አለናን ተሰናብቶት ተንቀሳቃሽ ስልኩን በጠረጴዛ ላይ አስቀመጠው።

"በኢየሱስ ስም …ይሄ ዳኛ ተንበቅብቆ ሊያንበቀብቀኝ እየሞከረ ነው….እባክህ ቢራ ስጠኝ
›› አለና…መቀመጫውን ለቆ ወደ በረንዳ ወጣ…..ልጁ ጁኒዬርም ለእሱና ለአባቱ አንድ አንድ ቢራ ከፍሪጅ ውስጥ አወጣና አባቱን ተከትሎ ወደበረንዳው ወጣ…..አንዱን ቢራ ለአባቱ አቀብሎት አንደኛውን ለራሱ ያዘና ከፊት ለፊቱ የበረንዳውን ግድግዳ ተደግፎ ቆመ፡፡

ወዲያው የእንስሳት እርባታ ድርጅት ውስጥ ለ30 አመት የሰራው ሱልጣን ከፊት ለፊት የውጪን በራፍ አልፎ ተከሰተ … በጭንቀት ተወጣጥሯል፣ የሰሌን ኮፍያ በጭንቅላቱ ላይ አድርጎ አንገቱን ደፍቶ ከፊት ለፊታቸው በአራት ሜትር ርቀት ላይ ቆመ፡፡

ሱልጣን ከከተማው ጥግ ከምትገኝ አንድ የገጠር ከተማ ተወልዶ ያደገ ሲሆን እስከ ስድስተኛ ክፍል ተምሮ ያቆረጠና በአባሮ ኢንተርፕራይ ስር የሚተዳደረውን የእንስሳት እርባት ድርጅት ውስጥ ተቀጥሮ ከሠላሳ አመታት በላይ ያገለገለ አገልጋይ ነው ፣ ሚስት ያገባው እዛ ድርጅት ውስጥ ስራ ከጀመረ በኋላ ነው….አምስት ልጅ ወልዶ ያሳደገውም አዛው ድርጅት ተቀጥሮ ከብቶችናና ፈረሶችን በመንከባከብ በሚያገኘው ደሞዝ ነው….ከአሁን ወዲህ ባለው ቀሪ ዘመኑም ከዛ ውጭ መስራት የሚችለው ሌላ ስራ ይኖራል ብሎ አያምንም…ለዛም ነው ለሰራው ስህተት በመንቀጥቀት ይቅርታ ለመጠየቅ ጌታው ፊቱ የቆመው፡፡

አቶ ፍሰሀ እሱ ምንም ከመናገሩ በፊት "ምን እንደምትል አውቃለሁ። ምንም የማዳምጥህ ነገር የለም… በአጭሩ ከስራ ትባረሀል››አለው
ጁኒየር በቆመበት ሆኖ አባቱን በድንጋጤ ተመለከተ..እንደዛ አይነት ውሳኔ ሰማለው ብሎ አልጠበቀም…..‹‹አይ አባዬ ትንሽ ሊያስደነግጠው ፈልጎ ነው እንጂ የእውነትማ አያባርረውም››ሲል በውስጡ አሰበ፡፡

"ጋሽ ፍሰሀ እንዴት እንዲህ ታደርጋለህ ?። እዚህ ለሠላሳ ዓመት በላይ ለአንተና ለቤተሰቦችህ አገልግያለው።"አዛውንቱ ሱልጣን መለማመጡን ቀጠለ፡፡

"ጥሩ ለዛ ሚመጥን በቂ የስራ መፈለጊያና የአገልግሎት ክፍያ እንዲከፈልህ አደርጋለው "

"ግን ... አንድ የመጨረሻ እድል ብትሰጠኝ ምን አለበት? "

" መቶ ሺ ብር ልሸጠው የማስበውን ልዩ ፈረሴን እኮ ነው በእንዝላልነት እንዲሰበር ያደረከው፣በቃ ከአሁን ወዲያ ቢድን እንኳን ምን አልባት የጋሪ ጎታች ፈረስ ይሆን እንደሆን እንጂ ለውድድር የሚያገለግል የግልቢያ ፈረስ አይሆንም፡፡ከዚህ በፊትም ስንት ከብቶች ውጭ አሳድረህ በጅብ እንዳስበላህ አትረሳውም አይደል…አንተ ላይ ያለኝ ትግስት አልቋል፡፡››

አቶ ፍሰሀ አየር ወደውስጡ ሳበ ። "ጌታ ሆይ፣ እኛን ውጥንቅጥ ውስጥ የሚያስገባን ነገር ከፊታችን ተደቅኖ እያለ ስለእሱ እንኳን ተረጋግተን ማሰብ አልችልም። በቃ ከፊቴ ጥፋልኝ…ሰኞ ቼክህ እንዲዘጋጅልህ አደርጋለው፣እዎ እርባታ ድርጅቱ ፋይናንስ ክፍል ጋር አስቀምጥልሀለው…ከዛሬ ጀመሮ እዚህም ሆነ የስራ ቦታ አይንህን ማየት አልፍግም፡፡››ቁርጥ ያለውን የመጨረሻ ውሳኔውን አሳወቀው፡፡፡

"አንድ ተጨማሪ እድል ስጠኝ ጋሽ ፍሰሀ በልጆቼ እምላለው…ሁለተኛ አላሳዝንህም፡፡››

"ይህን ንግግር ከዚህ በፊትም በተደጋጋሚ ሰምቼዋለሁ።አሁን በጥበቃ እያስገፈተርኩ ሳላስወጣህ በክብር ጊቢዬን ለቀህልኝ ውጣ፡፡››
"ጋሽ ፍሰሀ…"

"ደህና ሁን… እና መልካም ዕድል "

አባቱን ተወና የልጁን የጁኒዬርን አይን አይን ማየት ጀመረ …ከልጅነቱ ጀምሮ የሚያውቀውና ሲንከባከበው የኖረ ልጅ ስለሆነ የአባቱን ሀሳብ ለማስለወጥ የሆነ ነገር ይላል ብሎ ነበር የጠበቀው.. ጁኒየር ግን ዓይኖቹን ወደመሬት ደፋ ፡፡ ጋሽ ሙስጠፋ በመጨረሻ
ያደረገው ቦት ጫማ ላይ የተጣበቀውን ጭቃ እያራገፈ እንገቱን እንደደፋ ጊቢውን ለቆ ወጣ።የግቢው በር መዘጋቱን እንደተሰማ ጁኒየር ወደአባቱ ተመለከተና"እንደምታባርረው አላውቅም ነበር" ሲል በቁጭት ተናገረ።

" በቃ..ከአሁን ወዲህ ከእሱ ምንም ጥቅም ማግኘት አይቻልም…እድሜው ገፋቷል ጉልበቱም ደክሞል…ዛሬ ፈረሱን እንዲሰበር ካደረገ ነገ ራሱን ይሰብርና የእድሜ ልክ ሸክም ነው የሚሆንብን።"

"ቢሆንስ!ማባረሩ አስፈላጊ ነበር? ለጥፋቶቹ ልትጮህበት..ወይንም በገንዘብ ልትቀጣው ትችል ነበር ፣ወይንም ደግሞ አንዳንድ ኃላፊነቶቹ አንስተሀው ቀላል ስራ ላይ እንዲመደብ ማድረግ ትችል ነበር ፡፡››

‹‹ነገርኩህ እኮ ከአሁን በኋላ አያስፈልገንም….ከዛፎች ትምህርት መውሰድ አለብህ..ቅርንጫፋቸው ላይ ያሉ ቅጠሎች ሲደርቁ ወዲያው ከላያቸው ላይ አራግፈው ያስወግዷቸዋል….ህይወት እንደዛ ነው….››

‹‹ቢሆንም ውሳኔ ጭካኔ የታከለበት ነው፡፡››

"ይህን ንግድ የምትሠራ ከሆነ ልጄ፣ ልብህ እንደብረት ጠንካራና ደንዳና መሆን አለበት።

ሥራው ሁልጊዜ አስደሳች አይደለም፣ ታውቃለህ። ደንበኞችን የሚያምር እራት ከመጋበዝና ከሚስቶቻቸውና ከሴት ልጆቻቸው ጋር ከመሽኮርመም የበለጠ ብዙ ነገር አለ።››በማለት ልጁን በአሽሙር ወጋው፡፡

ጁኒዬር ሱልጣን ላይ የተወሰደውን ከባድ ቅጣት ለመቀበል ከብዶት ራሱን ወዘወዘ፣ ከዛ በእጁ ከያዘው ቢራ አንዴ ተጎነጨለትና‹‹ቅድም ከዳኛው ጋር በስልክ ስታወራ ነበር….ስለሰሎሜ ልጅ መሰለኝ?››ሲል ጠየቀው፡፡

‹‹አዎ ….ዛሬ ዳኛውን ለማናገር ቢሮው ሄዳ ነበር››

‹‹ እንዴ?››

"አድርጋዋለች፣ ይህን ለማድረግ ጊዜ እንዳላጠፋች አስተውል። ዳኛው በሁኔታው በጣም ነው የተደናገጠው፡፡ ዳኛ ጡረታ በመውጫ ጊዜው እንዲህ አይነት ፈታኝ ጉዳይ ስለተጋረጠበት ለስሙ ፈርቷል።"

"አለም ከእሱ ምን ፈለጋ ነው?"
44👍7