ስንክሳር
7.32K subscribers
825 photos
4 videos
37 files
237 links
በስንክሳር channal ስንክሳሩ ተገልጦ ቅዱሳን ይዘከራሉ፣ ወቅቱን የጠበቁ መረጃዎችን ያገኛሉ፡፡ ይከታተሉን!
Download Telegram
💚💛 #ቅድስት_አትናስያ 💛❤️
የዚህች ቅድስት ሕይወት በብዛት የእግዚአብሔርን ቸርነትና የንስሃን ፍጹምነት የሚያሳይ ነው:: ጥንተ ነገሩስ.እንደ ምን ነው ቢሉ:-
ቅድስት አትናስያ ግብፃዊት ስትሆን የነበረችውም #መኑፍ
በሚባል አውራጃ በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን ነው:: ይህ ዘመን
"ዘመነ ከዋክብት" ይባል ነበር:: ከቁጥር የበዙ ቅዱሳንም በዘመኑ ነበሩ:: ቅድስት አትናስያም ከክርስቲያን ወላጆች ተወልዳ:
እንደሚገባ አድጋ: ገና በወጣትነቷ ሁለቱም ወላጆቿ ሞቱባት:: ነገር ግን ብዙ ሃብት ትተውላታልና ምን
እንደምታደርገው ሃሳብ ሆናት:: #መንፈስ_ቅዱስ ግን
መልካሙን ሕሊና አደላትና አብርሃማዊ ሥራን ለመሥራት
ቆረጠች:: መጀመሪያ አገልጋዮችን አዘጋጀች:: እንደየ ወገኑ
ለእንግዶችና ለነዳያን ቤትን ሠራች:: በጐውን እድል
መርጣለችና ለብዙ ዓመታት ለነዳያን በማድላት: እንግዶችን
በመቀበል ተጠመደች:: በዚህ ሥራዋም እግዚአብሔርንም
ሰውንም ደስ አሰኘች::
ግብሯ እንዲህ ነው:: በሌሊት ጸሎት: በመዓልት ግን
እንግዶችን መቀበል: እግር ማጠብ: ማስትናገድ: ማስተኛት:
ስንቅ አሰንቆ መስደድ ነው:: በዚህ ግብሯ ከምንም በላይ የወቅቱን ጻድቃን አስደስታለች:: በዚያው ልክ ግን ዲያብሎስ ተቆጥቶ ይከተላት ጀመር::
በብዙ ጐዳና አልሳካልህ ቢለውም በክፉ ጐረቤቶቿ አማካኝነት ግን ተሳካለት:: የአካባቢዋ ሰወች ወደ እርሷ ተሰብስበው በብዙ ማታለል ከቅድስና ሕይወቷ ፈቀቅ
እንድትል አደረጉ:: እነርሱ መልካም ሥራዋን ያስተዋት በመልክ ቆንጆ ነበረችና
ይህንን ተጠቅመው ነው:: "ውበትና ሀብትሽን አታባክኚ"
ብለው ከጐዳና አስወጧት:: መጽሐፍ ክፉ ባልንጀርነትን
የሚቃወመው ለዛ ነው:: መልካም #ክርስቲያን ማለት
ባልንጀራውን የሚመርጥ ነው::
+የሚገርመው ያን ያህል እንግዳ ተቀብላበት ያላለቀ ገንዘብ
አሁን ግን ተመናመነ:: ክፉዎቹ ምክራቸውን ቀጠሉ:: አካሏን
እንድትሸጥ አሳምነው ሴተኛ አዳሪ አደረጉዋት:: ባንዴ ከዚያ
የቅድስና ከፍታ ወርዳ አካሏን ለዝሙት የምትሸጥ ሆነች::
+ነገሩን የሰሙ ገዳማውያን ሁሉ አዘኑ: አለቀሱላት:: ይልቁኑ
ለእነሱ የእናት ያህል ደግ ነበረችና ከዲያብሎስ ሴራ
ሊታደጉዋት ቆረጡ:: ከመካከላቸውም #ቅዱስ_ዮሐንስ_
ሐጺርን ለዚህ ተግባር መረጡ:: እርሱ በአጋንንት ላይ ስልጣን
ያለው ሰው ነውና::
እነርሱ ሱባ዗ ይዘውላት አባ ዮሐንስ ሐጺር ወደ መኑፍ
ከተማ ሔደ: ወደ ቤቷም ደረሰ:: ጠባቂዋን አስፈቅዶ ሲገባ
ለረከሰው ድርጊት የመጣ ሰው መስሏት ተዘጋጅታ ነበር:: አባ
ዮሐንስ ሐጺር ግን አጋንንትን ያርቅ ዘንድ እየዘመረ ገባ::
"እመኒ ሖርኩ ማዕከለ ጽላሎተ ሞት . . . በሞት ጥላ ሥር
እንኩዋ ብሔድ አንተ ከኔ ጋር ነሕና ክፉን አልፈራም" እያለ
ቀረባት:: (መዝ. 22)
ፈጠን ብሎ ከጐኗ ተቀምጦ ቅዱሱ ምርር ብሎ አለቀሰ::
አትናስያ ደንግጣ "ምነው?" አለችው:: "የአጋንንት ሠራዊት
በራስሽ ላይ ሆነው እየጨፈሩኮ ነው" አላት:: አስከትሎም
አጋንንቱን በጸሎቱ ቢያርቅላት በአንዴ ወደ ልቧ ተመለሰች::
ከእንቅልፍ እንደሚነቃ ሰው የሠራችውን ሁሉ ማመን
አቃታት:: ተስፋም ቆረጠች:: ቅዱስ ዮሐንስ ግን
"ግዴለሽም: ንስሃ ግቢ:: ፈጣሪ ይምርሻል" ብሎ
አሳመናት:: "እሺ አባቴ" ብላ ከቀደመው ዘመን ሥርዓት
ያለውን አንዱን ቀሚስ ለብሳ: ጫማ ሳትጫማ: ሌላ ልብስ
ሳትደርብ: ምንም ነገር ሳትይዝ ከቤት ወጣች::
ቤቷን አልዘጋችም:: ዘወር ብላ ወደ ሁዋላም አልተመለከተችም:: ቅዱሱን ተከትላ ጉዞ ወደ በርሃ ሆነ:: ያበእንክብካቤ የኖረ አካል እሾህና እንቅፋት: ብርድና ፀሐይ
ጐበኘው:: ሲመሽ እጅግ ደክሟታልና "እረፊ" ብሏት ሊጸልይ
ፈቀቅ አለ:: መንፈቀ ሌሊት በሆነ ጊዜ #መላእክት ከሰማይ የብርሃን
ዓምድ ዘርግተው አንዲትን ነፍስ በዝማሬ ሲያሳርጉ አየ::
"የማን ነፍስ ትሆን" ብሎ ወደ #አትናስያ ሲሔድ መሬት ላይ
ዘንበል ብላ ዐርፋ አገኛት:: ቅዱሱም "ጌታ ሆይ! ምነው
ለንስሃ እንኩዋ ብታበቃት?" ብሎ አለቀሰ:: ፈጣሪ ከሰማይ ተናገረ:- "ገና ከቤቷ ተጸጽታ ስትወጣ ነው
ይቅር ያልኩዋትና ደስ ይበላችሁ" አለው:: ይህንን የአምላክ
ቃል ሁሉም ገዳማውያን ሰምተው እጅግ ደስ አላቸው:: "ጻድቅ 7 ጊዜ ይወድቃልና: 7 ጊዜ ይነሳል::"
@dn yordanos
💚💛 ጻድቃን እንድራኒቆስ ወአትናስያ 💛❤️
ሁለቱ ቅዱሳን ባል እና ሚስት (ባለትዳር) ናቸው:: የነበረበት ዘመን 4ኛው መቶ ክ/ዘመን ነው:: እስኪ #እግዚአብሔር የቀደሰው ጋብቻ ምን እንደሚመስል እንመልከት::

#እንድራኒቆስና_አትናስያ በዘመናቸው ከልጅነት ጀምረው ቃለ እግዚአብሔርን የሚሰሙ : ለወላጆቻቸው የሚታዘዙ ነበሩ:: ዘመኑ ደርሶ በሚገባው የተክሊል ሥርዓት ጋብቻቸውን ፈጸሙ:: 40 ቀን ከተፈጸመ በሁዋላ ከምንም ነገር በፊት 2ቱ ቁጭ ብለው ተወያዩ::

የውይይታቸው ርዕስ ደግሞ "ፈጣሪያችን በምን እናስደስተው" የሚል ነበር:: ውይይታቸው የጠናቀቀው በእነዚህ ውሳኔዎች ነው::
1.ሁልጊዜም እንግዳ መቀበል አለብን::
2.ነዳያን ከቤታችን ሊጠፉ አይገባም::
3.ጸሎት : ጾምና ስግደት በቤት ውስጥ አይቁዋረጥም::
4.አብሮ ለመተኛት መቸኮል የለብንም::

እነርሱ መልካምን አስበዋልና አምላክ የሰጣቸውን ሃብት ሲመጸውቱ ኖሩ:: ከዘመናት የቅድስና ጉዞ በሁዋላ በፈቃደ እግዚአብሔር 2 ልጆችን አከታትለው ወለዱ:: ወንዱን "#ዮሐንስ" : ሴቷን ደግሞ "#ማርያም" አሏት::

እነርሱን ከወለዱ በሁዋላ እንደ ገና ሌላ ውሳኔ አሳለፉ:: "ይህንን ላደረገልን ጌታ ከዚህ በሁዋላ አልጋ እንለያለን" ብለው ለ12 ዓመታት በጾምና በጸሎት ተወሰኑ::
+ሕጻናቱ ዮሐንስና ማርያም በቅንነት አድገው እድሜአቸው 12 ሲሆን 2ቱም በአንድ ቀን ታመው ሞቱ:: ይህ ለአንድ ወላጅ የመጨረሻው አሰቃቂ ፈተና ነው:: ሁሉቱም (እንድራኒቆስና ሚስቱ አትናስያ) ልጆቻቸውን ታቅፈው ወስደው ቀበሩ::

#እንድራኒቆስ ከቀብር በሁዋላ ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብቶ ምርር ብሎ አለቀሰ:: ግን እንዲህ አለ:-
"አምላከ #ኢዮብ! አንተ ሰጠኸኝ:: አንተም ነሳኸኝ:: ስምህ ለዘለዓለም ይባረክ" ብሎ ሔደ:: እናት #አትናስያ ግን ከሐዘን ብዛት ልቡናዋ ሊሠወር ጥቂት ቀረው::

የልጆቿ መቃብር ላይ ተደፍታ ስታለቅስ ቅዱስ መልአክ ልቡናዋን ወደ ሰማይ አሳረገው:: ልጆቿ ዮሐንስና ማርያም በገነት ውስጥ ከቅዱሳን ጋር ሐሴትን ሲያደርጉም ተመለከተች:: ወዲያው ወደ ቤት ተመልሳ ለባሏ እንድራኒቆስ ያየችውን ነገረችውና ደስ አላቸው::

እዛው ላይ "ለዚህ ውለታው ከነፍሳችን ውጪ የምንሰጠው የለም" ብለው ሊመንኑ ተስማሙ:: እጅግ ሃብታሞች ነበሩና ነዳያንን ሰብስበው : ሃብት ንብረታቸውን : ቤት ርስታቸውን አካፍለው ወደ ገዳመ አስቄጥስ ሔዱ::

እርሷ ከሴቶች ገዳም : እርሱ ደግሞ ከወንዶቹ ገቡ:: ለ12 ዓመታት በፍጹም ተጋድሎ ለፈጣሪያቸው ተገዙ:: በእነዚህ ዘመናት ተያይተው : አንዱ ስለ ሌላው ሰምቶ አያውቅም:: በጸሎት ግን ያለማቁዋረጥ ይተሣሠቡ ነበር::

ከ12 ዓመታት በሁዋላ የፍቅር አምላክ በሁለቱም ልቡና በተመሳሳይ ሰዓት : ተመሳሳይ ሐሳብን አመጣ:: እርሱ ከአበ ምኔቱ (#ታላቁ_አባ_ዳንኤል) : እርሷም ከእመ ምኔቷ አስፈቅደው ወደ #ኢየሩሳሌም ከቅዱሳት መካናት ለመባረክ ጉዞ ጀመሩ:: በየፊናቸው ጥቂት እንደተጉዋዙ እርስ በርስ ተያዩ::
+እርሷ ለየችው:: እርሱ ግን ጭራሽ ሊለያት አልቻለም:: ይህም ጥበበ እግዚአብሔር ነው:: 2ቱም እየተጫወቱ : እየጸለዩ በሰላም ተባርከው ወደ ግብጽ ተመለሱ:: በእነዚህ ጊዜያት ቅድስት አትናስያን የሚለያት አልነበረም:: አካሏ በገድል ከመለወጡ ባሻገር የለበሰችው እንደ ወንድ መነኮሳት ነበር::

ወደ #ገዳመ_አስቄጥስ ሲደርሱ ጸጋው ተሰጥቶታልና #አባ_ዳንኤል ባልና ሚስት መሆናቸውን አወቀ:: "ለምን አብራችሁ አትኖሩም?" አላቸው:: "እኛ ደስ ይለናል" አሉት:: ከዚያ እርሷ እያወቀችው: እርሱ ሳያውቃት ለ12 ዓመታት አብረው በቅድስና ኖሩ::

ከእነዚህ ዘመናት በሁዋላ ግን ሐምሌ 28 ቀን ቅድስት #አትናስያ ታመመች:: አባ ዳንኤል ሥጋውን ደሙን አቀብሏትም ዐረፈች:: ሊገንዟት ሲቀርቡ ቅዱስ #እንድራኒቆስ መልኩዋን ልብ ቢለው ሚስቱ ናት::

በአንድ ጊዜ ሚስቱንና የሚወደውን ባልንጀራ በማጣቱ አለቀሰ:: እርሷን ቀብረው ወደ በዓቱ ተመልሶ "ጌታ ሆይ! ውሰደኝ?" አለ:: እርሱም ተከትሏት ዐረፈ:: አባ ዳንኤል እርሱንም ቀብሮ ጥዑም ዜናቸውን ጻፈ::
From:- dn yordanos abebe
@senkesar @senkesar